Thursday, September 24, 2009

አውራ የሌለው ምንም የለው! (No Leader no Glory!)


ሶሻሊዝም ካወረሰን መዘዝ አንዱ በ “ጋራ አመራር” ላይ ያለን የተወላገደ አስተሳሰብ ይመስለኛል። እዚህ ድምዳሜ ላይ የደረስሁት ጥቂት የማይባሉ ማሕበራዊና ፖለቲካ-ቀመስ ድርጅቶችን አሠራር ካገናዘብሁ በኋላ ነው።

ተደጋግፎ መኖር የግድ ከሆነበት ዘመን ጀምሮ በ “አውራ” መመራት አማራጭ አልተገኘለትም። ይህ ታዲያ በሰው ልጅ ዘር ብቻ የተገደበ እንዳይመስላችሁ። እንደ ንብ በደመ-ነፍስ የሚንቀሳቀሱት ሳይቀሩ አውራ ከሌላቸው ጣፋጭ ማር ቀርቶ ደረቅ ቂጣ መጋገር ይሳናቸዋል። ልብ ብላችሁ ከሆነ “አውራዎች” አላልኩም - ባንድ ቤት ውስጥና ባንድ ወቅት አንድ አውራ ብቻ ነው ሊኖር የሚችለውና ነው።

ጥሩ አውራ የጠለቀ ትምህርት፤ የተመሰከረ ልምድ፤ በሀቅ ለማገልገልና በውጤቱም ለመኩራት የጋለ ፍላጎት ያለው ነው። የሰውና የማቴሪያል ኃይሎችን አነቃቅቶና አስተባብሮ መሥራት ይችላል። በቅጣት ፋንታ ሽልማትን ማነቃቂያ መሣሪያው ያደርጋል። የሰዎችን አመኔታና ድጋፍ የሚያገኘው በተግባሩ ምሳሌ ሲሆንና ለሚያገለግለው ሕዝብ ፍቅርና ከበሬታ ሲያሳይ እንደሆነ ያውቃል።

ታዲያ እንዲህ ያለ ችሎታና ሥነ-ምግባር ያለውን ሰው የሚፈልገው ብዙ ነውና የኛ እናደርገው ካልን ከመንገዳችን ወጥተን ልናግባባውና ምቹ የሥራ አካባቢ ልንፈጥርለት ግዴታ ነው። በራዕይና በአጠቃላይ መርሆች ላይ ስምምነት እስካለን ድረስ ስልት የመቅረጹንና ውሳኔ የመስጠቱን ሥልጣን ለመሪውና እርሱ ላዋቀረው ቡድን መተው አለብን።

እሱ ላዋቀረው ቡድን?
አዎ! አውራው ላዋቀረው ቡድን። አንድን ድርጅት ወይንም መሪ ለሥልጣን የምናበቃው ብዙ አማራጮችን አገናዝበንና የዚህኛው ድርጅት ራዕይ ይጥመናል፤ ለኛም ላገራችንም ይበጃል ብለን ነውና የኛ ሀላፊነት እዚያ ላይ ማቆም አለበት። የመረጥነው የተሻለውን ፕሮግራም ብቻ ሳይሆን ፕሮግራሙን ለማስፈጸም በቂ ዝግጅትና ዕውቀት እንዲሁም ተአማኒነት አለው የምንለውን አውራ ጭምር ነው።

ልብ ብላችሁ ከሆነ በኢትዮጵያ ፖለቲካዊና ማሕበራዊ ድርጅቶች ውስጥ እንዲሰፍን የፈቀድነው ያሠራር ባህል አውራን ሺባ ያደርጋል። ዕውቀቱም ልምዱም ታማኝነቱም አለህና ና ምራን ካልነው በኋላ ለመምራት የሚያስችለውን ሥልጣን እንነፍገዋለን። ከማያውቁትና ከማያውቃቸው ሰዎች ጋር ተጣመድና ውጤት አሳይ እንለዋለን። በዕውቀትም በባሕርይም በምንም እርሱን ከማይመስሉ ሰዎች ጋር አቆራኝተን “እየተግባባችሁ” ሥሩ እንለዋለን። የማኔጅመንትን ሳይንስ ያልተማረው ገበሬ እንኳ ትጉውን በሬ ከአባያ በሬ ጋር አያጣምድም። የተገራውን ካልተገራው ጋር አያሰማራም። አንዳንዴማ ደብዳቤ እንኳ ሳይቀር በጋራ እንዲረቀቅና በያንዳንዷ ቃል ላይ “የጋራ” ስምምነት እንዲኖር እንፈልጋለን። የጽሕፈት ቤት ሠራተኞች መቅጠር፤ መገምገምና አስፈላጊ መስሎ ሲታየውም ያስተዳደር ርምጃ መውሰድ የአውራው የማይገሰስ ሥልጣን መሆኑን እንኳ የማናውቅ አለን። በኔ ይሁንባችሁ ወገኖቼ! - ያወቀውና የተማረው በእንዲህ ዓይነቱ ኋላቀር ማሕበር ውስጥ ጥዋ አይጠጣም፤ አባልም መሪም ለመሆን አይጣደፍም። ለዚህ ሳይሆን ይቀራል በአብዛኞቹ የኢትዮጵያ ድርጅቶች ውስጥ በባለሙያ ፋንታ የተገኘው የተነሰነሰበት? - ባገር ቤትም በዳያስፖራውም ማለቴ ነው። ከለብ-ለብ አመራር ልንጠብቅ የምንችለው የኋልዮሺ ጉዞና እጅግ የቀናን እንደሁ ደግሞ ለብ-ለብ ውጤትን ነው።

ለዚህ ነው ፕሬዚደንትም እንበለው ሊቀመንበር፤ ጠቅላይ ሚኒስትርም እንበለው የድር ዳኛ፤ አብሮት የሚሠራውን ካቢኔ ወይንም ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ የመምረጥ መብት ሊኖረው ይገባል ብዬ የተነሳሁት። ይህ ሀሳብ እንደ ኮሶ የሚመራቸው “የጋራ አመራር” ደቀመዛሙርት እንዳሉ አልጠራጠርም። የቱንም ያህል ይምረራቸው እንጅ ትምህርትንና ሙያን በስሜትና በወገናዊነት ልናካክሳቸው እንደማንችል መቀበል አለባቸው።

በፖለቲካም በሌላውም መስክ ችኮ አቋም መያዝ በጎ አይደለምና እመሀል ላይ አስታራቂ መፍትሔ አግኝቻለሁ። እንዲህ ይሁን - አሠራሩን እስክንለማመደው ድረስ አውራው 51% የሚሆነውን ካቢኔ ወይንም የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ የመምረጥ ሥልጣን ይኑረው። ሳንውልና ሳናድር በሁሉም ዓይነት ድርጅቶች ውስጥ የአውራውን ሥልጣን (executive power) ብናጠናከር በሁሉም ድርጅቶች ውስጥ ውጤታማነት ጣራ በጥሶ ይወጣል። ባለሙያውም ከየከተመበት ብቅ እያለ “እሺ ላገልግል” ይላል። የመጨረሻ ቤሳየን ሳልቆጥብ የምወራረድበት ጉዳይ ነው።

ታዲያ ይሄ አምባገነንነትን አይጋብዝም ወይ?
ፈጽሞ! አምባገነንነት በላያችን ላይ ይነግሥ ዘንድ የኛንም የማንንም ፈቃድ ጠይቆ አያውቅም። ለዚህ ከኢትዮጵያ የበለጠ ምስክር የለም። የምንመርጠው መሪ በኛና በርሱ መሀከል የተፈረመውን የራዕይና የፕሮግራም ሰነድ ተከትሎ ነው የሚሠራው። ይህን ለመከተሉ ማረጋገጫችን ደግሞ የተዘረጋው የቁጥጥርና የሪፖርት አቀራረብ ሥርዓት ነው። ለርሱ፤ ለሥራ አስፈጻሚውና ለጠቅላላ ጉባዔው አከፋፍለን የሰጠነው የሥራና የሥልጣን ድርሻ ነው። “አራተኛው መንግሥት” የሚባለው ነጻ ፕሬስም ፍቱን የማረጋገጫ መድሀኒታችን ነው።

የጋራ አመራር ጉዳይስ? የሰፊው ህዝብ ጉዳይስ?
ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ባለበት አገር ሕዝብ ያገሩ ባለቤትም ነው የሥልጣን ቁንጮም ነው። መሪዎቹን የመምረጥና የመሻር ዕድል ባላገኘበት ሁኔታ ግን ሰፊው ሕዝብ የማንም ባለቤት የምንም ቁንጮ አይደለም። ሀቁን እንነጋገር ካልን ሰፊው ሕዝብ ከሚገለጽባቸው መለያዎች መሀከል መሀይምነት፤ ድህነት፤ ረሀብተኝነትና ኋላቀርነት ጥቂቶቹ ናቸው። ለተፈጥሮና ለመንግሥት አደጋ መጋለጥም የዋዛ አበሳዎቹ አይደሉም። ይህ ዕውነታ ዝንተ-ዓለም አብሮን መኖሩን እያወቅን ነው ሌኒናውያን “ታሪክ ሠሪው ሰፊው ሕዝብ ነው!” እና “የጋራ አመራር!” የሚሏቸውን ሴሰኛ መፈክሮች ኳኩለው ብቅ ያሉት። ታዲያ ይኼ በሕዝብ ጀርባ ላይ ፊጥ ለማለት እንዲጠቅማቸው ያመጡት እንጅ ሰፊው ሕዝብ አንዲት ሀባ ስልጣን ያየበት ጉዳይ አይደለም። ለነገሩ ሕዝብ ያልተማረ ከሆነ እንዴት ነው በጋራ መርቶ ውጤት የሚያስገኘው? እንዴትስ ነው ታሪክ ሊሠራ የሚቻለው? እስቲ እነዚህን መፈክሮች የሙጥኝ ብለው የነበሩ ሶሻሊስት አገሮችን ጤንነት አጠያይቁ። ሁሉም እንደከሰሩና አንዳዶቹም ብትንትናቸው እንደወጣ ትሰማላችሁ።

ትዝ ይላችሁ እንደሁ በ“ሰፊው ሕዝብ” እና በ“ጋራ አመራር” ዘፈን መደንቆር የጀመርነው ከ 1966 በኋላ ነበር። ጥቂት የማይባለው የሕብረተሰብ ክፍል በይሉኝታም ባድርባይነትም ባለማወቅም ተገፋፍቶ “አዎን ሰፊው ሕዝብ!” “አዎን የጋራ አመራር!” አለ። በግለሰብ የመፍጠርና የተነሳሽነት ኃይል ላይ ቀዝቃዛ ውኃ ቸለስንበት። ግላዊነት “እርኩስ-ወአርዮስ” ተብሎ እንዲያቀረቅርና እንዲሰደድ ተገፋ። ከግለሰብ ጋር ተፈጥሮዋዊ ቁርኝት ያለቸው ፋይዳዎች - ዕውቀት፤ ምጥቀት፤ ተነሳሺነት፤ ፈጣሪነትና ምሁራዊነት የንኡስ ከበርቴው ፀያፍ ባህርዮች ተብለው ተኮነኑ። በጥራት ፋንታ ብዛት፤ በዕውቀት ፋንታ ታማኝነትና ጎጥ፤ በሙግት ፋንታ የጅምላ ስምምነት ባህላችን ሆኑ። ከዚያን ዘመን ጀምሮ ነው መቅኖ ያጣ ሕዝብ የሆንነው ወገኖቼ።

የግለስቡ ጉዳይስ?
ባንጻሩ ደግሞ “ግለሰብ የችሎታም የፈጠራም የታሪክም ብቸኛ መንስኤ ነው” የሚሉ አገሮች አድገውና ተመንድገው እናያለን። የግለሰብ መብት መከበር የቡድንና ያገር ነፃነት መከበርን ያረጋግጣል ብለው ስለተማማሉ ዘንድሮም የብልጽግናና የመረጋጋት ባለቤት ናቸው። የግል
ንብረትንና የግለሰብ የፈጠራ ሥራ መከበርን የሕገ-መንግሥታቸው አውታር በማድረግ የተፈጥሮ ሃብታቸውን ባግባቡ እየፈለፈሉ ላገርና ለወገን ጥቅም አውለዋል። የጫካ መጨፍጨፍና በሣት የመጋየት አሳዛኝ ዕጣ አልደረሰባቸውም። አፈራቸው ተሟጦና ለዛውን አጥቶ ሕዝባቸው ለስደትና ለምጽዋት አልተዳረገም። እነዚህ አገሮች የሁሉንም ግለሰብ እድገትና የዕውቀት አድማስ በመገንባት ላይ ብቻ የተወሰኑ ሳይሆኑ ከዜጎች ውስጥ ልዩ ችሎታና ተሰጥኦ ያላቸውን ወጣቶች (ያገር ንብረቶች) እየመረጡ ተሰጥኦዋቸውን በሚመጥን ልዩ የ “ኤሊት” ትምህርት ቤት አስገብተው ይንከባከቧቸዋል - የነገው መሪዎችና የፈጠራ ሰዎች ከነርሱ መሀል ነው የሚገኙትና!

ማርክሲስቶች “ኤሊትዝም”ን ላፋቸው እንደማይወዷት ሁላችንም እናውቃለን። ይሁንና ልጆቻቸው ኤሊትና ያገር መሪ ይሆኑ ዘንድ በልዩ ትምህርት ቤት ለማስተማር የሚሽቀዳደሙት እነርሱው ናቸው። ሀርቫርድን፤ ስታንፈርድንና ፕሪንስተንን ለልጆቻቸው ሲቃዡ ነው የሚያድሩት። ልጆቻቸው የነዚህ ኤሊት ዩኒቨርሲቲዎች ምሩቅ እንዲሆኑ የማይፈነቅሉት ድንጋይ የሚሳሱለት ገንዘብ የለም። ከዚህ የበለጠ ሂፖፕክራሲ አለ?።

የኛውን አገር ታሪክ መለስ ብለን ብናይ ግለሰቡን የመኮትኮትና የማነጽ አስፈላጊነት ግንዛቤ ያገኘው ገና ትናንት በ1896 ዓ/ም ነው። ዳግማዊ አፄ ምኒልክ የመጀመሪያውን የፈረንጅ ትምህርት ቤት ከግብጽ በመጡ ሁለት አስተማሪዎች ጀመሩና ይህን ጅምር በእጥፍ ድርብ ያፋጥኑት ገቡ (እኒህ መሪ 61 የዘመናዊነት መነሾ ፕሮጀክቶች እንደጀመሩ በብላቴን ጌታ መርስዔ ሀዘን መጽሐፍ ላይ አንብቤ ተደንቄአለሁ)። አፄ ኃይለሥላሴም በምኒልክ ጅምር ላይ ብዙ ገነቡ። ከመደበኛ ትምህርት ቤቶች በተጨማሪ እንደ ጀኔራል ዊንጌት፤ ቅዱስ ዮሴፍና ሳንፎርድን የመሳሰሉ የኤሊት ትምህርት ቤቶች ተቋቋሙ። ከነዚህ ትምህርት ቤቶች ነው ብዙዎቹ መሪዎቻችን የወጡት - ቢያጠፉም ቢያለሙም።

ቀጥሎ የመጡት መንግሥታት ግን ጀኔቲክ መሠረታቸው ማርክሲስት ስለሆነ የግለሰቡ ተነሳሽነትና የልማት ሞተርነት ሊዋጥላቸው አልቻለም። መሬት የግል መሆኑ፤ ፍትሀዊ የንግድና የኢንዱትሪ መስክ መፈጠሩ ገበሬውንና ነጋዴውን ከጭብጣችን እንዲያፈተልክ ያደርጋል ብለው ስልሚሰጉ ፖሊሲዎቻቸው ፀረ-ግለሰብና ፀረ ውድድር ናቸው።

እነዚህ መንግሥታት በምሁሩ ላይ ያደረሱት በደልና አገር ጥሎላቸው እንዲወጣ ያካሄዱት ሴራ አንደኛው አንጀት-አቁሳይ ታሪካችን ነው። ምሁሩ ለማይፈልገኝና ለሚያንጓጥጠኝ ሕብረተሰብ ምንተዳዬ አለና መድረኩን ላላዋቂዎች አስረክቦ ኑሮውን ማሳመር ተያያዘ - ተሰደደም። የሚወደስበትና የሚከበርበት ዓለም ሲያገኝ ያን አዲስ ዓለም ዓለሜ ብሎ ተቀበለ። ባሁኑ ጊዜ የሀበሻ ባለሙያ ከሁዋይት ሀውስ እስከ ኮንግሬስ፤ ከወል-ስትሪት እስከ ሜይን-ስትሪት ከአካዴሚያ እስከ አምራችነት ተነስንሶበታል። ለተማረው ሕዝብ ፍልሰት (brain drain) ጥሩ ተምሳሌት ከፈለጋችሁ ሩቅ መሄድ አያስፈልጋችሁም ለማለት ነው።

ታዲያ ከየት እንጀምር?
የምንጀምረውማ የተሳሳቱ አመለካከቶችን ከመቀየር ሊሆን ይገባል። ዴሞክራሲያዊ አሠራር ማለት “የጋራ አመራር” ማለት እንዳልሆነ እንቀበል። ሕብረተሰቡን ሳይሆን ግለሰቡን የመብትና የደሞክራሲ ሥርዓት መነሻም መድረሻም እናድርግ። ከስኬታማ ድርጅቶችና ሀገሮች በስተጀርባ ምንጊዜም አንፀባራቂ አውራዎች እንዳሉ አንዘንጋ። ባንድ ቤትና ባንድ ወቅት ሊኖር የሚችለው አንድ አውራ ብቻ ነውና ለመረጥነው አውራ በቂ ሥልጣን እንስጠው። እንንከባከበው። እንደንቦቹ ዙሪያውን ከበን ከሀሳየ-መሲሆች እንጠብቀው። እንዲፈታልን የምንጠይቀው ችግር ባንድ ጀንበር የሚሞከር አይደለምና ዋና መሥመሩን እስካልሳተ ድረስ ቢያዳልጠውም “አይዞህ አለንልህ!” እንበለው። አውራ የሌለው ምንም እንደማይኖረው እንወቅ!

