Friday, April 16, 2010

"ዱድ! ብሩን አሳዬኝ!" Dude, Show Me the Money!


በውጭ የሚኖረው ወጣት ባገሩ ፖለቲካ ንቁ ተሳታፊ አለመሆኑ ያሳዝነኛል። አንዳንዴማ ከዚያም ያለፈ ነው የሚያደርገኝ። ሰሞኑን ታዲያ ጃዋር ሲራጅ መሀመድ የተባለ ኦሮሞ ወገኔ ተስፋ ዘራብኝ።

ዲሲ በተካሄደው ዓውደ ጥናት ላይ ነው የ24 ዓመቱ ጃዋር “ዱድ” ሥራውን ሲያቀርብ ያዳመጥሁት። የነጠሩ ሊቆች የሚወጡበት የስታንፈርድ ዩኒቨርስቲ ምሩቅ ነውና የዋዛ 24 ዓመት እንዳይመስላችሁ። ባንፃሩ ደግሞ ከጃዋር ጋር መድረክ የተጋሩት ምሁራን ባገራችን ፓለቲካ ውስጥ ቆይታ ያደረጉ፤ የቤታችንን ግድግዳ ጌጦች ያህል የምናውቃቸው ባለውለታዎቻችን ነበሩ። እዚህ ላይ በጃዋርና በሌሎቹ መሀከል የነበረው የዕድሜ ልዩነት ከልክ በላይ እንዳስደመመኝና ጥያቄዎች እንደጫረብኝ ልደብቃችሁ አልችልም። ያነሳቸው ነጥቦች ጆሮዬ ላይ ሲዘምሩብኝ ነው የከረሙትና ላከፍላችሁ ብዕሬን አነሳሁ።

ሦስት ቀን ስለፈጀው ዓውደ ጥናት ባንዲት አንቀጽ ውስጥ ጥቂት ልበልና ጃዋር በምሳሌነት እንዲያገለግለኝ ወደመረጥሁት ወደ ወጣቱ ጉዳይ እመለሳለሁ። ያለጥርጥር እጅግ የተሳካ ስብሰባ ነበር። አዘጋጆቹ ብዙ ጉልበት እንዳፈሰሱበት የሚመሰክሩ አሻራዎች ስላየሁ አብዝቼ ላመሰግናቸው እወዳለሁ። አቅራቢዎቹም፤ ታዳሚውም ሀላፊነታቸውን ሲወጡ ያየሁት ፍጹም በሰከነ ቋንቋና በደርባባ ባህርይ ስለነበር ስልጡን ፖለቲካ ተገቢ ቦታውን እያገኘ ነው አልሁ። ታዲያ በባህላችን “ግን” ካልተጨመረበት ምስጋና ምስጋና አይሆንምና ለወደፊቱ ይታሰብበት ዘንድ ላዘጋጆቹ ትንሺ ቅር ያለኝን ነገር ላካፍላቸው እወዳለሁ። የኢትዮጵያ ችግር በርካታ ሆኖባችሁ ይመስለኛል ሁሉን ርዕስ ለመሸፈን ባደረጋችሁት ሙከራ ዓቢይ ጉዳዮች ላይ ሊያወያዩን የመጡ ምሁራን ሰዓት እያነሳቸው ነገራቸውን እንዲቆራርጡ መገደዳቸው አሳቆኛል። ያቅራቢዎቹን ቁጥር ሰብሰብ ማድረግ ቅያሜ የሚያስከትል ሆኖባችሁ ይሆን?