ከሁለት ገጽ በላይ መጻፍ መንዛዛት ነው የሚለውን የራሴን ህግ ሰበርኩ ልበል?

kuchiye@gmail.com

Friday, July 31, 2009

"መድረክ እንዲህ ሊያናቁር ይገባል?"
በአንድነት ፓርቲ ዙሪያ የሚናፈሰው ውዝግብ ወርደ-ሰፊ ትምህርት ያዘለ ነው።

ትምህርቱ ለፓርቲው ሀላፊዎችና ደጋፊዎች ብቻ ባድራሻ የተላከ ሳይሆን ባገራቸው ፖለቲካ ሕይወት ውስጥ ሁነኛ ለውጥ እናመጣለን ብለው ለሚባዝኑ ሌሎች ፓርቲዎች ጭምር የሚተርፍ ይመስለኛል። ከዲስኩር ላድናችሁ ብዬ ነው እንጅ በዚህ ዙሪያ ብዙ የምለው ነበረኝ።

አንድነት ውስጥ አሁን ለተፈጠረው ውዝግብ መነሻ የሆነው “መድረክ ውስጥ እንግባ አንግባ? የምንገባስ ቢሆን ምን ዳር-ድንበር አስቀምጠን ቢሆን ይሻላል?” የሚለው ነው። ሌሎች በበራሪ ወረቀት የሚበተኑ ክሶችና ሀሜቶች በተረፈ-ፖለቲካና በማድቤት ወሬነት የሚመደቡ ናቸው።

መድረክ በመሠረቱ፤
ማንም ይጀምረው ማን መድረክ ያለፈው 18 ዓመት የተዛባ የፖለቲካ ጉዞ የፈጠረው ህዋስ ነው። ዘረ-መል (ጄኔቲክ) ምንጩ የተለዬ ነውና ቀደም ባለው ዘመን ከተፈጠሩ ስብስቦች ጋር በመሳ ሊታይ የሚገባው አይደለም።

መድረክ ከሚነቀፍባቸው ምክንያቶች፤
መድረክ ላይ ከሚሰነዘሩት ነቀፋዎች መሀከል ሁለቱንና ዋናዎቹን ላንሳ። (ሀ) መድረክን የመሠረቱት የብሔር ድርጅቶች ናቸው፤ (ለ) መድረክ ውስጥ ሕዝባዊና ድርጅታዊ መሠረት የሌላቸው ግለሰቦች ተሰንገዋልና እነሱን ከድርጅት ጋር መሳ ማዬትና መወጣጫ እርካብ ማቀበል ጅልነት ነው የሚሉት ናቸው።

የብሔር ድርጅቶች የሆኑ እንደሆንስ?
ኢትዮጵያ ውስጥ የብሔር ድርጅቶችና የብሔር ስሜት የለም ብሎ ራሱን የሚያታልል ካለ በዚህኛው ክፍለዘመን የሚኖር አይደለም። የቱን ያህል ዘግናኝ ቢሆንም ያገራችን የፖለቲካ እውነታ የብሔር ቅኝት አለው። የቅኝቱ ቁስል መንግሥት ባለፉት አሥራ ስምንት ዓመታት ባካሄደው የተሳሳተ ዘመቻ ይበልጥ እንደሰፋ መዘንጋትም ስህተት ላይ ይጥላል። አንድ የዩኒቨርሲቲ መምህር በቅርቡ የገጠመውን ግራ መጋባት ላጫውታችሁ። መምህሩ በንግሊዝኛ አነበነበና ተማሪዎቹ ገብቷቸውና አልገባቸው እንደሆነ ጠየቀ። ጭንቅላቶች ግራና ቀኝ ተወዛወዙ። ችግሩ የንግሊዘኛ ቋንቋ ችሎታ መሆን አለበት አለና ትምሕርቱን በብሔራዊ ቋንቋው ባማርኛ ደገመውና ተከትለውት እንደሁ ጠየቀ። ጥቂት የማይባለው ክፍል አሁንም እንዳልተከተለው ተረዳ።

የመምህሩን ልምድ ከብዙ አኳያ ልንተነትነው የምንችል ቢሆንም ከጽሁፌ ዓላማ አንፃር ዓይኑን ያፈጠጠብኝ ነገር አለ። የብሄርን ጉዳይ የምንፈታው አግልለነው ሳይሆን ወደጉያችን ጠጋ አድርገን መሆኑን ነው። ባዲስ አመለካከትና በብልህ ስሌት መልክ ካልያሳዝነው አገራችን የምታመራበት አቅጣጫ እጅጉን አያምረም። ለዚህ ነው መድረክ ውስጥ ገብቶ መሥራትም ሆነ በተወሰነ ደርጃ ተሻርኮ መንቀሳቀስ ትክክለኛ የፖለቲካ አማራጭ መስሎ የሚታዬኝ።

ሌላም ልንስተው የማይገባን የፖለቲካ ቁምነገር አለ። መድረክ ውስጥ ያሉት ድርጅቶችም ሆኑ ግለሰቦች ይህን ያህል በብሔርተኝነት ልክፍት የተጠመዱ አይመስሉኝም - ያለፈው አሥራ ስምንት ዓመት የፖለቲካ ተመክሯቸው ብሔርተኝነት ለነርሱም ለክልሎቻቸውም ለኢትዮጵያም ጠቀሜታ እንደሌለው አስገንዝቧቸዋል የሚል ታሳቢ ማድረግ ይቻላልና። ከዚህም በተጨማሪ የምንኖርበት ዓለም ወደ ግሎባላይዜሺን መጣደፉ ትምህርት ሳይሰጣቸው ያልፋል ማለት ብልህነታቸው ላይ መሳለቅ ይሆናል አልሞክረውም።

“ታዲያ ይህ ከሆነ ድርጅቶቻቸውን ለምን ሕብረብሔራዊ አያደርጉም?” የሚል ጥያቄ ቢነሳ አግባብነት አለው። ወገኖቼ! ሁሉም ፖለቲካ መንደራዊ ነው የሚለውን ብሂል መዘንጋት የለብንም። ፌደራላዊው የፖለቲካ አወቃቀርና የባጀቱ አፈሳስስ አጉራ-ተኮር እንደመሆኑ መጠን እነዚህ ፓርቲዎች ደጋፊዎቻቸውን የሚደርሱት በዚሁ መሥመር በመጓዝ ይመስለኛል። በፈረንጁ አገር እንደምናየው “ፌደራል መንግሥቱ ጋር ተሟግቼ መንገድ አሠራሁልህ...ወዘተ” ማለት የማይችል ፓርቲና ፖለቲከኛ ዳግም ላይመረጥ ነውና አንዳንድ ፖለቲከኞች ይህን መንገድ ቢከተሉና መራጮቸውን ለመቅረብ መንገዳችን ይህ ነው ቢሉ ልንደነቅም ልንነቅፋቸውም አይገባም። ለነገሩ ብንደነቅና ብንነቅፍ ምን ለውጥ እናመጣለን?

ትንሺ ላክልበት። ፓርቲዎች የብሔር ቅኝት ስላላቸው ብቻ ሁሉም የአንቅጽ 39 አሺቃባጭ ናቸው ማለት አይደለም። ሁሉም ክልላዊ አወቃቀርን ይደግፋሉ ማለት አይደለም። እንዲህ ዓይነት ፓርቲዎች ጋር ተቀራርቦ መሥራት ብሔራዊ አንድነትን ሊያስገኝ የሚችል አጀንዳ በመቅረጽ ረገድ በር ይከፍታል። ካልተነጋገሩና አልፎ አልፎም “የቢራ ዲፕሎማሲ” ካላካሄዱ መተማመን አይገኝም፤ ስውር ጥላቻንና ጥርጣሬን ማስወገድ አይቻልም። ዴሞክራሲያዊ ባህልን ለማዳበርም ሆነ ከውዝግብ ነፃ የሆነች ኢትዮጵያን ለመፍጠር አይቻልም። ያችን የምታውቋትን ጥቅስ አሁንም ልድገማትና “የፖለቲካ መነሻውም መድረሻውም ንግግር ነው” ።

የታዋቂ ግለሰቦች ጉዳይ!
በመድረኩ ውስጥ በግለሰብ ደረጃ ከተሰባሰቡት መሀከል የስዬ አብርሃና የነጋሶ ጊዳዳ ስም ጎልቶ ይነሳል። ገብሩ አሥራት በአረና ትግራይ ጃንጥላ ሥር ይሁን እንጅ ስሙ በጅጉ ሲነሳ እሰማለሁ። ቀልዱን እናቁምና ሁሉም ሰው እኩል አቅም፤ እኩል ተደማጭነት፤ እኩል ዕውቅት፤ እኩል ልምድ እኩል ዝናና ግርማ-ሞገሥ የለውም። ባንድ በኩል “ሴሌብሪቲ” የምንላቸው አሉ በሌላ በኩል ደግሞ “እኛ” አለን። ምን ማድረግ ይቻላል? ጨካኝ ዓለም ናት!

ሁሉም እኩል ቢሆንማ ኖሮ እኔና ኃይሌ ገብረሥላሴ እኩል ልንደመጥ ነው፤ አንኳኩተን እኩል በር ሊከፈትልን ነው፤ በምርጫ ተወዳድረን ኃይሌን የማሸንፍ ዕድል አለህ ልትሉኝ ነው። ህልም!

እነስዬ መድረክ ውስጥም ሆኑ ከመድረክ ውጭም ሆኑ የሴሌብሪቲ ደረጃቸው የሚያስገኝላቸው የፖለቲካ እሴት አለ። የሚያመጡት ዕውቀት ልምድና ተከታይ አለ። ያሳለፉት ሕይወትም ሆነ በቅርቡ ዘመን የደረሰባቸው ጉስቁልና ስለራሳቸውም ስላገራቸውም ብዙ ያስተማራቸው አለ። ስለሌሎቹ አላውቅም እንጅ ስዬ አብርሃ በቪ.ኦ.ኤ ደህና ነገር ሲናገር ትዝ ይለኛል። ሙሉ በሙሉ አንጀቴን ባያርሰውም ገብሩ አሥራት ዋሺንግተን መጥቶ በተናገረው ላይ ማለፊያ ጅምር አይቸበት ነበር። ሰዎችን የምናቀርበውና የምናርቀው ብትናንት ተግባራቸው ብቻ እየመዝንን ከሆነ በማናውቀው ንግድ ውስጥ ተሰማርተናል ማለት ነው። በጨዋ ቤት ፖለቲካ የወደፊት ጥቅም ማስከበሪያና የወዳጅ ክበብ ማስፊያ መሣሪያ ነው። ባለጌ ቤት ደግሞ የቂም በቀል መወጫና የዜሮ ድምር ሙግት መንኮራኩር ይሆናል። ምድባችን ከባለጌዎቹ ጎራ እንዳይሆን አምላክን መማለድ ተገቢ ነው።

ከመዝጋቴ በፊት የምመኛቸውን ጥቂት ነገሮች ላካፍላችሁ። በትናንቱ ላይ የማላዘንና የቁርሾ አባዜያችን እንዲለቀን እመኛለሁ። ከዴሞክራሲያዊ ውይይት በኋላ በተደረጉ ውሳኔዎች ተገዥ መሆንን እንድንማር ልቦናችንን ይከፍትልን ዘንድ እመኛለሁ። ግለሰቦችም፤ ድርጅቶችም፤ መንግሥታትም የሚያመሩት ወደ ዝቅተኛው የውጤታማነት ዕድሜያቸው መሆኑን ይቀበሉ ዘንድ እመኛለሁ።
kuchiye@gmail.com
ማሳሰቢያ። አስፈላጊ ባይሆንም ከመድረክም ከተጠቀሱት ግለሰቦችም ጋር እውቅና እንደሌለኝ እገልጻለሁ

Saturday, June 13, 2009


"የግልገል ግቤ-3 እና የላሟ ታሪክ!"

“ላም እሳት ወለደችና እንዳትልሰው እሳት እንዳትተው ልጇ ሆነ!”
ይህ አባባል ግለሰቦችም ማሕበረሰቦችም በኑሮ ሂደት ውስጥ አስጨናቂ ምርጫ እንዲያደርጉ የሚገደዱባቸው ሁኔታዎች መኖራቸውን የሚያመለክት ነው። እነዚህ ሁኔታዎች ብንዘጋቸው የማይዘጉ፤ መልስ እስካላገኙ ድረስ ከፊታችን ዞር የማይሉ ችኰ ነገሮች ናቸው። 3ኛው የግልገል ግቤ ፕሮጀክት እንዲህ ሆኖብን ስለከረመ እንደልማዴ የማውቀውንና የሚሰማኝን ላካፍላችሁ መረጥሁ፡
ስለ ግቤ
ግቤ የተንጣለለውን የኢትዮጵያ ደቡብ ምዕራብ ክፍል እያካለለ መልኩን አሳምሮ ወደ ኬንያ ዳርቻ የሚነጉድ ወንዝ ነው። ታዲያ እርባና ያለው ሕይዎት ሳይኖር ቆይቶ በደርጉ ዘመን ሠርተህ ብላ ተባለ። ከዚያ በኋላ ግቤ-1 እና ግቤ-2 የሚባሉ ፕሮጀችቶች ተከናውነው 400 ሜጋዋት ኤለክትሪክ ኃይል የማመንጨት አቅም ተገንብቷል። ግቤ-2 ፍጻሜ ያገኘው በኢሕአዴግ ዘመነ መንግሥት መሆኑን መግለጽ ተገቢ ይመስለኛል።
ግልገል ግቤ-3
የግልገል ግቤ-3 ፕሮጀክት ፅንሰ-ሀሳብ በአፍሪካ ውስጥ ተወዳዳሪ የሌለው የኤሌክትሪካ ኃይል ማመንጫ ጣቢያ በመገንባት ላይ የተመሠረተ ነው። እንደ ግብጹ “አስዋን” ዳም ለኢትዮጵያ የልማት ሞተር ሊሆን የሚችል ሃይል ለመፍጠር ማለት ነው። የፕሮጀክቱ ሥራ ሦስት ቢሊዮን ዶላር አካባቢ እንደሚፈጅ ሲገመት በሚጠናቀቅበት ጊዜ 1870 ሜጋዋት እሌክትሪሲቲ ያመነጫል። ለንጽጽር እንዲረዳችሁ ያሁኑ የኢትዮጵያ አቅም የሚያሳዝን 600 ሜጋዋት ብቻ ነው። ለዚህ ነው አገራችን በኩራዝ የምትኖረው። ለዚህም ነው ዋና ከተማዋ አዲስ አበባ ሳትቀር በሳምንት ለሦስት ቀን የኮረንቲ ራሽን የተዳረገችው። ግልገል ግቤ-3 ካገሪችን ተርፎ ለጎረቤት አገሮችም የመሸጥ አቅም እንደሚያስገኝ ይነገራል።

ታዲያ ከባድ ችግር ተፈጥሮላችኋል! የግቤ ወንዝ ውልደቱም ጉልምስናውም እርጅናውም ኢትዮጵያ ውስጥ ሆኖ እያለ ኢትዮጵያ በዚህ ወንዝ እንዳሻት ልትጠቀም አትችልም የሚሉ ጉዶች ፈልተዋል። “በገዛ ዳቦዬ ልብ-ልቡን አጣሁት” ዓይነት ነገር መሆኑ ነው። እንዳሸን መፍላት ብቻ ሳይሆን ለዚህ ፕሮጀክት የሚያስፈልገውን ገንዘብ ኢትዮጵያ እናዳትበደር እያከላከሉም ነው። ግብጽና ሱዳን በግልገል ግቤ-3 ታላቅነት ተደናግጠዋል (ኬንያም እንዲሁ)። ኤንቫይሮንሜንታሊስቶች የሚያናፍሱት አጀንዳና የሚያፍሱት ዶላር በማግኘታቸው ፈንድቀዋል፤ እኛ ደግሞ በነገሩ ግራ ተጋብተን የላሟን ዓይነት ሆነናል። ሦስቱንም በየተራ ላስረዳ።
ግብጽና ሱዳን
በምናውቀው ምክንያት ግብጽና ሱዳን የኢትዮጵያን መጎልበት አይፈልጉም። ጠንካራ ኢትዮጵያ ማለት ካባይ ወንዝ ላይ ድርሻዋን የምትጠይቅ ኢትዮጵያ ትሆንባቸዋለችና ወደሠላምና ወደብልጽግና የሚወስዳትን ጎዳናዎች ሁሉ በፈንጅ ከማጠር አይቦዝኑም። ያባይ ወንዝ መነሻውን እስካልለወጠ ድረስ ከነዚህ አገሮች ጋር ያለን ባላንጣነት ይቀጥላል። ይህ ያጉል ተጠራጣሪ አመለካከት ሳይሆን (ኮንስፒረሲ ቲዎሪስት አለመሆኔን ታውቃላችሁና) ግብጦችም ደርቡሾችም በሰነዘሩብን ተደጋጋሚ ጦርነትና ባሴሩብን ሴራ መጎዳታችን በታሪክ የተመሰከረ ነው።

ግብጾች የግቤ-3ን ፕሮጀክት ለማሰናከል ጥድፊያ ላይ ናቸው ይባላል። በውሀ አጠቃቀም ሕግ የተራቀቁ ናቸው የሚባልልላቸው ድርጅቶቻቸው፤ ምሁራኖቻቸውና የዲፕሎማቲክ ጡንቻቸው የግቤ-3 ፕሮጀክትን “ጐጅነት” በማስተጋባት ላይ ይገኛሉ። የውሮፓ ኢንቬትመንት ባንክ፤ ዓለም ባንክና አሁን ደግሞ ያፍሪካ ልማት ባንክ ለግቤ-3 ገንዘብ እንዳያበድሩ ከኤንቫይሮንሜንታሊስቶች ጀርባ ሆነው ዘመቻ እያካሄዱ ነው። ዘመዶቼ! ግብጽ በዓለም አቀፍ መድረኮች ያላት ተደማጭነት ቀላል እንዳልሆነ ምንጊዜም መዘንጋት የለብንም ።
የኤንቫይሮሜንታሊስቶች ጫጫታ!
ኤንቫይሮንሜንታሊስቶች ጥሩ ጎን ያላቸውን ያህል አንዳንዱ ባሕርያቸው አስቂኝ ነው። ግቤ-3ን በሚመለከት ግድቡ ከተሠራ ያካባቢው ነዋሪ ሕዝብ ኑሮ ይበላሻል ይላሉ። ኤኮሎጅ ይናጋል ይላሉ። እስኪ በፈጠራችሁ የትኛው የኑሮ ዓይነት ነው የሚበላሸው? መለ-መላ የሚኬድበት? ከንፈር የሚተለተልበት? ረሀብ፤ ድንቁርና፤ መሀይምነትና በሽታ የነገሱበት? ወይንስ ደግሞ ጥቂት ቱሪስቶች የፎቶ አጋጣሚ አግኝተው የበላይነት ስሜት የሚገዙበት?

ቢማሮ አምደልካር የተባለው ከጋንዲ የሚተካከል የህንድ አባት “ምሁሩ በገጠሩ ላይ ያለው ፍቅር ማለቂያ የሌለው ብቻ ሳይሆን አሳፋሪም ነው” ይልና “በሀቅ ከተመለከትነው ገጠሩ የድንቁርናና የበሽታ ጉሮኖ፤ የጎሰኝነት ኩሬ፤ የጠባብ አመለካከት ጎተራ ነው” ብሎ ይደመድማል። እኔ ደግሞ “ኋላቀር የኑሮ ዘይቤዎችን አላግባብ የሚያወድሱና ከዘመናችን የኑሮ ዘይቤ ጋር መሳ-ለመሳ ለማስቀመጥ የሚሞክሩ እነርሱ ጤነኞች አይደሉም ደህና ሀኪም ያስፈልጋቸዋል።” እላለሁ

ስለ ኤንቫይሮንሜንት ካነሳን ዘንድ የዓለም ሥልጣኔ አስቸጋሪና አስቸጋሪ ያልሆኑ ምርጫዎችን እያደረገ ነው እዚህ የደረሰው። አሜሪካ፤ አውሮፓና እስያ የተገነቡት ኤንቫይሮንሜንት ሳይቀየር አይደለም። ሁቨር፤ አስዋን፤ ሜርዌ፤ ያንግቴዝና ሌሎችም እርቆ መሳፍርት የሌላቸው ግድቦችና ልማቶች ሲከናወኑ ሰፋፊ መሬቶች በውሀ መጥለቅልቅ ነበረባቸው። የታሪክ ቅርሶችና ማዕድኖች ሳይቀሩ በሐይቆቹ ሥር ማቅረታቸው አማራጭ አልነበረውም። እነዚህ ታላላቅ ፕሮጀክቶች የዜጎችን የኑሮ ደረጃ በመለወጥ በኩል ያደረጉት አስተዋጽኦ ግዙፍ ነውና ክርክር እንኳ አይጠይቅም።

ልብ በሉ። የመኖርና ያለመኖር ጥያቄ በተነሳ ቁጥር ኤንቫይሮንሜንት ሁለተኛ ደረጃ ትኩረት ነው የሚያገኘው። በኔ ግምት ግቤ-3 ለኢትዮጵያ የመኖርና ያለመኖር ጥያቄ ነው። የሚያወላዳ ሀብት ለሌላትና በመጨረሻው የድህነት እርከን ላይ ለምትገኝ ኢትዮጵያ “ኤሌክትሪፊኬሽን” አማራጭ የሌለው የልማት ርምጃ ስለሆነ የትኛውም መንግሥት ሥልጣን ላይ ቢሆን ወደኋላ የሚባልበት ጉዳይ አይሆንም። የምናዘገዬው ጉዳይም አይደለም።
ታዲያ ምኑ ነው እኛን ግራ ያጋባን?
እኛን ግራ ያጋባን የኢሕአዴግ ጉዳይ ነው። ኢሕአዴግ በላሟ ልጅ ይመሰላል። ከጎኑ እንዳንቆምና ያለም ባንኮችን ሎቢ እንዳናደርግ የኢሕአዴግ ደጋፊ ልንመስል ነው። አይተን እንዳላየን እንዳንሆን ደግሞ ያገር ህልውና ጥያቄ አለበት። የቅርብ ዘመን ታሪካችንን እንኳን መለስ ብለን ብናይ ይህ ትውልድ ሁለት ተመሳሳይ ፈተናዎች ገጥመውት እንደነበር ማስታወስ እንችላለን። አንደኛው በ1969ኙ የሶማሌ ጦርነት ጊዜ ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ በኤርትራው ጦርነት ጊዜ ነበር። ሕዝባችን ያደረገው ምርጫ ከመንግሥቶቹ ጋር የነበረውን ቅራኔ ለጊዜውውም ቢሆን ወደጎን አርጎ ባገር ጉዳይ ላይ ተረባረበ። የግቤን ጉዳይ በዚያ ትይዩ የማስቀምጥበት ምክንያት አለኝ። ይኸውም የታሪክ ጠባሳና መጥፎ “ፕሬሲደንስ” ፈጥረን እንዳናልፍ ከመስጋት ነው።
የምን ፕሪሲደንስ ነው ደሞ?
ኢትዮጵያ በአባይ ውሀ ሳትጠቀም ለዘመናት ኖራለች። በአንፃሩ ደግሞ የሱዳንና የግብጽ ሕልውና የተመሠረተው በዚህ ወንዝ ላይ ነው። ኢትዮጵያ በአባይ ወንዝ ላይ የረባ የባለቤትነት መብትና ያጠቃቀም ፕረሲደንስ አልመሠረተችምና በወንዙ ላይ ሁነኛ ፕሮጀክት እጀምራለሁ ብትል የሱዳንንና የግብጽን ስምምነት ማግኘት ያስፈልጋታል። ያለም ሕግ እነሱን ይደግፋልና። ህልውናቸውን ለማስጠበቅ በኢትዮጵያ ላይ ጦርነት እስከማወጅ የሚያደርስ መብት ይኖራቸዋል። ሰዶ ማሳደድ ይሏችኋል ይሄ ነው።

አባይ ጥሩ አስተምሮናልና ግቤ ወንዝን ሰደን ማሳደድ አንችልም። ስለሆነም ያለንን የባለቤትነትና የመብት ጥያቄ በማያወላዳ ሁኔታ የማረጋገጡ ጉዳይ ወሳኝ ነው። ለኤንቫይሮንሜንታሊስቶችና ለአሳዳሪዎቻቸው ግፊት ከተፈታንና መብታችንን አሳልፈን ከሰጠን ሀገራችን ሁነኛ ልማት ማካሄድ የምትችልበትን የመጨረሻ ዕድል አባከነች ማለት ይሆናል። ከመጨረሻው የድህነት እርከን ፈቅ ለማለት እንኳ ላንችል ነው ማለት ነው። ዛሬም ጎጅ ፕረሲደንስ ላለመክፈት እንጠንቀቅ። የውጭ ባላንጣዎቻችን ማለፍ የማይችሉትን መሥመር ዛሬውኑ እናስምር።

ይህን ስናደርግ ዴሞክራሲንና የሕግ የበላይነትን በሀገራችን ለማስፈን ከኢሕአዴግ ጋር የምናደርገውን ትግል እየቀጠልን መሆኑ አነጋጋሪ እንኳ አይደለም። በኔ ግምት ሁለቱ እንቅስቃሴዎች አይጻረሩም። እንዴትና በምን መልኩ የሚለውን ልንወያይበት እንችላለን። የቱን ያህል አስጨናቂ ቢመስልም በጉዳዩ ላይ ጨዋ ውይይት ማድረግን ልንሸሸው አንችልም።
ፀጋዬ ሙሉሸዋ በዚህ ጉዳይ ላይ ጥሩ ጽፏልና አንብቡለት። http://www.ethiomedia.com/adroit/2431.html

kuchiye@gmail.com

Friday, June 05, 2009


"ይድረስ ለውድ ብርቱካን!"
ቃሊቲ እስር ቤት - አዲስ አበባ


“ታውቅ ይሆን?” እያልኩ አወጣና አወርዳለሁ። “የስንቱን ህሊና እንደነካች ታውቀው ይሆን?” እላለሁ።

የሰሞኗ ጀንበር የምትጠልቀው የሁለተኛ ልጄን መወለድ ሳሰላስል ነው። ታዲያ ከየት መጣ የማልለው ጭንቀት በድንገት ይወረኛል። ጭንቀቱ ስለልጆቼ እንጅ ስለኔ እንዳይመስልሺ። “እኔ የማውቃትንና ያደግኩባትን ኢትዮጵያ፤ በማይነጥፍ የፍቅር እስተንፋስ ኮትኩቶ ያሳደገኝን ቀዬ፤ ይሰማኝ የነበረውን ልበ-ሙሉነትና ብሩህ ተስፋ፤ በበቂ የማይወሳለትን የወገኔን ጨዋነትና የመቻቻል ባህል.....ልጆቼ የነዚህ ቅርሶች ባለቤት የመሆን ዕድል ይገጥማቸው ይሆን?” እያልኩ ነው የምጨነቀው።

ከአጉል ውዳሴ አይቆጠርብኝ እንጅ ምንኛ ስሜቴን እንደነካሺው ላሳውቅሺ እፈልጋለሁ። ከቃሊቲ እሥር ቤት በጥር ወር 2006 ገደማ የፃፍሺውን ደብዳቤና አሁን በታህሳስ 2008 እንደገና ወደ እስር ሊወረውሩሺ ሲዘጋጁ “ቃሌ!” በሚል ርዕስ ለሕዝብሺ የሰጠሺውን ምስክርነት ደጋግሜ አነባቸውና ስሜቴ ሲታደስ አየዋለሁ። አልፎ አልፎም ይሁን እንጂ ዓለማችን ጠንካራ መንፈስ ኖሯቸው የተስፋ ራዕይ በሚናኙ ሰዎች መታደሏን አስታውሼ እጽናናለሁ። ስለጠንካራ መንፈስሺና ስለ ተስፋ ሰጭነትሺ ከልብ አመሰግንሻለሁ።

ውድ ብርቱካን!
ቀይ ሺብርና ነጭ ሺብር የወላጆቻችንን ቅስም ሰብረው ለስደት ኑሮ ዳረጓቸው። አሁን ደግሞ ሕዝባችንን በጎሳና በሀይማኖት ለመከፋፈል የሚረጨው መርዝ የምንተነፍሰውን አየር እየበከለው ይገኛል። ለዚህ ነው ያሁኑም ትውልድ ስደተኛ እየሆነ የመጣው። አየሺ! ያምባገነኖች ተግባር ርኩስ ነው የሚባለው ተቀናቃኞቻቸውን በመፍጀታቸውና በማፈናቸው ብቻ አይደለም። ከዚያ ባላነሰ የሚጎዱን መጭው ትውልድ የተስፋ ባለቤት እንዳይሆን በሚያካሂዱት የሥነ-ልቦና ጦርነት ነው።

“ዴሞክራሲንና በሥነ-ምግባር የታነጹ መሪዎችን መሻት መብታችን ነው!” ማለትን ካቆምን፤ ተፈጥሯዊና ሕገመንግሥታዊ መብታችንን ከጃችን ሊመነጭቁ ሲመጡ “ወግዱ አናስነካም!” ማለትን ካልለመድን ያኔ ነው የሺንፈትም ሺንፈት የሚሆንብን። ለዚህም ነው ያንች “ወግዱ!” እና “መብቴን አላስነካም!” ለሁላችን ምሣሌ የሆነው።

ኢሕአዴግ ሊያሳምነን የሚጥረው ኢትዮጵያ ከዚህ የተሻለች መሆን እንደማትችል ነው። የተሻለ ዴሞክራሲ፤ የተሻለ ፍትህ፤ የተሻለ አስተዳደር ሊኖር እንደማይችል። የሚመራንን ፓርቲ ስንመርጥና ለዴሞክራሲ ዝግጁ መሆናችንን ስናስመሰክር የዴሞክራሲን ጎዳና ፈጽሞ ይዘጋዋል። የጎሣ ፖለቲካ እንዳላመቸው ሲረዳ የሀይማኖትና ሌሎች ልዩነቶችን ያሰፋፋል። ይሁን እንጅ ኢሕአዴግ ራሱ የማይስተው አንድ ዕውነታ አለ። የሚቆጣጠራቸውን የእርሻ መሬቶች፤ የፋይናስና የንግድ ድርጅቶች፤ ትልቅ ደመወዝ ከፋይነቱንና ወታደራዊ ኃይሉን የጭቆናና የማባበያ መሣሪያ ባያደርግ ኖሮ ላንድ ጀንበር ሥልጣን ላይ እንደማይቆይ ያውቃል። በሕዝባዊ ፍቅር ተከልሎ በሁለት እግሩ የቆመ መንግሥት እንዳልሆነ ያውቀዋል። ባለሥልጣኑም ካድሬውም ሠራዊቱም በውስጣቸው ይህን ያውቃሉ።

ውድ ብርቱካን!
ኢሕአዴግ በጥፋት ጎዳና መጓዙን አቁሞ የሕዝብና ለሕዝብ የሚያደርገውን ጎዳና ቢመርጥ የሁላችንም ምኞት ነው። የኛው መንገድ የአንድነት የዴሞክራሲ የመብት የዕኩልነትና የዕርቅ ስለሆነ በፍቅርና በተስፋ ተሞልቷል። ለሰው ልጅ ከተስፋ የሚበልጥ ቁምነገር የለምና ተስፋን ምርኩዛችን እስካደረግን የነገው ሕይወታችን ከዛሬውው የተሻለ እንደሚሆን አንጠራጠርም።

የተስፋን የአንድነትንና የጥንካሬን ካባ ስላላብሺን ለውለታሺ መጠን የለውም። በቅርቡ ከእስር ወጥተሺ የጀመርሺውን ያዲስ ትውልድ አደራ እንድትወጭ፤ ያዲሲቷን ኢትዮጵያ ጉዞ አብረሺን እንድትጓዥ እንጸልያለን። የኔዎቹ ሁለቱ እንዲሁም ያንችዋ “ሄሌ” እጅግ መልካም የሆነች ኢትዮጵያ ትኖራቸዋለች።
kuchiye@gmail.com

Friday, May 29, 2009

"መሬት የመቸብቸቡ ጉዳይ! "

ችስታ የመታቸው አገሮች ሰፋፊ መሬታቸውን ለውጭ መንግሥታት በገፍ የመቸብቸባቸው ፈሊጥ በዓለም መድረኮች አነጋጋሪ ሆኗል። በኛው አካባቢም ብዙ ንትርክና ቁጣ እንደጫረ ተረዳሁና ጉዳዩን መመርመር ጀመርኩ። ሳያጣሩ ወሬ ሳያነቡ መምሬ መሆን አጉል ነውና በመጠኑም ቢሆን አንብቤ ያገኘሁትን ላካፍላችሁ።

ሳኡዲ፤ ኤሚሬት፤ ኳታር፤ ኩዌት፤ ግብጽ፤ ሊቢያ፤ ቻይና፤ ደቡብ ኰርያና የመሳሰሉትን አገሮች የእህል ዋጋ ሰማይ እየነካ መሄዱ የምግብ ሴኪውሪቲ እያሳጣቸው ነው። ባዮ-ፊውል ለማውጣት ሲሉ ፈረንጆቹ ለዓለም ገበያ የሚቀርበውን እህል መቀነሳቸውም ሼኮቹን ያስደነቀ አይመሰለኝም።

ይሁን እንጅ እንደ ሳኡዲ ያሉትን የናጠጡ ሀብታሞች ያሳሰባቸው ከላይ የተጠቀሰው ብቻ አይደለም። ሳውዲዎች በማይታመን ዋጋም ቢሆን እህል በበረሀ ውስጥ ያመርታሉ። የሳውዲ እርሻዎች ለብሔራዊ ኩራት ምንጭ ሆነው ይቆዩ እንጅ በከርሰ-ምድር ያለውን የውሀ ክምችት ክፉኛ በሟሟጠጥና አካባቢን በመበከል ረገድ ጋውፋህ (የተሲያት እንቅልፍ) የሚነሱ ዓይነት ሆነውባቸዋል። በኢትዮጵያው ኮንትራት የተመረተው ሩዝ በታላቅ ሥነ-ሥርዓት ታጅቦ ለሳኡዲው ንጉሥ ሲቀርብላቸው በፈገግታ የተሞሉት ያለምክንያት አልነበረም። ለምን አይሞሉ? ርስቱ ከወንዝ ባሻገር፤ የተገኘው በነፃ፤ የኤክስፖርት ታክስ አይከፈልበት፤ የሚሟጠጠው የሌላ አገር ውሀ፤ የሚመረዘው የሌላ አገር መሬት።

ከወዲሁ ላስጠንቅቃችሁና የውጭ ኢንቬስትመንት ለዕድገት እጅግ አስፈላጊ ግብአት ነው ከሚሉት ወገን ነኝ። ስለሆነም የመሬቱን ኮንትራት የማየው በ “ጠርጥር” መነጽር ተጋርጄ አይደለም። ለዚህም ነው አዲስ ዓይነት “የጅ-አዙር ቅኝ አገዛዝ” ወዘተ የሚለውን ዝባዝንኬ ክርክር የማልስማማበት። አገርም ግለሰብም የሚፈርሙትን ውል በቅጡ ካሰቡበትና ጥቅማቸውን ለማስከበር በቂ ጥንቃቄ ካደረጉ የጅ-አዙርም የሌላም ዓይነት ቅኝ አገዛዝ ሰለባ አይሆኑም። ደ!