የጃዋር አቀራረብ የወጣት ለዛና የወጣት ነፃ አስተሳሰብ የተንጸባረቀበት ነበር። በዝግጅት ደረጃም የተሻለ ሆኖ አግኝቸዋለሁ - ፓወር-ፖይንት ተክኖሎጅን ተጠቅሟል፤ የኢትዮጵያ ፖሊቲካ ምን ዓይነት አጣብቂኝ ውስጥ እንዳለ ለማስረዳት በቃላት ጋጋታና በ “እጠቅሳልሁ” “አልጠቅስም” አባዜ አልታሰረም። በአዕምሮ ውስጥ ታትሞ በሚቀር ቪዡዋል ቻርት አማካይነት በሁለት የፖለቲካ ጠርዞች ላይ የሚገኙትን አስተሳሰቦች ደህና አድርጎ ተንትኖ መፍትሔው መሀል ላይ መገናኘት ብቻ መሆኑን በሚገባ አስረድቷል።

በርሱ ስሌት በ “ብሔርተኛውም” ሆነ “ኢትዮጵያዊነት” በሚለው ካምፕ ውስጥ አክራሪ ዓይነት አቋም ያላቸው ከ 20% አይበልጡም። ቀሪው 80% ፍጹም ሠላማዊ ኑሮ ፈላጊና የብሔር ቅርሱን ለማዳበር የሚያስችል ሥርዓት እስካገኘ ድረስ በኢትዮጵያዊነት መለያው የሚኮራ ነው። “ሆኖም ግን በየመድረኩና በየቤቱ ከሚመነዘሩት የመልካም ምኞት መግለጫዎች ባሻገር ተጨባጭ ሥራ መሠራት አለበት” አለ።

“ፈተናው እዚህ ላይ ነው ወገኖቼ! አዲሱ ትውልድ ለዙሪያ ጥምጥም ፍልስፍና፤ ለዲስኩርና ለቃላት ማንጠር ትዕግሥትም አንጀትም የለውም” ሲል አስጠነቀቀ ጃዋር ድምጹን ከረር አድርጎ። አውራ ጣቱንና የታጠፈች ሌባ ጣቱን ሕዝቡ እንዲያይለት ከፍ አድርጎ ደጋገሞ እያፋተገ “ይህ ትውልድ የ ሾው-ሚ-ዘ መኒ! ትውልድ መሆኑን መቀበል አለብን!” አለ። ጭብጨባውና ቻቻታው መለኪያ ከሆነ በዚያች ወቅት የታዳሚውን ቀልብ ሙልጭ አድርጎ ኪሱ እንዳስገባ አልጠራጠርኩም። ለዚህም ነው “ዱድ! ብሩን አሳዬኝ!” የምትለዋን የጽሑፌ ርዕስ ያደረግኋት።

ጃዋር “ሾው-ሚ-ዘ መኒ!” ሲል ወጣቱ ትውልድ እንደሸቀጥ በገንዘብ የሚገዛ ነው ለማለት አልነበረም። “ባዶ ቃላት አትመግበኝ! ከዚህ የጥርጣሬ ዘመን ወደመተማመን ዘመን እንዴት እንደምንሸጋገር ያለህን ተጨባጭ የመፍትሄ ሀሳብ እፊቴ ቁጭ አድርግልኝ” ማለቱ ነበር። የጃዋር ትውልድ ባጠቃላይ፤ የአማራ/ትግሬ ዝርያ የሌለው ክፍል ደግሞ በተለይ፤ አዲሱ የኢትዮጵያዊነት ገጽታ በማያሻማና ቅሬታን በሚያጠፋ መልኩ ተነድፎ ሲተገበር መሳተፍ እንደሚፈልግ ጃዋር አሳውቋል። ይህን ዕውን ለማደረግ የሚወሰዱ ርምጃዎችም በዕለት-ተለት ግንኙነቶቻችን ሳይቀር የሚንጸባረቁ መሆን እንደሚገባቸው በአጽንኦት ነበር ያስረዳው። ነጥቡን ለማስረገጥ መሰለኝ፤ መድረኩ ላይ ከርሱ ጋር የተሰየሙትንና ዞር ብሎም ታዳሚውን ሕዝብ በዓይኑ ቃኘት አድርጎ “ይህ ፎቶግራፍ ኢትዮጵያዊነትን በቅጡ ስለማንጸባረቁ እርግጠኛ አይደለሁም” አለ።