በነገራችን ላይ በመሬት ችብቸባው ንግድ የተሰማራችው ኢትዮጵያ ብቻ ሳትሆን ሱዳን፤ ዛምቢያ፤ ታንዛኒያ፤ ኮንጐ፤ ሞዛምቢክ፤ ካምቦዲያ፤ ዩክሬን፤ ሰርቢያና የመሳሰሉት ጭምር ናቸው። ሩስያ አውስትራሊያና ብራዚልን የምያካክሉ የዳጎሰ ኤኮኖሚ ያላቸው ሳይቀሩ ከነሳኡዲ ጋር ሽር ጉድ እያሉ ነውና ያዲሱ ዓለም የኢንቬስትመንት ቄንጥ ይህ እንደሆነ እንወቅ። በዚህ ረገድ ኢትዮጵያም ድርሻዋን ለማግኘት ብትሯሯጥ ልንገረም አይገባም - ኢንቬስትመንት ካፒታል እንደሷ የሚያስፈልገው አገር የለምና።

ታዲያ ችግሩ የት ላይ ነው? በጣም ጥሩ ጥያቄ። ችግሩ ያለው መሬት የሚቸበችቡት አገሮች ግልጽነትንና ተጠያቂነትን በማያውቁ መንግሥታት ሥር የሚተዳደሩ መሆናቸው፤ አኮናታሪዎቹም ተኮናታሪዎቹም ሙስናን ባህል ያደረጉ መሆናቸው፤ የውል ዝርዝሩ ድብቅ መሆኑ፤ ኢንቬስተሩ ያመረተውን እህል ሙልጭ አድርጎ ወዳገሩ ወይንም ወደ ዓለም ገበያ የመውሰድ መብት እንዲኖረው መደረጉ ይገኙበታል። ይህ ብቻ አይደለም! ውሉ ስለከባቢ ዓየር መበከል፤ ስለብሔራዊ የውሀ ቋት መሟጠጥ፤ ስለነዋሪው ሕዝብ መፈናቀል ከመጨነቅ ይልቅ የኢንቬስተሩንና የውል ሰጨዎችን ኪስ በማሟሸት ላይ የተጣደፈ ነው የሚሉም ይበዛሉ። እኔ ማነኝና ነው አዋቂዎች የሚሉትን ላስተባብል የምሞክረው? እንቀጥል…

ከኢንቬስተሮቹስ ምን ይጠበቃል? ይህም ሌላ ጥሩ ጥያቄ ነው። ኢትዮጵያን በሚመለከት ከሳውዲ ኢንቬተሮች ጋር የተፈረመው ውል በምስጢር ስለተያዘ ምን ዝርዝር እንዳለው አይታወቅም። ይህ ነው እንግዲህ ግልጽ ያለመሆን ጣጣ። ኢንቬስተሮቹ የሚሉት የሥራ ዕድል፤ ምርጥ ዘር፤ አዲስ ቴክኖሎጅ፤ ዘመናዊ ማኔጅመንት፤ ትምህርት ቤቶች፤ ክሊኒኮች፤ ይዘን እንመጣለን ነው። ከተጠቀሱት ጥቅሞች ኢትዮጵያ ምን ያህሉን እንዳገኘች የሚያውቅ ሰው ካለ ይንገረንና የትኞቹ ዕውንት የትኞቹ ደግሞ ባዶ ተስፋ እንደሆኑ መለየት እንችላለን።

እስከዚያው ድረስ ግን ከሌሎች አገሮች ያገኘነውን ተመክሮ መሠረት አድርገን መወያየቱ ክፋት የለውም። ሌሎች አገሮች ውስጥ የተቋቋሙ የ “መንግሥት-ለመንግሥት” ወይንም የ “መንግሥት-ግል” የርሻ ኮንትራቶች ብዙ ፋይዳ አሳይተው እንደማያውቁ ያለም ታሪክ ይመሰክራል። ለነገሩ መንግሥት የሚይዘው ነገር የት ቦታ ነው ፈይዶ የሚያውቀው? ባንጻሩ ደግሞ የውጭ የግል ኢንቬስተሮች ካገሬው የግል ኢንቬስተሮች ጋር የሚጀምሯቸው ፕሮጀክቶች ብዙ ውጤት ታይቶባቸዋል። የኢትዮጵያ መንግሥት ሁሉን በጄ ከሚለው አባዜ እስካልተላቀቀ ድረስ የሳውዲውም ሌሎችም ፕሮጀችቶች ብዙ ዕድሜ እንደማይኖራቸው ከወዲሁ መመስከር ይቻላል።

ወደማጠቃለሉ ላምራ። ከላይ እንደጠቀስኩት የውጭ ባለካፒታሎች በደሀ አገሮች ውስጥ የእርሻ ሥራ ለማስፋፋት መሺቀዳደማቸው የዘመናችን ክስተት ነውና ልናቆመውም ልንሸሸውም አይገባም። ጥያቄው ኢንቬስተሮች ይግቡና አይግቡ ከሚለው ላይ አይደለም - ይህ ብዙ አያከራክርምና። ፍሬ ነገሩ ያለው እንዲህ ያለው ውል ሁለቱንም ወገን ሚዛናዊ በሆነ መንገድ የሚጠቅም ነው አይደለም ከሚለው ላይ ነው። ለዚህ ደግሞ የግልጽነት ጥያቄ ወሳኝ ይሆናል። ያገሬው ኢንቬስተር ተሳታፊነት ወሳኝ ይሆናል። ብሔራዊ ጥቅም የማስከበሩ ጉዳይ ወሳኝ ይሆናል። ተገቢው የኤንቫይሮንሜንት ሕግ መውጣቱና ማስከበሪያ መሣሪያዎቹም መደራጀታቸው ወሳኝ ይሆናል። የውጭው ካፒታል የሚንቀሳቀስበት የሕግ ዳር-ድንበር መከለሉ ወሳኝ ይሆናል። ስለሚፈናቀለው ገበሬና በከብት-ርቢ ስለሚተዳደረው ሕዝባችን እጣ-ፈንታ በቅጡ ማሰብ ወሳኝ ይሆናል።

ከሁሉም በላይ ደግሞ የዴሞክራሲ የመልካም አስተዳደርና የሕግ የበላይነት መስፈንን የግድ ይላል።

እነዚህ ሳይሆኑ ቀርተው የመንግሥት ቢሮክራቶች በግብታዊነትም በሌላ ተነሳሺነትም የሚያደርጉት ውሳኔና የሚፈራረሙት ውል የሚያስገኘው ጥፋትና ኪሣራ ነው። በቆቃ ሀይቅና በወንዞቻችን ላይ እየደረሰ ያለው ሁኔታ አሳዝኖን ከሆነ ይኸኛው ደግሞ ከትውልድ ወደትውልድ የሚተላልፍ የሀዘንም ሀዘን ይሆናል። የኢትዮጵያ ሕዝብ የውሎቹን ዝርዝር የማወቅ መብት አለው።

Kuchiye@gmail.com

----------
(እንግሊዝ ለሚቀናችሁ፡ “The Economist” May 23, 2009 አንብቡ። ብዙውን ያገኘሁት ከዚያ ነው)

Tuesday, May 05, 2009

"ኤይድስ በዳያስፖራው ኢትዮጵያዊ መንደር! "

ከዲሲ ሕዝብ 3% ያህሉ በኤይድስ በሽታ የተበከለ ነው። አንዳንዶች ማዕከላዊ ቁጥሩ ከዚህም እጥፍ ይሆናል ይላሉ። የጥቁሩን ሕብረተሰብ ብቻ ነጥለን ብንወሰድ 7% የሚሆነው የበሽታው ሰለባ ሆኗል።

ዛሬ የኤይድስ አክቲቢስት መስየ የቀረብሁት በበቂ ምክንያት ነው። በውጭ ከሰፈረው ኢትዮጵያዊ ወገናችን አብዛኛው መቶኛ ዋሽንግተን ዲሲ አካባቢ የሚኖር ስለሆነ ሁኔታው በግለሰብም፤ በማህበረሰብም ደረጃ ሊያሳስበን ይገባል። ከዚያም አልፎ ሊያስደነግጠን ይገባል። በጤናው መስክ የተሰማራ ወዳጄ በኢትዮጵያዊው ህብረተሰብ ውስጥ የኤይድስ ቁጥር በከፍተኛ ደረጃ እየጨመረ መምጣቱን ያጫወተኝ አይቼበት ከማላውቀው ትከዜ ጋር ነበር። በሱ ግምት የሀበሻው ሕብረተሰብ ተነጥሎ ቢጠና የተለከፈው ወገን ከ 10% እንደማያንስ አልተጠራጠረም። በተለይ ወጣቱ አካባቢ።

የዋሺንግተን ዲሲው ኤች አይቪ ኤይድስ ሁኔታ የወረርሽኝ ያህል አስደንጋጭ ደረጃ ላይ ስለደረሰ የመንግሥትንና የሕብረተሰቡን ትኩረት እያገኘ ነው። በሀበሻው መንደር ግን ግንዛቤውም ድንጋጤውም ጎልቶ አለመታየቱ እጅግ ያሳስባል!

ከወዳጄ ጋር ጭንቅላቶቻችንን ለጥቂት ጊዜ አጋጨንና የሚከተሉትን ቁምነገሮች ልናካፍላችሁ ተስማማን። በዚህ ዓለም ላይ ባለማወቅ ከምናደርጋቸው ስህተቶች እያወቅን የምንፈጽማቸው በጅጉ እንደሚበዙ የሰው ልጅ ታሪክ የመሰከረው ነውና የምናውቀውንም እንደገና መማማራችን አስፈላጊ ነው። ከተወሰነ ፍጥነት በላይ መንዳት ቅጣት እንደሚያስከትል እያወቅን ቲኬት የተከናነብን ስንቶች ነን? በኤይድስ ላይ የሚደረግ ውይይትንም በዚሁ መልኩ እንየው።

ኤይድስ መሠሪና ፈሪ ጠላት ነው። አዕምሮአችን በመጠጥ ወይንም በፍትዎት የተዘናጋበትን ሰዓትና አሳቻ ቦታ መርጦ ያጠቃል። ስለሆነም መጠጥ መጠጣት ካለብን ልካችንን እንወቅ።
ፍትዎት እንደታንጎ ሁለት ደናሺ ይጠይቃል። እኔ ጥንቁቅ ነኝና ጓደኛየም ትንቁቅ ትሆናለች ማለት አይቻልም። ያልተጋቡ ጓደኞች ኮንዶም መጠቀምን ከጀግንነትና ከስልጡንነት ሊቆጥሩት ይገባል። የኮንዶም ፍትዎት ያለኮንዶም ከሚደረግ ፍትዎት እኩል እንደሚጥም አዕምሮአችን ይቀበለው። ባለትዳሮችም ቢሆኑ አንደኛው ወገን በምንም መነሻ ይሁን ስጋት አደረብኝ ካለ “እንመርመር ቀፈፈኝ” ማለትን መፍራት የለበትም። ሌላው ወገንም እንዴት ተደፈርኩ! ብሎ አካኪ ዘራፍ አይበል። ምርመራው ለሁለቱም ይበጃል፤ መተማመንና ፍቅርን ያጠናክራል።
ሀገር ቤትን እንፍራ። አዎን ያገር ቤት ጉብኝትን መፍራት ነው። ያገራችን ሴቶች ቀድሞውንም ቆንጆ መሆናቸው አንሶ አሁን ደግሞ ይበልጡን እያማሩና እያማለሉ ሄደዋል። ኢትዮጵያ በዓለም ከፍተኛ የኤይድስ ተሸካሚ ከሚባሉት አገሮች አንዷ መሆኗን ስንገነዘብ፤ ሥራ አጥነት ወጣቱን በፍትዎት ንግድ ውስጥ እንዲሰማራና የቤተሰብ ሀላፊነትን እንዲሸከም ያስገደደበት አገር መሆኑን ስናይ፤ “ረሀብ ባንድ ቀን ይገድላል ኤይድስ ፋታ ይሰጣል” የሚሉት አሰቃቂ ቀልድ የነገሰባት አገር ሞሆኗን ስንረዳ፤ ከልማት ይልቅ የቡና ቤቶች የክለቦችና የማሳጅ ፓርለሮች ኢንዱስትሪ እንደ እንጉዳይ የፈሉባት አገር መህኗን ስናስታውስ፤ ሙያ ይመስል አዲሳባ ባንኮክን ሆናለች እያለ የፍትዎት ቱሪዝምን የሚያሞግስ ትውልድ የበረከተበት አገር መሆኗን ስንረዳ ዳያስፖራውያን ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግ እንዳለብን እንረዳለን። ዶላርንና የውሸት ትዳርን አሰፍስፈው የሚጠብቁ እነርሱ አደገኞች ናቸውና እንቆጠብ።

በዋሽንግተን ዲሲ አካባቢ የሚኖረው ኢትዮጵያዊ በኤይድስ ወረርሽኝ በከፍተኛ መቶኛ የተመታው አገር ቤት ጋር ባለው ንኪኪ እንደሆነ በድፍረት መናገር ይቻላል። በሌላው ያሜሪካ ክፍልና በሌላው ክፍለ ዓለም ያሚኖረውም ኢትዮጵያዊም ከዚህ መቅሰፍት የተከለለ አለመሆኑን መዘንጋት የለበትም።

ገለልተኛነታችን ሊጎዳን መሰለኝ። ሀበሾች ስንባል ከሌላው ስደተኛ ህብረተሰብ በበለጠ በራሳችን ማህበረሰብ ውስጥ ተከልለን መኖርን እንመርጣለን። ይህ ተፈጥሯዊ መነሻ ቢኖረውም ተቋሞቻችን የሚገባንን እንክብካቤና ትመህርት ከሚሰጡበት የዕእድገት ደረጃ ላይ ካልደረሱ ተጎጅዎች እንሆናለን። አሜሪካኖቹ ኤይድስን በሚያክል አደገኛ ጠላት ላይ በሚያካሂዱት ዘመቻ ላንሳተፍ ነው። በዚህ በሽታ የተጠመዱ ወገኖቻችን ተደብቀው እንዲኖሩና ራሳቸውንም ሌሎችንም እንዲጎዱ ሰበብ እየሆንን ነው። ሀበሻው ጋር አድረን ሀበሻው ጋር ውለን ሀበሻው ጋር እስካመሸን ድረስ እንዲህ ያለ አደጋ ይመጣል፡፤

እናስ ታዲያ ምን ይሁን? እናማስ ሀላፊነት እንውሰድ። በየግላችን መውሰድ የሚገባንን ርምጃ በሃላፊነት ስሜት እንወጣ። ልጆቻችንንም ሰብሰብ አድርገን ያለ መሽኮርመም በዚህ ጉዳይ ላይ መወያየት ነው። በሞት ፊት መሽኮርመምን ምን አመጣው?