በዚህ ጊዜ ነበር የጉባዔው አዘጋጆች ወደ መድረኩ ብቅ ብለው በኢትዮጵያ ጉዳይ የሚያገባቸውን ሁሉ መጋበዛቸውን የገለጹት። በድረ ገፆች አማካይነት ከተደረገው ግልጽ ግብዣ በተጨማሪ ካንዳንዶቹ ጋር ቀጥታ ግንኙነቶች ተደርጎ አመርቂ ምላሺ እንዳልተገኘ አስረዱ።

እዚህም ላይ “ሕምምም!” ያሰኘ ቅጽበት ተፈጥሮ ነበር። ጃዋር ያዘጋጆቹን ጥረት አድንቆ እርሱ ራሱ ጉባኤው ላይ ቢገኝ ምን ዓይነት ምቾት እንደሚሰማው ጥርጣሬ አድሮበት እንደነበረ ተናዘዘ። ሆኖም ግን ላቀረባቸው ነጥቦች ሕዝቡ ይሰጠው የነበረውን ከበሬታ ካዬ በኋላ በውሳኔው እንደኮራ አልሸሸገም። በመቀጠልም “የቀሩት ወገኖቻችን ካልመጡ ከመንገዳችን ወጥተን የምናደርገው የማግባባትና የማረጋጋት ሥራ በቂ አልነበረም ማለት ነው” ብሎ በዚህ ረገድ ብዙ እንደሚቀረን አስተማረ። ይህ ሰው በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ ገና ብዙ ሚና እንደሚኖረው፤ በዕድሜም በብሔሩም በዕምነቱም እርሱን መሰል ዜጎችን በመሳብ ረገድ ከፍተኛ አስተዋጻኦ እንደሚያደርግ ፍንትው ብሎ ነው የታየኝ።

በዚህ ስብሰባ ላይ ወጣቱን ትውልድ ወደፊት የማምጣቱ አስፈላጊነት አንገብጋቢ እንደሆነ በብዛት ተወስቷል። የ 24 ዓመቱ ወጣት 55+ ሶች ጋር መቅረቡ ነው ጥያቄውን ከምኔውም በበለጠ ትርጉም የሰጠው። አንዳንዶቹ አቅራቢዎች ይህን ጉዳይ ሲያወሱ ጥፋት እንዳጠፋ ሰው መሸማቀቅ አይቸባቸዋለሁ። በዚህ ፈጽሞ አልስማማም። የቀድሞዎቹ ብዙ መሥዋዕትነት ለመክፈላቸውና ብዙ ለማስተማራቸው አጠያያቂ አይደለም። በወቅቱ ተረካቢ አለማፍራታቸው፤ አንዳንዶቹ ደግሞ ወንበር የሙጥኝ ማለታቸው፤ ከሁሉም በላይ ደግሞ ወጣቱን የሚስብ ራዕይና የሚጥመው አሠራር አለመንደፋቸው ጥፋት ነው። አባጣ ጎባጣ ያልበዛበት የትውልድ ሺግግር ሳያደርጉ በየጓዳቸው ቢከተቱ ግን የጥፋትም ጥፋት ይሆንባቸዋል። ስለዚህ እስቲ ፈረንጆቹ “ሜንተርሺፕ” የሚሉትን ነገር ይሞክሩት። ያንዳንድ ወጣት እጅ ይያዙ።