የሀይማኖት የፖለቲካና የማህበራዊ ተቋሞችም ችግሩን እያዩ እንዳላዩ አይሁኑና ይህን መሠሪ ጠላት በመዋጋት ረገድ አመራር ያሳዩን። ሦስቱም ቢሆኑ ጤነኛ ሕብረተሰብ በሌለበት ሊጠነክሩና ሊከበሩ አይቻላቸውም። በንዲህ አይነት ቅዱስ ዘመቻ ውስጥ የነቃ ተሳትፎ ያሚያደርግ ተቋም ከበሬታም ያገኛል የአባላትና የደጋፊ መሠረቱንም ያሰፋል። ኤይድስ በርዕዮተ ዓለምና በሀይማኖት ቀኖና ላይ የሚያሾፍና የሚረታ ሴሰኛ ባላንጣ ነው።


ቁጥር ቀልባችሁን ያስገኝልን እንደሁ ትንሺ በቁጥር እናስደንግጣችሁ። ዊኪፒዲያ የተባለው ድርጅት ለአቅመ አዳም የደረስውን በኤይድስ የተለከፈ ሕዝብ እንዲህ ያስቀምጠዋል። ታንዛኒያ 8.8% ኬንያ 6.7% ኮንጎ 4.9% ኢትዮጵያ 4.4% ። የሲ.አይ.ኤው ርፖርት ደግሞ የኢትዮጵያውን ወደ 10-18% ይተምንና በ 2010ዓ/ም ደግሞ ከ19-27% እንደሚደርስ ያሳስባል።

እንግዲህ የዲሲው ኤይድስ መቶኛ ከሦስተኛው ዓለም መቶኛ መብለጡ ካላስደነገጠን ምን ሊያስደነግጠን እንደሚችል አናውቅም። ዲሲን ከሦስተኛው ዓለም ጋር እንመድበው ይሆን?

Kuchiye@gmail.com

Monday, April 20, 2009

"ከተለየኸን ደህና ሁን!"
ለጥላሁን ገሠሠ ሙዚቃ ሙት መሆኔን አገር ያውቃል። የርሱ ሙዚቃ ዳግም ላይሰማ ይታገዳል ያሉኝ ይመስል ከሰሞኑ መልሼ መልሼ የማዳምጠው ጥሌን ብቻ ነበር።

እንደኔ ሙዚቃን የሚያሻምድ ሰው ጥላሁን ለትውልዳችን የተሰጠ ልዩ በረከት፤ የዕምነታችንና የሁሉም ዓይነት ምኞታችን መገለጫ ነው ብሎ ከደመደመ ቆይቷል። አጋነንክ የሚል ከመጣም እስከመጨረሻው እሞግተዋለሁ እንጅ እንደ ሉሲና እንደ አክሱም ሀውልት ብሔራዊ ቅርሳችን ነው ባይ ነኝ። ለዚህ ይመስለኛል የጥላሁን ዜና-ዕረፍት እንደተሰማ ሚሊዮኖች በመብረቅ የተመታ ያህል ባሉበት የደረቁት፤ ያነቡትና የተከዙት።

የኔው ድንጋጤና ሀዘን ግን ወደ ፍስሐና ወደ መስጋና ሲለወጥ ፋታ አልፈጀበትም። ልማድ ሆኖብኝ ሲከፋኝና ፍቅር-ፍቅር ሲለኝ ኮምፒውተሬ ላይ ዘወትር በተጠንቀቅ የሚጠብቀውን የጥሌን ሙዚቃ ነው ጠቅ የማደርገው። ዛሬም ያንኑ አደረግሁና ወደ ትራክ ስድስት መራሁት። የሙዚቃው አጀማመር ገና ከመነሻው ምድርን ቃጤ የሚያደርግ ዓይነት ነው፤ በጣም የተሟሟቀ፤ የጥድፊያ ጥሪ ያለበትም የሚመስል…...ጥሌን የሚጣራ የሚመስል። ወዲያው ተቀላቀሉ ጥሌና ሙዚቃ…..ይለቀው ጀመራ በዚያ መረዋ ድምጹ!

“ያሳለፍነው ዘምን ደስታን ያየንበት…….ተመልሶ ቢገኝ አሁን ምን አለበት”
እ….ህህ! እህ..እህህ! አይይይይ!

ይሄን ሙዚቃ ስንቴ እንደሰማሁት የሚያውቀው ፈጣሪ ብቻ ነው። ጥላሁን እጅግ አስቸጋሪ የሆኑ ኖታዎችን አዋህዶ የዘፈነበትና የድምጹ ቅላፄ ጐልቶ የወጣበት በዚህ ዘፈን ይመስለኛል። ቢሮዬ ወዲያው ተሟሟቀ። ለቀቅሁት እኔም እንዳቅሜ… አጀብኩት ጥሌን። ቢሮዬ ውስጥ ማን ለሲማኝ? ምድረ ፈረንጅ “ምን ተፈጠረ?” ብሎ ቢመጣም በቂ ምክንያት አለኝ አልኩ። የከበረና የተባረከ ህይወትን እየተሰናበትሁ ነው ካልኳችው እንደሚገባቸው አልተጠራጠርኩም። መቼም ፈረንጆች አይደሉም? ቀጠልን እኔና ጥሌ!.. “እ….ህህ! እህ..እህህ! አይይይይ!” አልን። ስንቱን ባነሆለለ ፈገግታው አየት ያደረገኝና “ቀጥል! ጥሩ ይዘሀል!” ያለኝ መሰለኝ ምን ገዶኝና ማንን ፈርቼ? ቀጠልኩ የጥሌን ትዝታና ውለታውን በልቤ እየመዘገብሁ።

ይሄ ነው እንጅ አልኩ! እንዲህ ነው እንጅ ጥሌን ማስታወስ። 55 ዓመት ሙሉ የምድረ ሀበሻን ቤት በደስታና በፈንጠዝያ የመላ፤ ያሳቀ፤ ያስደለቀ፤ መድረኮችን ያስጨነቀ፤ የወደደና ያዋደደ። ሺኝቱ በተለየ መሆን አለበት አልኩ። ልንሸነው የሚገባው በትዝታ ቅኝት፤ በባቲ ለዛ፤ ባንች-ሆየ ቃና፤ በ “ሠላመካ” ዝማሬ መሆን አለበት ብዬ ወሰንኩ። የ “አልቻልኩም”ን ጀግና፤ የ “ይህ ነው ፍላጎቴን” መሪ-ጌታ የምንሸኘው ከበሮው እየተደለቀ፤ ሳክሱ እየሳቀ፤ ትራንፔቱ እያማለለ ሊሆን ይገባል አልኩ።

ጥላሁን ዝንተ ዓለም አይረሳም። መሰል-የለሺ እንጉርጉሮዎቹን፤ ግርማ ሞገሱንና የርሱ ብቻ የሆነ ለዛውን በውስጠኛው የምናባችን ክፍል አትሞብናልና። የዘመናችንን የኪነት የበህር ልጅ እንዴትስ ልንረሳው ይቻለናል?

በል ደህና ሁን ጥሌ! ከተለየኸን… ደህና ሁን!
Kuchiye@gmail.com

http://www.voanews.com/horn/amharic_audio.cfm

Friday, December 12, 2008

"Amharic or English? – Expanding the Democratic Base"

I confess I am as badly hyphenated as any in the Diaspora. Only the other day a rude awakening hit home when my son asked me to translate an Amharic article I wrote in connection with the Obama campaign. Apparently an insider had intimated to him about a tangential reference I made to the young man.
http://www.abugidainfo.com/wp-content/uploads/2008/11/obama_election_110808.pdf.

Translate I did, carrying a sense of guilt for raising an Amharic language challenged child. Assuming my own family serves as microcosm of a typical Diaspora family, surely the question of whether or not to write in English becomes a real issue.

But wait! Just about a year ago I encountered a dilemma of the reverse kind. In one of my rare moments of brilliance I concluded that punditry in English is not of much consequence since 80% of Ethiopians in the Diaspora, according to my cursory survey, are far more conversant in Amharic than they truly are in English. That is when I started writing in Amharic with still improving eloquence. Who am I kidding? my English wasn’t that earth shattering in the first place.

Such being the case, who indeed are Ethiopian pundits targeting as their audience or are they trying to convert the converted, to teach the learned? Are they engaged in a feel-good exercise that the elite are all too often accused of? If they knowingly target the learned 20%, aren’t they investing 80% of their effort on 20% of the opportunity? Please understand I am asking theses questions in good faith and from a desire to see the ideas of these brilliant minds flourish in every Ethiopian house and heart.

Just look around and figure out how many out of 10 people in a public gathering, the church, the mosque or “Mahber“ understand let alone appreciate the luminous articles of Prof. Alemayehu G/Mariam, Prof. Teodros Kiros, Fekade Shewakena, Robel Ababiya and Selam Beyene, to name but a few? Not many, I am afraid. Isn’t it precisely the reason why we conduct meetings in Amharic? Isn’t it why we have Amharic rather than English radio and TV stations? Amharic rather than English newspapers? So what is up with this cyber punditry in English?

Let’s for the sake of expediency assume 20% of our community posses adequate knowledge of the English language; enough to understand conceptual arguments and patient enough for lengthy diatribes. Since we are in a giving season, I will throw in another 5% to account for the “Am-English” speaker and swell the potential audience to 25%. Of this, what percentage will be interested in politics? What percent will access the internet regularly and if that to check emails and pay the bloody bills electronically? What percentage will postpone chasing the American or some other dream and sacrifice an afternoon for a public rally to protest the unfair imprisonment of Teddy Afro? I would say a paltry 1%. Trust me; this number did not come out of thin air but from real experience. If you are Thomas the doubtful, take a look at some factual information on the most frequently visited websites:


Trafic rank based on combined measure of page views & users (average one month)
Abugidainfo 264,538
Ethiomedia 150,303
Ethiopian Review 130,675

Traffic rank based on a combined measure of page views and users (reach) – Average 3 months
Abugida 154,542
Ethiomedia 156,787
Ethiopian Review 75,468
Source: Alexa (December 4, 2008)

Let’s see.
http://abugidainfo.com, for example, enjoys an average of 4,408 visitors per day including repeat visitors, (264,538/30 days/2pages per person =4,408). Does that mean my article on Abugida will be read by all 4,408 visitors? Most certainly not; but I will dwell on that some other time.

Considering a universe of about 1 million Ethiopians living abroad, the combined number of hits our websites receive is dismal. I have deliberately left out the home front for two reasons. One, most good websites are banned. Two, even if they were not banned, the pathetic bandwidth problem of the country makes internet surfing a truly demoralizing experience. These are material facts over which web site administrators and cyber pundits need to scratch their heads about.

So the question becomes “How do we increase internet traffic?” Jeff Bezo of Amazon and Eric Schmidt of Google fame would tell us the key is “content”. Trust me once again, these billionaire tycoons know what they are talking abut.

How do you then improve content and increase traffic when you are writing in English with almost total disregard to 80% of the community?

Is this going to be a case of damned if we write in Amharic and exclude the young and damned if we write in English and ostracize the majority? It doesn’t have to be.

Obviously, a blanket outreach module does not work since communities have varied interests, language preferences, esthetic values etc. We can and must stratify our society into meaningful groups so that appropriate communication modules that help in reaching every sector of society proliferate. Only then will we be able to expand the democratic base and garner sustained support from well informed and well committed citizens.

As for me, I will continue to have fun writing in Amharic and maybe occasionally in English. Just find me copy of that famous book “Lemma Begebeya” so I can launch a “Meserete Timhrt” program for my son.

Merry Christmas!

kuchiye@gmail.com

Saturday, November 08, 2008

“የኦባማ ትንግርትና ዳያስፖራው!”
ባሜሪካው ትንግርትና በበራክ ኦባማ መመረጥ ያልተደነቀና ያልፈነደቀ የዴሞክራሲ ወዳጅ ተፈልጎ የሚገኝ አይመስለኝም። በውጥረት የተከበበች ዓለምና ተስፋ እየራቀው የመጣ ሕዝብ ሁሉም ማለፊያ ሊሆን እንደሚችል የሚያረጋግጥለት ድምጽ ሲያገኝ ደስ ይላል።

ይህ እንዳለ ሆኖ ከዛሬው ፈንጠዝያና ግርግር ባሻገር የምናገኘውን መጠነ ሰፊ ትምህርት እንዳንስት እሰጋልሁ። ትምህርቱ ላሜሪካኖች ብቻ የመጣ ሳይሆን ያለም ዳርቻን ያዳረሰ አዋቂውንና ምሁሩን ሁሉ አፍ ያስከፈተ የሚሊኒየም አርዓያ ስለሆነ ነው።

የኦባማ ትንግርት አይቀሬ የትውልድ ርክክብና የዘመን ሺግግር የታወጀበት ለመሆኑ አያጠራጥርም። አሜሪካ ይኑር ኢትዮጵያ፤ አውስትራሊያ ይኑር ብራዚል፤ የዚህ የ21ኛው ክፍለዘመን ትውልድ አመለካከትና የትኩረት አቅጣጫ ከኛው አመለካከት ፈጽሞ የተለየ መሆኑን ለማዬት በቅተናል። ያረጀ ርዕዮት በአዲስና ወደፊት ብቻ በሚመለከት ርዕዮት መቀየር እንዳለበት ተረድተናል። የቆዳ ቀለም፤ የብሔር መሠረትና ሌሎቹም ኋላ ቀር አመለካከቶች አሳፋሪ ቅርሶች እንደሆኑ በማያሻማ ቋንቋ ተነግሮናል። አዲሱ ትውልድ የስጋት ዘንግ በመስበቅ፤ የጥርጣሬ መርዝ በመዝራት፤ ከፋፋይ ፕሮፓጋንዳ በመንዛት እንደማይደነብርና እንደማይበገር አሳውቆናል። የማኪያቬሊን መጽሀፍ ሲያነበንቡ የሚያድሩና የፖለቲካ እንዝርት ሲያሽከረክሩ የሚውሉ ገዥዎች ዘመናቸው እንዳበቃ ይህ ትውልድ በራክ ኦባማን በመምረጥ አውጇል።

በትንሿ በራሴ ቤት እንኳ ተአምር ለማየት በቅቻለሁ። የ23 ዓመቱ ልጄ ኦባማ ጋሪ ላይ የተሳፈረው ከመነሻው ነበር። የ4ኛ ዓመት ኮሌጅ ተማሪ ቢሆንም ቅዳሜና እሁዱን፤ ሌላም ትርፍ ጊዜውን ለበራክ ዳረገ። ይህን አገኛለሁ ብሎ ሳይሆን ለኔና ለመሰሎቼ ያልተሰማን የትውልድ ቃጭል ጥሪ ተሰምቶት። እልም ባለ በረዶና በበጋው ወበቅ ከኒው ሃምሸር እስከ ቨርጂኒያ በራሱ ገንዘብ እየተጓዘ የማያውቃቸውንና የማያውቁትን ሰዎች ቤት አንኳኳ። ባራክንና ፕሮግራሙን አስተዋወቀ፤ አሳመነ፤ ስልጡን ሙግት ተሟገተ፤ ግልምጫ ቀመሰ፤ ተጠራጠረ፤ እንደገና ደግሞ አመነ። ተማረ.. ብዙ ተማረ።

ከምንምና ከማንም ይበልጥ እንቅልፉን ሲወድ የማውቀው ብላቴና፤ ሰዎች በፖለቲካ ውይይት ተጠምደው ሲያይ ከሞኝ ይቆጥር የነበረ ወጣት፤ ና እንግዳ ተዋወቅ ሲሉት መኝታ ቤቱ ውስጥ የሚታሺ ልጅ፤ አይፖዱን ጆሮው ላይ ሰክቶ እራሱን ኬሌላው ዓለም ያገለለው “ማይክ” ዛሬ ግፊቱንና ወኔውን ከየት እንዳገኘው ሳሰላስል እራሴ ይዞራል። በኔ የሀያ ዓመት ጭቅጭቅና ማባበል ያልተበገረ ቆዳና አዕምሮ በዚህ ዘመን በነፈሰ አየር ፈክቶና አብቦ አገኘሁት።

ይህ በጎ አየር ያወደው የኔውን ቤት ብቻ ሳይሆን መላ ሕብረተሰቡንና መላ የወጣቱን ትውልድ እንደሆነ የተረዳሁት ወዲያውኑ ነው። ፈረንጁና ጥቁሩ፤ ሂስፓኒኩና ኦሪየንታሉ፤ ወጣቱና ሽማግሌው፤ ሴቱና ወንዱ በኦባማ ፕላትፎርም አማካይነት አንድ አካልና አንድ አምሳል ሆነው፤ ያንድ አገር ዜጋና ያንድ ብሩህ ተስፋ ባለቤት ሆነው፤ እንደ አንደ ትልቅ ሠራዊት ተንቀሳቅሰው ኦባማን አስመረጡት።

አገራቸው የምትጓዝበትን የስግብግብነት፤ የጥፋት፤ የጥርጣሬና የጥላቻ ሀዲድ ፍቅር መተሳሰብና ሰብአዊነት ተዋህደው በፈጠሩት ሀዲድ ለወጡት። ባውሮፕላን ተበሮ በመኪና ተንድቶ ማለቂያ በማይገኝለት፤ ያዳም ዘር ዓይነት በሚተራመስበት የሦስት መቶ ሚሊዮን ዜጎች ቤት ይህ የሥልጣንና የትውልድ ሺግግር ሲፈጸም አንዲት ጥይት አልተተኮሰችም፤ አንዲት ቦምብ አልፈነዳችም። ተሸናፊው ማኬን የበራክን ማሸነፍ ተቀብለው መድረኩን ሲለቁ ያደረጉት ንግግር ልብ የሚነካ ብቻ ሳይሆን ስልጡን ፖለቲካ የቱን ያህል ስልጡን እንደሆነ የሚያመለክት ነበር። ለማኬን ከቀድሞ የበለጠ አክብሮት ሰጠኋቸው። ላሜሪካ የዴሞክራሲ ባህል ያላደርግሁትን ባርኔጣ አነሳሁለት። የዕለቱን ግዙፍነትና ምሳሌነት እንደተረዱ ሰዎች ሁሉ እንባዬ ሲንከባለል አገኘሁት። በዚህ ታሪካዊ የሺግግር ወቅት በህይወት መኖሬን ወደድሁት፤ ታሪክ ተመልካች ብቻ ሳልሆነ ያቅሜን ተሳትፌ የታሪኩ አካልና ባለቤት ሆንኩ። እኔና ልጆቼ ለመጀመሪያ ጊዜ ያንድ ዕምነትና ያንድ አስተሳሰብ ማሕበርተኞች ሆነን ጥዋ ጠጣን። ለዚህም ፀጋ ፈጣሪየን አመሰገንሁት። ከልቤ።