ወደ ጃዋር ልመለስና። በቃላቶቹም ቃላቶቹን ባጀቡት ስሜቶችም አዲስ የኢትዮጵያዊነት ራዕይ መቀረጽ እንዳለበት ነው አበክሮ ያስተማረው። ለምን በሉ? እንደርሱ ባሉ ወገኖቻችን መንደር እስከዛሬ የምናውቀው “ኢትዮጵያዊነት” በሰሜኑና በደገኛው ባህል እንዲሁም በዚያ ሕዝብ ሳይኪ ዙሪያ የተገነባ ነውና ሌላውን ጮቤ ሊያስረግጠው መጠበቅ የለበትም። ባመዛኙ እንዲያገለግልም እንዲያኮራም የተደረገው የዚያኑ የሰሜን ደገኛ ሰው ስለሚመስል አንዳንዴ ቁጣ ቢያስነሳም መገርም እንደሌለብን ቃላት ሳይልቆጥብ ተናገረ። ከቶውንም “ና በድሮው ኢትዮጵያዊነት ዙሪያ እንሰባሰብ ብትለኝ አይመቸኝምና አቤት ለማለት አልጣደፍም” ነበር ያለው። እንዴ ካልተመቸው ምን ይበል?

እንግዲህ ያልሆነ ትርጉም ለመስጠትና አጉል ድምዳሜ ላይ ለመድረስ አትጣደፉ! ጃዋር በኢትዮጵያዊነቱ የሚያምን፤ የነገው እንጅ ያለፈው ብዙም ፋይዳ እንደሌለው የተረዳ፤ ነገር ግን አዲሱ የኢትዮጵያዊነት ራዕይ አንዱን እላይ ሌላውን እታች በማያደርግ መልኩ በድፍረትና በስልት መቀረጽ እንዳለበት ነው ያሳወቀው። ዜጎችንና ብሔረሰቦችን የሚያቀራርብ፤ መተማመንን የሚያሰርጽ ድልድይ በያቅጣጫው ተዘርግቶ ባዲስ ጥርጊያ መንገድ ጉዟችንን እንድንጀምር ነው የሚመኘው። ችግራችንን በሠላማዊ ትግልና ተጨባጭ ርምጃዎች በመውሰድ እናስወግድ ነው የሚለው። ለኔም ለናንተም ጆሮ ከዚህ የተሻለ ጥዑም ሙዚቃ አለ?

ጃዋር የመጀመሪያውን ርምጃ ወስዷል፤ እኛስ ጎረቤታችንና ሥራ ቦታ ከምናገኘው ኦሮሞ፤ ትግሬ፤ ወላይታ፤ ሀረሬ አማራ..ወዘተ ጋር ለመቀላቀልና ለመወዳጀት ከመንገዳችን ወጥተን ሙከራ እያደረግን ነው? (አዎንና! ከመንገዳችን ወጥተን!) እውነተኛ ፍቅር የተመላበት ፈገግታ እየሰጠናቸው ነው? እንድንመቻቸው እያደረግን ነው? ጃዋር አዘጋጆቹን ያሳሰበውን አትዘንጉ። “እኛ ግብዣ አስተላልፈንላቸዋል መምጣት የነርሱ ፋንታ ነው ብላችሁ መቀመጥ የለባችሁም” ነበር ያላቸው። ካስፈለገ እጃቸውን ጎትታችሁም እንደማለት ጭምር መሰለኝ። ዕውነት አለው ወዳጄ!

የጃዋርን ዋና ቁምነገር አትርሱ። ወደድንም ጠላንም አዲሱ ትውልድ መድረክ ላይ ብቅ እያለ ነው። የተፈጥሮ ግዴታ ጭምር ነውና። አዲሱ ትውልድ ደግሞ የ “ሾው-ሚ-ዘ መኒ!” ትውልድ ነው። ከተስፋ ይልቅ ተጨባጭ ርምጃ፤ ከጥላቻ ይልቅ ፍቅር፤ ከቃላት ጋጋት ይልቅ ቅልጥፍ ባለ ቋንቋ እንድናወጋው ነው የሚፈልገው። ለሚንዛዛና ለቃላት አንጥረኛ ጊዜ የለውም። ለርሱ ጊዜ ወርቁ ነው።

የምወዳቸውና የምኮራባቸው የራሴ ልጆችም የጃዋርን መሥመር በጣሙን እንደሚጋሩ ገልጸውልኛልና ነገሩ ዕውነት ሳይኖረው አይቀርም ወዳጆቼ!

kuchiye@gmail.com

Thursday, April 01, 2010

ተቃዋሚው ብቃት አለው? - “Is the Ethiopian Opposition Viable?”