ስለ ኢትዮጵያዊው ሕብረተሰብ በጥቂቱ ላንሳ። ኢትዮጵያዊው ኦባማን የደገፈው በሙሉ ልቡ ብቻ ሳይሆን ለጊዜውና ለኪሱ ሳይሳሳ ነበር። በካምፔይኑ ቢሮዎች በፈቃደኝነት እየተገኘ የ “ምረጡ!” ስልክ የደወለው፤ ከቤት ቤት እየዞረ የቀሰቀሰው፤ ደካሞችን በግል መኪናው ወደምርጫ ጣቢያ ያመላለሰው ሀበሻ ብዛት ያመሪካኖቹንም የሚዲያውንም ቀልብ ስቧል። ባማርኛ የተጻፉ ማስታዎሻዎች፤ ስሞችና የመልካም ምኞት መግለጫዎች በካምፔይን ቢሮዎች ማዬት የተለመደ ብቻ ሳይሆን ላሜሪካ ሕብረቀለማዊ ውበት የበለጠ ድምቀት ያጎናጸፈ ነበር። በዚህ የተሳትፎ መጠን ኢትዮጵያውያን ወጣቶች በየመሥሪያ ቤቱ በተሿሚነት ብቅ ብቅ ቢሉ ልንደነቅ አይገባም።

ኢትዮጵያዊው ባሜሪካው ምርጫ እንዲህ በጋለ ስሜት የተሳተፈበት ምክንያት ለኔ ግልጽ ነው። ዳያስፖራዊው ዴሞክራሲን በትውልድ አገሩ ለማየት ከፍተኛ ትግል ያካሄደና ብዙ መሰዋዕትነት የከፈለ ነው። ባገሩ ያላገኘውን ፀጋ ዛሬ በሰው አገር ሆኖ ቀመሰው። በየካምፔይኑ ቢሮ ሲሯሯጥ፤ ያለክፍያ ሲለፋና የውድድሩን ዕድገት በአንክሮ ሲከታተል እናት አገሩንና ወገኑን እያስታወሰ ለመሆኑ አልጠራጥርም። ይህ ወግ አንድ ቀንና በቅርቡ የወገኑ እንዲሆን እየተመኘና ከህሊናው ጋር ቃል ኪዳን እየገባ ነው።

የኦባማ ትንግርት የዳያስፖራውም ድል ነው ስል ምክንያት አለኝ። በዚህ የምርጫ ጉዞ ውስጥ ወገኔ የበለጠ ዕውቀት፤ የበለጠ ልምድ፤ የበለጠ ወዳጅና ዘርፈ-ብዙ የግንኙነት መሥመሮች ዘርግቷል። የፖለቲካ ካፒታል አከማችቷል። ይህ ዕውቀት ይህ ግንኙነትና ይህ የፖለቲካ ካፒታል በሚያስፈልግበት ጊዜ የሚመነዘር ሀብት ነው። የዳያስፖራው የዴሞክራሲ ንቅናቄና ማህበራዊ ፕሮግራሞች በደለበ ልምድ፤ በሰላ ማኔጅመንትና በዘመናዊ ቴክኖሎጅ ተደግፈው ሲመሩ ይታየኛል። ይህ ልምድና የጋለ ስሜት ወደ ሀገር ቤት ሲዛመት ደግሞ በኢትዮጵያ አዲስ ዘመን ይሆናል።

kuchiye@gmail.com

Saturday, September 20, 2008

“ፊታውራሪ ተክለሀዋርያት ተክለማርያም - ኦቶባዮግራፊ”
የመጽሐፍ ግምገማ


የዘንድሮው በጋ በሥነ ጽሑፍ ረገድ ፍጹም ለጋስ ነበር ለማለት እደፍራለሁ። ሁለት ድንቅ ያማርኛ መጽሕፍት በማግኘቴ እንደታደልኩ ቆጠርኩት። የፊታውራሪ ተክለሀዋርያት “ኦቶ ባዮግራፊ” እና የብላቴን ጌታ መርስዔ ሀዘን “የኢትዮጵያ ታሪክ -ከንግሥት ሳባ እስከ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ” ግሩም መዘክሮች ብቻ ሳይሆኑ ባገራችን፤ በሕዝባችን፤ በባህላችንና በታሪካችን ላይ የየራሳችንን ግንዛቤ እንድንይዝ ነፃነት የሚሰጡ ሆነው አገኘኋቸው።

ስለሁለቱም መጻህፍት ባንድ አፍ መመስከር በሁለቱም ላይ ወንጀል መፈጸም ስለሚሆንብኝ በዛሬው አቅርቦቴ የተክሌ ኦቶባዮግራፊ ያሳደረብኝን ስሜት አካፍላችኋለሁ።

አስተዳደግ
ተክለሀዋርያት የተወለዱት በ1874-1876 አካባቢ ተጉለት ውስጥ ነው። እስከ ዘጠኝ ዓመት ዕድሜያቸው በቄስ ትምህርት ቆዩና ወግና ሥርዓት ያጠኑ ዘንድ በአደራ ልጅነት ሀረር ለራስ መኮንን ተሰጡ። በዚያ ዘመን ልጁን በጌታ ቤት ለማሳደግ የቻለ ወላጅ የታደለ ነበር። በኛ አገር ብቻ ሳይሆን በሌላውም። “ሳይደብር” መንደር የተወለደችው ተክሌ “በቤት ላይ ቤት የተሠራበትን” የሀረር ከተማ ስታይና በሱቆቹ ውስጥ የተደረደሩትን ስንትና ስንት ዓይነት የባህር ማዶ ዕቃዎች ስትመለከት ጉድ! አለች፤ ምኞትም ተለኮሰባት።

“ባህር ማዶ የሚባለውስ አገር እነዚህ ሁሉ የውበት ዕቃዎች የሚፈጠሩበት ስንትና ስንት ጥበብ ይገኝበት ይሆን?… እዚያው ድረስ ሄዶ ማየት፤ መፈረጅ፤ መመርመር፤ መዳሰስ የሚቻል ቢሆን እንዴትስ ባስደሰተ ነበር?” አለች።

ተክሌ ብሩህ ጭንቅላት ያላት ብልጣብልጥ “ማቲ” ስለነበረች ራስ መኮንንና ባለቤታቸው ሲወዷት ጊዜ አልፈጀባቸውም። እንደሎሌ ሳይሆን እንደ ልጅ አቀረቧት፤ ትምህርት ቤት አስገቧት። ከሃላፊነታቸው ጋር ተያይዞ በሚመጣ ሃሳብ ሲወጠሩ እንኳ ራስን የምታስቅ ተክሌ ሆና ተገኘች። ባለሟልነታቸው ከመጥበቁ የተነሳ አድዋ ጦርነት ካልዘመትኩ ብላ ብታለቅስባቸው ራስ መኮንን ሊጨክኑ አልቻሉም። “ግዴለም መንገድ ለመንገድ ያጨውተኛል ይዝመት” አሉ። አዎን ተክሌ ለዘመቻ ክብር በመብቃቷ ጓደኞቿ እስኪቀኑባት ድረስ ፈነደቀች። የተሸለመችውን መሣሪያ ወልውላ በአሥራ ሁለት ዓመቷ ለወግ በቃች። ግዳይ አታስቆጥር እንጅ እንዳቅሚቲ ከዚያ ያላነሰ ቁምነገር ሠራች።

በተክሌ ብሩህነትና የማወቅ ጉጉት የተማረኩት ራስ መኮንን ተክሌን ባሕር ማዶ ልኮ ለማስተማር ቃል ገቡ። ታዲያ ይህ ቃልኪዳን ተድበስብሶ ይቀራል የሚል ስጋት ያደረባት ተክሌ ራስን መውጫ መግቢያ አሳጥታ በጃንሆይ አፄ ምኒልክ ፈቃድ በአሥራ ሦስት ዓመቷ ሩስያ እንድትሄድ ሆነ። ሩስያ ያኔ የምትተዳደረው በንጉሠ ነገሥት ዛር ኒኮላ 2ኛው ነበር። ኮሚኒዝም ባገሩም አልተፈጠረም።

የመጽሐፉ ጭብጥ

ጽሑፉ በዕውነተኛ የሕይወት ታሪክ ላይ የተመሠረተ በመሆኑ የአንባቢን አመኔታና ቀልብ የመማረክ ኃይል አለው። ገና በህጻንነት ዕድሜ ባለታሪኩ ህሊና ውስጥ የተጠነሰሰው የማወቅና ሕብረተሰብን የመለወጥ ጉጉት ያዳም ዘር ጉጉት ነውና ወዲያውኑ እንጋራዋለን። ይሳካለት ይሆን? የአሥራ ሁለት ዓመት ልጅ በማያውቀው አገር ባህልና ዘመናዊ አኗኗር ከተነከረ በኋላ ከቀድሞ ጉጉቱና ከኢትዮጵያዊነቱ ጋር የመመለስ ዕድሉ ምን ያህል ይሆናል? ተምሮ የሚመለስ ቢሆንስ በኢትዮጵያ የተንሰራፋውን ኋላቀር ስርዎ ምንግሥትና ባህል የመቋቋም አቅም ይኖረዋል? ሥር በሰደደ ጥቅም የተሳሰሩት መሳፍንት፤ ባላባቶች፤ መሀል ሰፋሪዎች፤ ካሕናትና ሸኮች ምን ፈተና ይደቅኑበት ይሆን? ይህንን ሁሉ ለመቋቋም የሚያስችል የህሊና ጽናት፤ ስልትና ትዕግሥት ይኖረውስ ይሆን የሚሉ ጥያቄዎች መንፈሴ ውስጥ የተደረደሩት ከመነሻው ነበር። የተዋጣላት መጽሐፍ እንዲህ ያሉ ጥያቄዎችንና ስጋቶችን ባንባቢ ዓዕምሮ ውስጥ የመጫር ችሎታ አለው።

ከሥነ ጽሑፍ አኳያ
ይህ መጽሐፍ አንጸባራቂ የሥነጽሑፍ እሴቶች አሉት። ትረካው በአጫጭር ዓረፍተነገሮች የተገነባ ስለሆነ አንባቢን ትንፋሽ በሚያስቆርጥ ሀተታ ውስጥ አያንከራትትም። በጥንቃቄ የተመረጡ የለት-ተለት ቃላት ሕብረት ጽንሰ ሀሳቦችንም ሆነ ትረካዎችን የቱን ያህል እንደሚያሳምሩ በውል ያየሁት በዚህ መጽሐፍ ነው።

ፊታውራሪ ተወለዱበትን አጥቢያ፤ የህዝቡን አኗኗር፤ የራስ መኮንንን ችሎት፤ የመቀሌን ያምባላጌንና የአድዋን ጦርነቶች፤ እንዲሁም በልጅ እያሱና በተፈሪ መኰንን መሀከል የነበረውን የሥልጣን ሽኩቻ ፤ የሩስያ ቤተሰቦቻቸውን የተንጣለለና የረቀቀ አኗኗር፤ የኑሮ ፈተናዎቻቸውንና ገጠመኞቻቸውን የሚገልጹት ጨርቁን በጣለ ግልጽነት ነው። ቀልዳቸውና ያጻጻፍ ዘይቤያቸው የሚያስቅበት ጊዜ ብዙ ነው። ከሌሊቱ 8 ሰዓት እንደዕብድ ብቻየን የተንከተከትኩትን ቀን አልረሳውም። ታዲያ ልብ ያላለ ሰው አንዳንዱን ወዛም ቀልድ ሊስተው ይችላል።

በፊታውራሪ አገላለጽና የትንታኔ ዘይቤ ውስጥ ደግሞና ደጋግሞ የሚታይ ነገርም አለ። እኒህ ፀሐፊ የጣኦት ያህል የሚታዩትን የነቶልስቶይን፤ የነፑሽኪንን፤ የነሸክስፔርንና የሌሎችንም ሥራዎች በግላቸውና በሩሲያ አካዳሚ ውስጥ አንጥረውና አበጥረው ያነበቡ ለመሆናቸው አጻጻፋቸው ይመሰክራል። ስለዚህም ዘይቤያቸው ካብዛኛው ኢትዮጵያዊ ደራሲ የተለየ ሆኖ ታየኝ።

ተክሌ መልክዓ ምድሮችን፤ የታሪክ ክስተቶችን፤ የፖለቲካና ያስተዳደር ገጠመኞችን ሲገልጹ ባንባቢው ሕሊና ውስጥ የሚቀርጹት ሥዕል የሲኒማ ያህል ነው። ያውም ህብረቀለማዊ “ሃይ ዴፊኒሽን” ሲኒማ ያህል። የጸሐፊው ተክሌና የኔ ገጸባህርይ በብዕር ኃይል አንድ ሆኑ። ሳይደብር ምንጃር ከተክሌ ጋር ፊደል ቆጠርኩ፤ ዳዊት ደገምሁ፤ ስቦርቅ አደግሁ። በራስ መኮንን አደባባይ እድሌን አስተካከልሁ። አድዋ ላይ የጦርነትን አስከፊ ገጽታ፤ የመስዋዕትነትን ክብር፤ የኋላቀርነትን ጣጣ፤ የየዋህነትን መዘዝ፤ የክህደትን አስጸያፊ መልክ አስተዋልሁ። ሩሲያ በተክሌ “አያት” ቢብሊዮቴክ ውስጥ የተደረደሩትን መጻህፍት ከተክሌ ጋር ሆኜ አስጨነቅኋቸው፤ የሥልጣኔን ምስጢር ውለዱ አልኳቸው። ያገሬን ድህነትና ኋላቀርነት አንጀቴን እስኪያመኝ ድረስ ተቀበልሁት። በትጋት ተምሬ በቶሎ ላገሬ እንድደርስላት ከተክሌ ጋር ምህላየን አደስኩ።

የተክለሀዋርያት ፈተናዎች
ተክለሀዋርያት ኢትዮጵያ ከተመልሱ በኋላ የገጠማቸው ፈተናና ያለፉበት መንገድ አንባቢን ሰቀቀን ውስጥ የሚጥል ነው። ያስጨንቃል፤ ያስቆጣል፤ ያስተክዛል፤ ተስፋ ይሰጣል፤ እንደገና ደግሞ ተስፋ ያጨልማል። ሥልጣኔን ለማምጣት በሚተጉና የቀድሞውን ሙጥኝ በሚሉ መሀከል የሚካሄደው ጦርነት፤ ሴራ፤ ሺወዳ፤ እጅግ የበዛ ነበር። የተክሌ ጨቅላ መንፈስ በሚኒልክ የሥልጣኔ መውደድ ተማርኮ ነበር። ከሩስያ እንደተመለሱ ምኒልክ ስለሞቱ ለውጥ የማምጣት ተስፋቸውን መጀመሪያ በልጅ እያሱ ላይ፤ የልጅ እያሱ ነገር እንዳልሆነ ሲሆን በተፈሪ መኮንን (አፄ ኃይለ ሥላሴ) ላይ አሳረፉ።

ተክሌ ኢትዮጵያን ከድህነት ለማውጣትና ከጥቃት ለመጠበቅ የሚጠፋ ጊዜ ሊኖር አይገባም፤ በሀቅና በጥድፊያ መሥራት አለብን ባይ ነበሩ። አፄ ኃይለ ሥላሴ ደግሞ ይዘው የተነሱትን የለውጥ ተስፋ ለከንቱ ውዳሴና ለሥልጣን መቆያ ዳረጎት እያደረጉት መጡ። የተክለሀዋርያት ሀቀኝነትና ድፍረት ለቤተመንግሥቱና ለሥርዓቱ አልመች ስላለ ውለታ በሠሩላቸው ንጉሥ ታሠሩ በኋላም የግዞት ያህል በሀረር ሂርና እርሻቸው ላይ ኖረው አለፉ።

ኦቶ ባዮግራፊ መጻፍ ባልተለመደበትና ምናልባትም ስለራስ መመስከር እንደጉራ በሚቆጠርበት አገር የቀድሞዋን ኢትዮጵያ የምንመለከትበት መስኮት ስለከፈቱልን የፊታውራሪ ተክለሀዋርያትና የሳታሚ ልጆቻቸው ባለውለታ ነን። መጽሐፉ በቴፕ ቢቀረጽ ለብዙዎች የደስታ ምንጭ እንደሚሆን አይጠረጠርም። ለዶኪመንታሪና ለፊልምም በጣሙን የተመቼ ነውና እስቲ እንነጋገርበት። ወዳጆቼ! ይህ መጽሐፍ ከቤታችሁ መጥፋት የሌለበትና ለወዳጅ እንኳ የማይዋስ ነው።

የግርጌ ማስታወሻ
አንድ ሰው ስለራሱ ሲተርክ ያለፈባቸውን ዘመናት የታሪክና የባህል ጭብጦች መነካካቱ ግድ ነውና መጽሐፉ የሱ ታሪክ ብቻ ሳይሆን የትውልድም ታሪክ ይሆናል። ስለዚህ ፖለቲከኛውም፤ አስተዳዳሪውም፤ ነጋዴውም፤ ገበሬውም፤ ደራሲውም፤ ተዋናዩም ኦቶባዮግራፊ የመጻፍ ባህል እንዲያደብሩ ተገቢ ነው። “አይ እኔ ምን ታሪክ አለኝና?” በሚል ራስን ዝቅ በሚያደርግ ባህል ታስሮ ኦቶባዮግራፊ ከመጻፍ መቆጠብ የትውልድ ታሪክ ተቀርጾ እንዳይተላለፍ የሚያደርግ ዓይነት ወንጀል ይመስለኛልና በተለይ ዕድሜ መገባደጃ ላይ ያላችሁ ተነቃቁ እላለሁ።

kuchiye@gmail.com
"አንነጋገር? ... አንደማመጥ?"