በሕዝብ አዕምሮ ውስጥ ጥርጣሬ የመፍጠርን ያህል የፕሮፓጋንዳ ድል የለም። ለዚህ ማስረጃ ከፈለጋችሁ የሂትለር ቀኝ-እጅና የፕሮፓጋንዳ ጠበብት የነበረውን ጎብልስን ጠይቁት። ዓለም ሲፈጠር የት ነበርክ ትሉኛላችሁ እንጅ ከያን ጊዜ ጀምሮ ይመስለኛል ጥርጣሬ መፍጠር የፕሮፓጋንዳ መሣሪያ የሆነው።

ቀልጠፍ ብዬ ወደተነሳሁበት ርዕስ ልመለስና “በርግጥ ተቃዋሚው አገር የመምራት ብቃት አለው?” የሚል ጥያቄ መናፈስ የጀመረው በ‘97 ምርጫ ማግስት እንደነበር ትዝ ይለኛል። ቅንጅት ውስጥ በተፈጠረው ውዝግብ ቆሺታቸው ያረረ ደጋፊዎች ሳይቀሩ ነው አባባሉን የብስጭታቸው መወጫ ያደረጉት - ትልቅ ስህተት! በጣም ትልቅ ስህተት! ኢሕአዴግ ደግሞ እንኳንስ ይችን ያህል ቀዳዳ አግኝቶ እንዲያውም እንዲያው ነው በሕዝቡ ውስጥ የተፈጠረውን የጥርጣሬና የብሺቀት መንፈስ ደህና አድርጎ አራገበው።

እዚህ ላይ ባንድ ነገር እንስማማ። የሰው ልጅ በፍጥረቱ ተጠራጣሪና የ7 ቀን 24 ሠዓት ኑሮው በስጋት የታጠረ መሆኑን አትክዱኝም። ለዚህ አይደል እንዴ ኢንሹራንስ የሚገዛው? አጥር የሚያጥረው? ብቻውን የሚያወራውና የሚቃዠው? ልብ ብላችሁ ከሆነ ፖለቲከኞች ይህን ሰብዓዊ ደካማ ጎን ደህና አድርገው ነው የሚበዘብዙት....

“ነውጠኞች የቀድሞውን ሥርዓት ሊያመጡብህ ነው! እኛ ከሌለን አገር ትበተናለች! ሠላማዊ ኑሮህ ይናጋል! የብሔረሰቦች ነጻነት ይገፈፋል! የርስ በርስ ጦርነት ይነሳል! የስልምና አክራሪዎች አገርህን ይወሩታል! ተቃዋሚው አገር የማስተዳደር አቅም የለውም!”


የኢሕአዴግ ፕሮፓጋንዳ መዘውር ከላይ ለአብነት የጠቀስኋቸውን የስጋት መርዕዶች በመደጋገም እንደሚጠቀምባቸው እናውቃለን። “በመደጋገም” የምትለዋን ቃል እንደዋዛ አትዩብኝ። በፕሮፓጋንዳ ሳይንስ “ስጋት” ታላቅ ወንድም ቢሆን “ድግግሞሺ” ደግሞ ታናሹ ነው። እዚህ ላይ የኢሕአዴግ ዘመቻ በኢትዮጵያ ውስጥ የስጋት ድባብ አልፈጠረም የሚለኝ ቢመጣ “አንተ የሰጎኗ ወንድም ነህ!” ከማለት አላስተርፈውም። ዕለት ተለት በስጋት አየር ውስጥ የሚኖሩት ወገኖቻችን ቀርተው ያሜሪካና ያውሮፓ መንግሥታትም የዚህ ፕሮፓጋንዳ ዘመቻ ጭዳ ሆነዋል። “ህምምም!” በሚያሰኝ ጥርጣሬ ውስጥ ለመውደቃቸው አንድና ሁለት የለውም። ራሳቸው ሳይደብቁ ይነግሩን የለም እንዴ?