ያለንበትን ዘመንና የገባንበትን የፖለቲካ አጣብቂኝ በቅጡ ያጤነ ሰው ይህን ዓይነት ጥያቄ ያነሳል ብዬ ማመን ያስቸግረኛል።

ባለፈው ሳምንት “አዲስ ሬዲዮ” ከአቶ ገብሩ አሥራት ጋር ያደረገውን ቃለ ምልልስ ያዳመጥኩት በጥሞና ነበር። የፕሮግራሙ አዘጋጅ ያነሳቸው ጥታቄዎች መሠረታዊና በሳል ሲሆኑ አቶ ገብሩም ዋዘኛ የፖለቲካ ሰው አለመሆናቸውን አመላክተዋል ።

ያስደነገጠኝ ነገር ቢሆን ፕሮግሙ ፍፃሜ ላይ በአዘጋጁ ላይ የተሰነዘርው የስልክ ዘለፋ ነው። “ትናንት ከመለስ ዜናዊ ጋር ሆኖ አገር ያስገነጠለ፤ የጎሳ ፓርቲ ያቋቋመ ... ወዘተ እንዴት በፕሮግራምህ ላይ ታቀርባለህ? እንዴትስ ብለህ ሴፕቴምበር 20 ለገብሩ አሥራት የተጠራውን ሕዝባዊ ስብሰባ ታስተዋውቃለህ?” የሚሉ ዓይነት ነበሩ። ይህ ቀሊል አመለካከት በአብዛኛው ሕብረተሰብ ውስጥ እንደማይንጸባረቅ አውቃለሁ። አንዳንድ ሬዲዮ ጣቢያዎች ሥር ተለጥፈው ጉሮሯቸው እስኪነቃ ያንኑ ዜማ መልሰው መልሰው የሚጫወቱት የተወሰኑ ሰዎች ናቸው።

ጎበዝ! “ፖለቲካና ዲፕሎማሲ መንደርደሪያቸውም መደምደሚያቸውም ንግግር ነው። በፖለቲካ ውስጥ ዘላቂ ጥቅም እንጅ ዘላቂ ጠላት የለም” የሚሉትን ብሂሎች ስንት ጊዜ እንደጠቀስኳቸው አላስታውስም። ብሉይ በሐዲስ ኪዳን እንደታደሰ ያልሰሙ ሰዎች ዓይን ያጠፋውን ዓይኑን በማጥፋት፤ የገደለውን በመግደል ካልቀጡ በስተቀር ስርየት የተፈጸመ አይመስላቸውም። ይህ ታዲያ ወደፊት እንዳንራመድ ቀፍድዶ የያዘን አስተሳሰብና ለምንገኝበትም የፖለቲካ አጣብቂኝ ዋነኛው መነሾ ነው። የኛ አገር ብቻ ሳይሆን ኋላቀር በሚባሉ ሀገሮች ሁሉ የተንሰራፋ ነቀርሳ፡፡

ያለፈውን ሰላሳና አርባ ዓመት ታሪካችንን መለስ ብለን ብንቃኝ ብዙ መማር እንችላለን። የአጼ መንግሥት ባንድ በኩል፤ ጀብሀና ሻዕቢያ በሌላ በኩል ተደራድረው ለመስማማት ባለመቻላቸው በየጦር ሜዳው ሺዎች ረገፉ። ባንድ የፖለቲካ ርዕዮት ውስጥ የታቀፉት ኢሕአፓና መኢሶን በታክቲካዊ ልዩነቶቻቸው ላይ ለመወያየት እንኳ ባለመፈለጋቸው የብዙሀን ደም በከንቱ ፈሰሰ፤ እነሱም ድብዛቸው ጠፋ። ደርግም ንግግርን እንደሺንፈት ይቆጥር ነበርና በግትርነት ያካሄደው ውጊያ ለመቶ ሺዎች ህይዎት ማለፍ ምክንያት ሆነ። መለስ ዜናዊና ኢሳይያስ አፈወርቂ ሺምግልናን አሻፈረን ብለው ባካሄዱት ጦርነት እስከ መቶ አርባ ሺህ የሚደርስ ውድ ሕይዎት ጠፋ። የ2005 ምርጫ ያስከተለውን ውዝግብ ለመፍታት ዓለም-አቀፍ ሺማግሌዎች ዜናዊንና ተቃዋሚውን ወገን አነጋግረው ለማስማማት ያደረጉት ጥረት በምቢተኝነት በመክሸፉ የንጹሀን ደም ያለዋዛ ፈሰሰ፤ በሕዝቦች መሀከል አደገኛ ቁርሾ ተዘራ፤ ሕዝባችንም ይህ ነው ለማይባል የአፈና ዘመን ተዳረገ። ብዙ ተስፋ የተጣለበት የቅንጅት እንቅስቃሴ ጉዳት ሊደርስበት የቻለው በመሪዎቹ መሀከል የተፈጠረውን አልባሌ ልዩነት በንግግር ለመፍታት በጎ ፈቃድ ባለመታየቱ እንደነበር ሳላነሳው የማላልፈው ጉዳይ ነው።

በፈረንጆቹ አባባል ታንጎ ለመደነስ የሁለት ሰዎችን ፈቃደኝነትና የጋለ ስሜትን የጠይቃል። ለዚህ ነው ይህ ጥፋተኛ ነበር ይኸኛው ደግሞ አልሚ ነበር ወደሚለው ፍርድ ውስጥ ልገባ ያልፈቀድሁት። ቁምነገሩ ባለፉት አርባ ዓመታት ውስጥ የፖለቲካ ችግሮቻችንን እንደሠለጠነ ህዝብ በንግግር የፈታንበት ዘመን እንዳልነበረ ለማመላከትና የችግሮቻችን ሁሉ መፍቻ ቁልፍ እንዲሆን ለማሳሰብ ነው።

አዲስ ሬዲዮ ከገብሩ አሥራት ጋር ወዳደረገው ቃለ-መጠይቅ ልመለስ። አቅራቢው አበበ በለው የተዋጣለት ጋዜጠኛ እየሆነ መምጣቱ ልቤን ያረካዋል። አቶ ገብሩን ሲጋብዝ ትክክለኛ የጋዜጠኛ ሥራውን አከናወነ። ሳይጋብዝ ቀርቶ የወቀሳ ናዳ ቢደርስበት ኖሮ ብዕሬን ባላነሳሁለት ነበርና እሰዬው! እንኳንስ በጋዜጠኝነት ቃልኪዳንህ ተገኘህ እለዋለሁ። ጥያቄውው በሳል መልሱም ጉጉት የሚፈጥር ስለነበር እኒህ ሰው ስላገራቸው ያላቸውን አመለካከት ይበልጥ ለማወቅ በመስከረም 20ው ስብሰባ ላይ ለመገኘት ወስኛለሁ።

በቃለ-መጠይቁ ከአቶ ገብሩ አሥራት እንደበት የሰማኋቸው “አገራችን በከፋ አደጋ ላይ ትገኛለች! ያለው አስተዳደር ኢዴሞክራሲያዊ ነውና ተባብረን ደሞክራሲያዊ ሥርዓት እንዘርጋ! 80 ሚሊዮን ሕዝብ ባሕር በር የማግኘት ሕጋዊና ፖለቲካዊ መብት አለው!” የሚሉ ነበሩ። እነዚህ ለጆሮዬ ሙዚቃ ካልሆኑ የትኞቹ ሊሆኑ ነው? ስልክ ደዋዮቹን ያስከፋቸው የትኛው አባባል እንደሆነ ይገባችኋል?

ስዬ አብርሀ፤ ገብሩ አሥራትና ሌሎችም የቀድሞ ሕውሀት አመራር አባላት ባደረጉት ስህተት ተጸጽተው በኢትዮጵያዊነት ጸንተው ከሌሎች ወገኖቻቸው ጋር በጋራ ለመታገል እስከቀረቡ ድረስ ያላንዳች ማመንታት እቅፋችን ውስጥ ልናስገባቸው ያስፈልጋል። አንደኛው ዓቢይ የፖለቲካ ፈተናችን የወዳጅ ክበባችንን ማስፋት ነው። በተለይ ደግሞ በሥልጡን ፖለቲካና በሠላማዊ ትግል የምናምን ወገኖች እገሌን እናናጋግራለን እገሌን አናነጋግርም፤ እገሌን እንሰማለን እገሌን አንሰማም በሚል ቅሌት ውስጥ መታዬት የለብንም። ይህ ጠባይ መሳቁያና መሳለቂያ ከማድረግ አልፎ ለሀገርና ለወገን እንዳንደርስ ጠፍሮ የሚይዝ ሠንሰለት ነውና ልንበጥሰው ይገባል።

ባለፈው አርባ ዓመት በብዙ ጦርነት፤ በተደጋጋሚ የተፈጥሮ አደጋና በደካማ አስተዳደር የደቀቀች አገር ጀርባዋ ሌላ የጦርነት ዑደት ሊሸከም ይችላል ብሎ መገመት ያስቸግራል።

ለዚህ ነው አዲሱ መንገዳችን የንግግርና የድርድር መሆን ያለበት። ለዚህም ነው ያዲሲቱ ኢትዮጵያ ልጆች ያገራቸውን ጉዳይ በደመ-ነፍስ ሳይሆን በደመ-በሳልነት መመልከት ያለባቸው። ዘመኑ የንግግር የመደማመጥና የእርቅ ስለሆነ በዚህ ጎዳና ዘና ብለን ለመጓዝ የሚያስችለንን ዕውቀትና ዘዴ ለመካን እንሯሯጥ እላለሁ።

እንዴ! ንግግርና መደማመጥማ የጨዋ ወግ ነው!

Kuchiye@gmail.com
የግርጌ ማስታዎሻ። ኑዛዜው አስፈላጊ እንዳልሆነ ባውቅም ከአቶ ገብሩም ከፓርቲያቸውም ጋር ምንም ግንኙነት እንደሌለኝ ይታወቅ

Wednesday, July 30, 2008

"በርግጥ ኢትዮጵያ ላይ ሴራ አለ?"

ይህን ጥያቄ የማነሳው ያለ ምክንያት አይደለም። ጥቂት በማልለው የሕብረተሰባችን ክፍልና አልፎ አልፎም ቢሆን በተቃዋሚ ፓርቲዎች አካባቢ ሲንጸባረቅ የማየው የውጭ ፖሊሲ አዝማሚያ ስለሚያሳስበኝ ነው።

ክርክሬን አጭርና ደፋር በሆነ ዓረፍተ ነገር ልክፈትና “ታላላቅ መንግሥታት የኢትዮጵያን መጠናከርና አንድነት አይፈልጉም” የሚለው አመለካከት ከዘመናችን የፖለቲካ ጭብጥ ጋር የማይገናዘብ በማስረጃ ያልተደገፈ አጉል ስጋት ነው እላለሁ።

ከጭብጡ ጋር የማይገናዘብ ያልኩት ያለንበት ዘመን የኮሎኒያሊዝም መስፋፋትና “አፍሪካን የመቀራመት” ዘመቻ ያከተመበት መሆኑን ለማመልከት ነው። በዚያ ዘመን ኢትዮጵያን ለማዳከምና ግዛቷን ከዚህም ከዚያም ለመቦጨቅ የተጉ መንግሥታት በርካታ ነበሩ። ኢጣልያ፤ እንግሊዝ፤ ፈረንሳይ፤ ቱርክና ግብጽ ማለቂያ በሌለው ጦርነት ውስጥ ጠምደውን ለልማት የምናውለውን ውድ ጊዜና ሀብት ሰርቀውብናል። በሁለተኛ ደረጃ የሚታይ ይሁን እንጅ ግብጽና ሱዳን ዓባይ ወንዝን በተመለከተ ብዙ ይፈታተኑናል። ባካባቢው ከፍተኛ የክርስትና ሀይማኖት ተከታይ የሚገኝባት አገር በመሆኗም አንዳንድ የስልምና ሀይማኖት ተከታይ አገሮች ኢትዮጵያን በፍቅር አያይዋትም። የኋለኞቹ በየራሳቸው ችግር የተጠመዱና ከኃያላን ጋር የማይመደቡ በመሆናቸው ለጊዜው አላተኩርባቸውም።

ዘመኑ የተለዬ ነው፤
አሁን የምንገኘው ፈጽሞ ልዩ በሆነ የዓለም ፖለቲካ ድባብ ስር ስለሆነ የፈለግነውን ያህል ብንጠራጠር፤ ባለፈው በደላችን ላይ ብናላዝንና ብናቄም ላዲሱ ዓለም የኑሮ ፈተናችን የሚጠቅመን ነገር የለም። የዚህ ትውልድ አደራ በመቃ ብዕር የተጻፈና በብራና ላይ የተከተበ ሳይሆን በኮምፒውተር ግራፊክ የተቀረፀ የ21ኛው ክፍለዘመን አደራ ነው።

እራስ የሚያዞር ጥድፊያና በጀርባ የሚያርድ ተወዳዳሪ በበዛባት ዓለም የሀገራችንን ድርሻ ለመሻማትም ሆነ የክብር ቦታዋን ለማግኘት የምናደርገው ትጋት ፋታ መስጠት የለበትም። መመራመር ያለብን ያዲሱ ዓለም የፖለቲካና የኤኮኖሚ ድባብ ምን ይመስላል? በዚህ ድባብ ውስጥ ሁነኛ ተጫዋች ሆነን ለመገኘት በማሕበረሰብ ደርጃ ባቻ ሳይሆን በግለሰብ ደረጃ ምን ዝግጅት ማድረግ አለብን? በመጀመሪያና በሁለተኛ ደረጃ ከማን ጋር መሻረክ ይኖርብናል? የፓለቲካና የኤኮኖሚ ፖሊሲዎቻችን ወዳጅ፤ ካፒታልና የቴክኖሎጅ ፍሰት እንዲስቡ ምን ምቹ ሁኔታ መፍጠር አለብን እያልን ነው። ለሁለተኛ ጊዜ “በረሳነው ዓለም እንድንረሳ” መፍቀድ የራስን ሕይወት በራስ የማጥፋት ያህል ሀጢአት ይመስለኛል።

በመነሻነት ይህን ያህል ካልኩ በኋላ ተቃዋሚ ፓርቲዎች የውጭ መንግሥታትን ድጋፍ ለማግኘት፤ በተለይም ደግሞ ወሳኝ ሚና የሚጫወተውን ያሜሪካን መንግሥት ድጋፍና አመኔታ ለማግኘት ያደረጉት ጥረት አመርቂ ነበር ወይ? የሚለውን ልመልከት። መልዕክቴን በቅጡ ለማስተላለፍ ይረዳኝ ዘንድ ጥረታቸው “በቂ አልነበረም” በሚል ድምዳሜ እጀምራለሁ።

የተቃዋሚ ወገኖችና ያሜሪካ አስተዳደር መቃቃር፤
ቁጥሩ ትንሽ የማይባል የዳያስፖራ ነዋሪ፤ እንዲሁም ብዙ የፓርቲ፤ የሀይማኖትና የማሕበራዊ ድርጅት መሪዎች “ታላላቅ መንግሥታት ኢትዮጵያን በማፈራረስ ወይንም በማዳከም ሴራ ውስጥ አሉበት” የሚል አስተሳሰብ ያንጸባርቃሉ። የዚህ ሀሳብ አራማጆች በዋቢነት የሚጠቅሱት ሶማሊያ በ1974 ኢትዮጵያን ስትወር አሜሪካ የተከፈለበትን መሣሪያ አላስረክብም ማለቷን፤ እንዲሁም ወያኔ ሀርነት ትግራይ የሚባል ገንጣይ ቡድን በ1991 አገሪቷን እንዲቆጣጠር መፍቅዳቸውን ነው። ወደኋላ ከተመለስን ሌሎችም ይኖራሉ።

ይሁን እንጅ አሜሪካ ለምን እነዚህን አቋሞች እንደወሰደች፤ ይህ ደግሞ ከራሷ ብሔራዊ ጥቅም አንጻር ለምን ትክክል ነው ብላ እንዳሰበችና ፖሊሲዋ ኢትዮጵያንም ሌሎች አገሮችንም በሚመለከት ወጥነት እንዳለው መረዳት አለብን።