ታዲያ ሁለት ዓቢይ ችግሮች ይታዩኛል። አንደኛው ችግር ተቃዋሚው ወገን የዚህን ፕሮፓጋንዳ አደገኛነት ተገንዝቦ ቀጣይነት ያለው አምካኝ ፕሮፓጋንዳ በፈረንጁ ሰፈር ጭምር አለማካሄዱ ሲሆን ሁለተኛው ችግር ደግሞ የተቃዋሚው የፖለቲካ ገጽታ በመንግሥት እንዲነደፍ መፈቀዱ ነው። በሁለቱም ላይ ያለኝን የተሙን ሀሳብ አካፍላችኋለሁ።

በደፋር አስተያየት ልጀምርና ይህ ዘመን ኢትዮጵያን ወደከፍተኛ የዕድገት ደረጃ ለማሸጋገር ከምን ጊዜም የበለጠ ተነሳሺነት የገነነበት፤ የሰለጠነ የሰውና የማቴሪያል ኃይል የተከማቸበት ነው እላለሁ። በሌላ በኩል ደግሞ ተቃዋሚው ክፍል፤ በተለይም “መድረክ” ኢትዮጵያን ለማስተዳደር ያለው ብቃት ከየትኛውም ፓርቲና ስብስብ የላቀ ነው እላለሁ። እንዳላሰለቻችሁ በሦስት ዋቢዎች ብቻ ልወሰን።

የፖለቲካ ፕላትፎርም። የአንድነት/መድረክ ፖለቲካ ፕሮግራም የዜጎችን ችግር አበጥሮ የተረዳ ብቻ ሳይሆን ያጭርና የረጅም ጊዜ መፍትሄዎቻቸውንም የሚዘረዝር ነው። ያልተገደበ ሰብአዊና ዴሞክራሲያዊ መብት እንደሚኖር፤ የግል መሬትና ንብረት የሕገ መንግሥት ጽኑ ድጋፍ አግኝተው የኤኮኖሚና የማሕበራዊ እድገት አንቀሳቃሺ ሞተር እንደሚሆኑ፤ የኢትዮጵያ አንድነትና ልኡዋላዊነት ለድርድር የሚቀርብ እንደማይሆን፤ ብሔረሰቦችን የሚከፋፈል ፖሊሲ ተወግዶ ያንድ አገርና ያንድ ታላቅ ራዕይ ልጆች በሚያደርግ ፖሊሲ እንደሚተካ፤ 85ሚሊዮን ሕዝብ ህልውናውንና ስትራቴጅያዊ ጥቅሙን አደጋ ላይ በማይጥል መልክ ወደ ባሕር የመውጣት መብቱ እንደሚከበር፤.. ወዘተ ያስቀምጣል። ትናንት የቅንጅት ዛሬ ደግሞ ያንድነት የሆነው ራዕይ ገዥው ፓርቲ “አብዮታዊ ዴሞክራሲ” ከሚለው ራዕይ በዓይነትም በጥራትም የተሻለ፤ እጅግ በጣም የተሻለ ለመሆኑ ሕዝብ በቅጡ ያውቃል። ለዚህ ነበር በ ‘97ቱ ምርጫ ቅንጅትን የሾመው። ለዚህም ነው ዛሬ በአንድነትና በመድረክ ዙሪያ በሚያስደንቅ ቁርጠኝነት እየተሰባስበ ያለው። ሌላውን ለጊዜው እንተወውና በትግራይ ክልል እየተገለጸ ያለው የፓራዳይም ለውጥ አላስደነቃችሁም? ጥልቅና የምሥራች ትርጉም እንዳለው አልተረዳችሁም?

በቢሮክራሲ ልቀጥል። ማንኛውም ለሥልጣን የሚበቃ መንግሥት ሀገሪቱ አዳብራ ባቆየችው ያስተዳደር መዋቅር (ቢሮክራሲ) መገልገሉ ሀቅ ነው። ይህ የጦር ሠራዊቱን ይጨምራል። ምኒልክ ከዮሐንስ፤ ኃይለ ሥላሴ ከምኒልክ፤ ደርግ ከኃይለ ሥላሴ፤ ኢሕአዴግ ከደርግ በተረከቡት ቢሮክራሲ ነው አገር የመሩት። ሌላው ሀቅ ደግሞ እያንዳንዱ መንግሥት የተረከበውን ቢሮክራሲ አሻሽሎና አዳብሮ ለሚቀጥለው መንግሥት የማስረከቡ ዕውነታ ነው። በዚህ ስሌት እንደ ኢሕአዴግ ጠንካራ መሠረት ያለው፤ በተማረ የሰው ኃይልና በዘመናዊ የማኔጅመንት ዘይቤዎች የዳበረ ቢሮክራሲ የወረሰ መንግሥት አልነበረም። ኢሕአዴግ ራሱ ምን ዓይነት የመንግሥት-አስተዳደርና የማኔጅመንት ልምድ ይዞ በ1991 አዲስ አበባ እንደደረሰ የያኔ ሬዙሜውን ማዬት ይበቃል። በራሴ ላይ የጣልኩት የገጽ ማዕቀብ ከለከለኝ እንጅ ከአፄ ዮሐንስ እስከ ኢሕአዴግ ያሉት መንግሥታት ሥልጣን ሲይዙ የነበረባቸውን ፈተና አነጻጽርላችሁ ነበር። ላለፉት መንግሥታት ከልብ ታዝኑላቸዋላችሁ።

እዚህ ላይ ያች ልማዴ እንዳትቀር አንዳፍታ ከመሥመር ወጣ ልል ነው። ስለ ቢሮክራሲ ካወጋን ዘንድ “ቢሮክራሲ” ከፍተኛ የሥም ማጥፋት ዘመቻ የተካሄደበት ያገር ኃብት ነውና ይህን የተዛባ አመለካከት ማቃናት አለብን እላለሁ። ካጭር ትርጉሙ ብንነሳ “ቢሮክራሲ” ያንድ ትልቅና ውስብስብ መዋቅር አስተዳደራዊ አቅም ነው። በሹመት እየመጡ አናት ላይ ጉብ ከሚሉት አላፊዎች በስተቀር ሌላው ሕዝበ-ሠራዊት በሙያ ሚዛን እየተለካ እንደሚቀጠርበት ግዙፍ አገራዊ ፋብሪካ ተደርጎ ሊታይ ይችላል። መንግሥት ቢለወጥ፤ ሹም ከርቸሌ ቢወርድ፤ ጎርፍ ቢያጥለቀልቅ፤ ቢሮክራሲ ከቦታው ንቅንቅ አይልም። እንደ ዝቋላ ተራራና እንደ አዋሺ ወንዝ ካስቀመጡት ቦታ የሚገኝ ውሉን የማይስት ያገር ኃብት ነው ማለት ነው። ቢሮክራሲን ያልሆነ ጥላሸት የቀባው ባላባቱን፤ ከበርቴውን፤ ካፒታሊስቱንና ኢምፔሪያሊስቱን የሕዝብ ጠላት በማድረግ አንጀቱ ያልራሰለት የኮሚኒስት ሥርዓት ነበር። እንዲያው በሞቴ ኮሚኒስቶች የሚሉትን ከቁብ የሚጥፍ ሰው ተርፎ ይሆን?

በፓራዳይም ለውጥ ላጠቃል። ሦስተኛው ቁምነገር ደግሞ ለመድረክ መፈጠር ምክንያት የሆነ የፖለቲካ ክስተት መኖሩ ነው። የብሔር ፖለቲካ ከመሣሪያነት አልፎ ማቴሪያላዊም ሆነ ማህበራዊ ጠቀሜታ እንደማያስገኝለት ሕዝቡ መረዳት ከጀመረ ሰንበት ብሏል። መቼም ፖለቲከኞች ብልጥ አይደሉም? - የፓራዳይም ለውጥ ሕዝብ ውስጥ ሥር መስደዱን ከማረጋገጣቸው በፊት የአቋምና ያሰላለፍ ለውጥ አያደርጉም። ለዚህ ነው እንገነጠላለን ከሚሉት ጀምሮ ለዘብተኛ እስከሚባሉት ድረስ በብሔር ፖለቲካ ላይ ያላቸውን አቋም ሲከልሱ እያየን ያለነው። ዓለም ወደ አንድ ትንሺ መንደርነት እየተለወጠች በምትገኝበት በ 21ኛው ክፍለ ዘመን የብሔር ፖለቲካ የሚያራምዱ ሰዎች ከሌላ ፕላኔት እንደመጡ ፍጡሮች ይቆጠራሉና መለወጣቸው እሰዬ የሚያሰኝ ነው። የብሔር ፓለቲካ ያራምዱ የነበሩ ፓርቲዎች በመድረክ ውስጥ መሰባሰባቸው፤ በብሔር ፖለቲካ ዓለም ውስጥ ስማቸው የተጠራ እንደነ ስዬ አብርሃ፤ ነጋሶ ጊዳዳ፤ ገብሩ አሥራት፤ አረጋሺ አዳነና ቡልቻ ደመቅሳን የመሳሰሉ በመድረክ ውስጥ መሰባሰባቸው አንዳንዶች ሊያምኑ ከሚፈልጉት በላይ ጥልቅ መልዕክት ያዘለ ነው። ባጋጣሚና በድንገት የተከሰተ ፓራዳይም ሳይሆን ከ 45 ዓመት ተመክሮ የተወለደ ነው።

እዚህ ላይ “ተቃዋሚው ኢትዮጵያን ለመምራት ብቃት አለው?” ከሚል ጥያቄ ጋር ምን አገናኘው ብትሉ አልፈረድባችሁም። አያችሁ! ኢሕአዴግ ባለሙያና ደጋፊ የሚጨልፈው የብሔር ፖለቲካን በውድም በግድም ከሚያራምዱ ቁጥራቸው እየቀነሰና ወርዳቸው እየጠበበ ከሚገኝ የህብረተሰብ ኩሬዎች ነው። ባንጻሩ ደግሞ መድረክ ደጋፊና ባለሙያ የሚቀዳው እጅግ ሰፊ ከሆነ የህብረተሰብ ሃይቅ ነው። ለዚህ ነው ተቃዋሚው ክፍል፤ በተለይም “መድረክ” ኢትዮጵያን ለማስተዳደር ያለው ብቃት ከየትኛውም ፓርቲና ስብስብ የላቀ ነው ያልኩት - እመነሻዬ ላይ። የለየልኝ ቅን-አሳቢ መሆኔን ደጋግሜ ተናዝዣለሁና ቀሪዎቹ በብሔር ፖለቲካ ጠርዝ ላይ የሚገኙ ያገሬ ልጆች ከፊታቸው የተጋረደውን መጋረጃ እየቀደዱ አንድነትን፤ ኢትዮጵያዊነትንና ትልቅነትን እንዲያቅፉ እመኛለሁ።

ወዳጆቼ! ይችን ጽሁፍ ካነበባችሁ በኋላ በማወቅም ሆነ ባለማወቅ፤ በብስጭትም ሆነ በተንኮል ተነሳስታችሁ በተቃዋሚ ፓርቲዎች ችሎታ ላይ የጥርጣሬ አሉባልታ ብታናፍሱ ባደባባይ እሞግታችኋለሁ። ሲናፈስም ዝም ብላችሁ ካያችሁ ለእሰጥ-አገባ ተዘጋጁ። የምሬን ነው!