የ1974ቱ አብዮት የኮሚኒዝም ጽንስና የብሔርተኝነት ዝንባሌ ይነበብበት ስለነበር አሜሪካኖቹን ቢያቁነጠንጣቸው አያስገርምም ነበር። ከዚህም ሌላ ሶቪየት ዩኒየን የሶማሊያ ቆይታዋን በማቋረጥ ፊቷን ወደ ኢትዮጵያ ለማዞር እንደተዘጋጀች አሜሪካ ታውቅ ነበርና መሣሪያ መላኩን አቆመች። በዚህ ሁኔታ ለኢትዮጵያ የቀረው አማራጭ ጭልጥ ብሎ ከሶቪዬት ጉያ መግባት ሆነ።

ስለብሔርተኝነት ካነሳን አሜሪካም ሆነች ሌሎቹ ኃያላን መንግሥታት ብሔርተኝነት፤ በተለይ ደግሞ አክራሪ ዓይነቱ ብሔርተኝነት ለምን እንደሚገዳቸው መረዳት ያስፈልጋል። ብሔርተኝነት በባህርይው ገለልተኛና አትንኩኝ ባይ መሆኑ፤ አክራሪ ብሔርተኝነት በዓለም ታሪክ ውስጥ ብዙ ጥፋት ማስከተሉ፤ ከሁሉም በላይ ደግሞ አክራሪ ብሔርተኛ መንግሥት ባለበት አካባቢ የራሳቸውን ጥቅም ለማስከበር በሚያደርጉት ጥረት ውስጥ እንቅፋት ስለሚሆንባቸው ፈጽሞ አይፈቅዱትም።

ወደሁለተኛው የቅሬታ መንስዔ ልሸጋገር። ብዙ ሰዎች እንደሚያስቡት አሜሪካ ሕወሀት ሙሉ ሥልጣን እንዲጨብጥ አትፈልግም ነበር። “ሕውሀት በአንድ አነስተኛ ብሔረተስብ የተገነባ ፓርቲ ስለሆነ ሰፊ የሕዝብ መሠረት አይኖረውም፤ የኢትዮጵያ ሕዝብ ሕውሀትን የሚመለከተው እንደ ተገንጣይ/አስገንጣይ ሃይል ነውና አመኔታውን አይለግሰውም፤ ራሱ ሕውሀት ጥርሱን ነቅሎ ያደገው በአልባኒያ ኮሚኒስት ፓርቲ ሞግዚትነት ስለሆነ መልካም አስተዳደር በኢትዮጵያ ውስጥ ለማምጣቱ ምን ማረጋገጫ አለን?” የሚሉ ተጨባጭ ስጋቶችን ታስተናግድ ነበር።

የለንደኑ ድርድር፤
ከነዚህ ስጋቶች በመነሳት ነበር አሜሪካ ሕውሀትንና በመፈራረስ ላይ የነበረውን የሁለቱ ተስፋዬዎች መንግሥት (ጀኔራል ተስፋዬ ገብረኪዳንና አቶ ተስፋዬ ዲንቃ) ጥምር የሺግግር አስተዳደር እንዲያቋቁሙ ጥረት ያደረገችው። ሕውሀትና የነተስፋዬ መንግሥት ወደ ድርድር ጠረጴዛ ይዘውት የቀረቡት አቋም የተለያየ ቢሆንም ለማቀራረብ የማይቻል አልነበረም። በብዙ ጉዳዮች ላይ ስምምነት ተደርሶ በሽግግር መንግሥቱ ውስጥ የጦር ሚኒስቴርን ማን ይቆጣጠርና በሕይዎት ማጥፋት የሚጠየቁ የደርግ ባለሥልጣናት ሁኔታ በምን መልክ ይታይ የሚሉት ጥያቄዎች ድርድርሩን እንዳቆረፈዱት ይነገራል። ይህ በመካሄድ ላይ እያለ በመላ አገሪቱ በተለይም በአዲስ አበባ ውስጥ ሊፈነዳ የተቃረበ የፀጥታ ሁኔታ ተፈጠረ። አሜሪካኖቹ ለዚህ አሳሳቢ ሁኔታ ቅድሚያ ሰጡና ፀጥታ ለማስከበር የተሻለ ድርጅት የነበረው ሕውሀት ከተማዋን/ሀገሪቷን እንዲቆጣጠር ተስማሙ። “ጦሩ የተፈታውና የሕዝብ ድጋፍ ከድቶት የነበረው የነተስፋዬ መንግሥት በለንደኑ ውይይት ላይ በብልህነት ተደራድሮ ቢሆን ኖሮ ያገራችን የፖለቲካ ሁኔታ ልዩ መልክ ሳይኖረው ይቀር ነበር?” እያልኩ አንዳንዴ ራሴን አካለሁ።

ታዲያ አሜሪካኖች ለሕውሀት የሰጡት ድጋፍ ገደብ ነበረው። በኢትዮጵያ ውስጥ ዴሞክራሲ ለማምጣት ግዴታ አስገብተውና ይህን ቃል የማያከብር ቢሆን የኤኮኖሚና የዲፕሎማሲ ድጋፍ እንደሚነፍጉት አስጠንቅቀው ነው። የኸርማን ኮኸን “ኖ ዴሞክራሲ ኖ ኤይድ” ከዚህ መነጨ።
እዚህ ላይ “ሕውሀት ላሜሪካኖቹ የገባውን ቃል ሲያፈርስ፤ ጸረ ዴሞክራሲና ጠባብ ፖሊሲዎቹን ሲያራምድ ለምን ካሮታቸውን አልነጠቁትም?” የሚል ጥያቄ ቢነሳ አግባብነት አለው። ለዚህ ጥያቄ መልስ ማግኘት በዲፕሎማሲው መስክ የምናየውን ግድፈት በማጥራት በኩል ይረዳል ብዬ ስለማምን አንዳንድ ነገሮችን አነሳለሁ። ቢያስደስትም ቢያስከፋም።

አንደኛ። አሜሪካ በዓለም ዓቀፍ ደረጃ ካላት የተንሰራፋ ጥቅም፤ ኃላፊነት፤ አቅምና ትዕግሥት አንጻር ለአፍሪካ የምትሰጠው ጊዜ እጅግ አነስተኛ ነው። ስለ አፍሪካም ሆነ ስለያገሮቻችን አበጥ ያለ አመለካከት ያለን ሁሉ ያን አመለካከታችንን ጥቂት ማስተንፈስ አለብን። ኤኮኖሚያዊና ስትራቴጅያዊ ጥቅማቸው አናሳ በሆነባቸው አገሮች የዴስክ ኃላፊ አድርገው የሚመድቧቸው ግልገል ዲፕሎማቶች መሆናቸውን ስናይ በዓለም ፖለቲካ ውስጥ ያለን ቦታ የቱን ያህል የኮሰሰ እንደሆነ እንገነዘባለን።

ሁለተኛ። አሜሪካም ሆነች አውሮፓውያን ትኩረታቸውን የሚስብ አማራጭ ኃይል እስካላገኙ ድረስ ካለው መንግሥት ጋር መዳረቅን ይመርጣሉ። ለምን ብለው ጣጣ ውስጥ ይግቡ? “ተቃዋሚው የተበታተነና አብሮ ለመሥራት የማያመች ነው” እያሉ በመደጋገም ሲናገሩ የምንሰማው ለዚህ ነው። ኃያላን መንግሥታት በየትም አገር ቢሆን ጠንካራ አማራጭ ፓርቲ እንዲኖር መፈለጋቸው እርግጥ ነው። “ትራምፕ ካርድ” ይሉታል እነሱ። ዛሬ አንዱን ነገ ሌላውን ጠጋ በማድረግ ባገሪቱ ላይ ያላቸውን ፖሊሲና ፕሮግራም ያለ ብዙ ውዝግብ ለማራመድ የሚያመቻቸው አማራጭ ሲኖራቸው ነውና። አለያ የ “ስታተስ ኰ ፖለቲካ” መከተላቸውን ይቀጥላሉ።

ሦስተኛ። የዲፕሎማቲክ ፖሊሲ የሚቀረጸው በርካታ ነባራዊ ሁኔታዎች ተገናዝበው ነው። ሀቅ፤ የሞራል እሴቶችና የሕገመንግሥት አንቀጾች ብዙ ሚዛን ላይደፉ ይችላሉ። አሜሪካ በሕገመንግሥቷ ዴሞክራሲን ለማስፋፋትና ለመብት የሚታገሉ ሕዝቦችን ለመርዳት የገባችውን ክቡር ቃል ኪዳን ችላ እያለች አንዳንዴ ከአምባገነኖች ጋር ስትወግን የምናየው አምባገነኖች ስለሚጥሟት ሳይሆን ሁነኛ አማራጭ ስለምታጣ ነው።

ወደለንደኑ ጉባኤ ልመለስና ሌላ አሜሪካኖቹን ያነሆለለ አንድ ግንዛቤ ነበር። “የሕውሀት ኃይል የተገነባው ጠባብ የብሔረሰብ መሠረት ላይ ስለሆነ የሌሎች ብሔረሰቦችን ድጋፍና አመኔታ ለማግኘትም ሆነ ሁነኛ የፖለቲካ ኃይል ሆኖ ለመቆየት በዴሞክራሲ ፋና-ወጊነት የታሪክ ቦታ መቅረጽ ይፈልጋል። ከረጅም ጊዜ ጥቅሙ አንጻር ሲታይ የኢትዮጵያን ሕዝብ ባለውለታ ማድረግ “ደ!” የሚያሰኝ ጥያቄ ነው” የሚል ሎጅክ-ቀመስ ነገር ግን ገራገርነት የሚነበብበት አቋም ወሰዱ። ኸርማን ኮኸን ስቴት ዲፓርትመንትን ከለቀቁ በኋላ በጻፉት መጽሀፍ ይህ ግንዛቤ ግድፈት እንደነበረውና ሕውሀት ቃሉን ያልጠበቀ አምባገነን መንግሥት መሆኑን በምሬት ገልጸዋል።

በላይኛው የጽሁፌ ክፍል አሜሪካኖቹ ለወሰዱት አቋም ምንና ምን ታሳቢ አድርገው እንደነበር የማውቀውንና የሚመሰለኝን ያህል ላስጨብጥ ሞክሬያለሁ። ዛሬ ላይ ሆኘ ሳየው በአጭሩ ጊዜ አሜሪካ ያገሯን ጥቅም ችላ ብላ ለኢትዮጵያ ዴሞክራሲ ስርጸት መቆም ይገባታል እያልን ባደባባይ መዝለፋችን ትክክል አልነበረም፤ ያተረፍነው ነገር የለምና። በሌላ በኩል ደግሞ አሜሪካኖቹ የሕውሀት ፕሮፓጋንዳ ሰለባ ሆነው ተቃዋሚው ወገን አክራሪ ብሔርተኛ ነው፤ የደርግ ርዝራዥ ነው፤ የአማራ ስብስብ ነው በሚል አሳፋሪ የቀለም ቅብ ውስጥ መሳተፋቸው የጥፋትም ጥፋት ነበር።


ላጠቃል፤
ታላላቅ መንግሥታት በኢትዮጵያ መዳከምም ሆነ መበታተን የሚጠቀሙት አንዳችም ነገር ስለሌለ ይህን ዘመን ያፈጀ አስተሳሰብ መላቀቅ አለብን። በኤኮኖሚና በሚሊተሪ የዳበረች፤ ላካባቢው መረጋጋት አስተማማኝ ኃይልና አጋር የምትሆን ኢትዮጵያን ይመርጣሉ ብሎ ማሰብ ይበልጡን ሚዛን ይደፋል። ከዚህም ሌላ 80 ሚሊዮን ሕዝብ ሠላምና መረጋጋትን አግኝቶ የነፍስ ወከፍ ገቢውን ቢያሳድግ ታላቅ ገበያና ታላቅ ወገን ተፈጠረ ማለት ነውና አሜሪካም ሆነች ሌሎቹ አይከፉም። በአንጻሩ ደግሞ ከኢትዮጵያ መራብ ያሚተርፋቸው ነጻ የስንዴ ርዳታ ማመላለስ ብቻ ነው። ከኢትዮጵያ የእርስ-በርስ ግጭት የሚያገኙት በሚዘገንን የነፍስ አድን ዘመቻ ውስጥ መዘፈቅ ብቻ ነው።

ራዕያችን በምንመኘው ደረጃ ድጋፍ ሳያስገኝ ቀርቶ ከሆነ ጥፋቱ የኛ እንጅ የነርሱ አይመስለኝም። ራዕይ ስሜትን በሚነካ መልክ ተቀርጾ፤ በማለፊያ የዲፕሎማሲ ጥበብ ተጠቅልሎ ከተወዳዳሪ ራዕዮች በልጦ መገኘት አለበት። የዲፕሎማሲና የውጭ ግንኙነት ጥረታችን “የኛን ሀሳብ ተቀበሉን፤ የኛን ጭኸት ስሙን” ከሚለው ረድፍ ወጥቶ ለምንና በምን ምክንያት እኛ የተሻልን አማራጭ እንደሆንን፤ እንዴትስ የፖለቲካ፤ የኤኮኖሚ፤ የዕምነት፤ የስትራቴጅና የደህንነት መሥመራችን ከነርሱ መስመር ጋር እንደሚጣጣም በማሳመን ላይ ያተኮረ ሊሆን ይገባል።

በሌላ በኩል ደግሞ ራዕይና ፖሊሲ ጥቅል ስለሆኑ “ግሩም!” ከመባል ያለፈ አድናቆትን አያስገኙም። ቁምነገሩ ያለው ከዝርዝሩና ፈረንጆቹ “ብርንዶውን አሳየኝ” ከሚሉት ላይ ነውና ያፈጻጸም ፕላንና ይህን በተግባር ለመተርጎም የሚችል ሰፊ የድጋፍ መሠረት ያለው ድርጅት እንዳለን ማሳመን ግዴታችን ይሆናል።

ድጋፍ ማግኘትና አጋር ማብዛት ብዙ ሥራ፤ ብዙ ስልት፤ ብዙ አንደበተ-ርቱዕ ዲፕሎማቶች፤ ብዙ ትዕግሥትና ብዙ ሺር-ጉድ ይጠይቃል። ኃያላን መንግሥታት ሳይቀሩ አንዱ በሌላው ላይ ካልተደገፈ ብቻቸውን መቆም አይችሉምና የወዳጅ ክበባችንን በውል እናስፋ። ይህ “በራስ መተማመን” የምንለውን ክቡር መርህ የሚያኮስስ ሳይሆን ውጤታማነቱን የሚያፋጥን መሆኑንም አንሳት።

ወዘተርፈ…(የኦባማ ጉዳይ)
ሰሞኑን የኢትዮጵያ ጉብኝታቸውን ያገባደዱት ያሜሪካ ረዳት የውጭ ጉዳይ ሚንስትር ዴቪድ ክሬመር ኢትዮጵያን በተመለከተ ያሜሪካ የውጭ ፖሊሲ መሠረታዊ ለውጥ እንደማይኖረው አስገንዝበዋል። ከኦባማ መመረጥ ጋር ብዙ ተስፋ ለምናደርግ ጥሩ ማስጠንቀቂያ ይመስለኛል።

ዴቪድ ክሬመር ድረስ ሳልሄድ በጥልቅ ትንታኔውና በወዛም አቀራረቡ የሚታወቀው የኛው “ኢትዮ ፐንዲት” www.http://ethiopundit.blogspot.com/ ጁን 29 ባስነበበው ጽሑፍ ኢትዮጵያን በተመለከተ ያሜሪካ ፖሊሲ ይለወጣል ብሎ ማሰብ አደጋ እንዳለው አስጠንቅቋል። “ዴሞክራቶቹ ቢል ክሊንተን፤ ማደሊን ኦልብራይት እና ሱዛን ራይስ ከመለስ ዜናዊ ጋር የነበራቸው መሞዳሞድ በሪፐብሊካኑም አስተዳደር ቀጥሎ ቡሺ፤ ኮንደሊዛ ራይስ፤ ቪኪ ሄንደርሰንና ጀንዳይ ፍሬዘርም የመለስ አሳዳሪ ሆነው ሰንብተዋል” ይላል። በመቀጠልም “ጆን ማኬን ከዚህ የተለየ ፖሊሲ ይከተላል ብሎ ማሰብና የመለስ ደጋፊና አሁን የባራክ ኦባማ የውጭ ግንኙነት አማካሪ ሆና የምታገለግለው ሱዛን ራይስ ኦባማ በዜናዊ ላይ ፊቱን እንዲያዞር ትማጸናለች ብሎ መጠበቅ አስቸጋሪ ነው” በማለት ይደመድማል።

አዘለም አንጠለጠለም መልዕክቱ ፓርቲዎች ቢለዋወጡ እንኳ ያሜሪካ የውጭ ፖሊሲ ይህን ያህል መሥመሩን አይስትም ለማለት ነው። ገና ብዙ ሥራ ይጠብቀናል ለማለትም ነው።

kuchiye@gmail.com

Friday, July 11, 2008

“ሠላማዊ ወይስ ትጥቅ? - እንካ ስላንቲያዎቹ!”


ሰሞኑን በድሕረ ገጾች ላይ የማነባቸው አስተያየቶችና ትችቶች ሁለት ቤሳ የምታወጣ ሀሳቤን እንዳካፍል ገፋፉኝ። ግርማ ካሣ “ኢሕአዴግን ማስወገድ ወይስ መለወጥ?” በሚል፤ ፕሮፌሰር ማሞ ሙጨ ደግሞ “ሕብረትን በማስቀደም…” ሮቤል አባብያ “አንድነት ፓርቲ ለሚከተለው የሠላም ጎዳና ይሁን ብለናል” በሚሉ ርዕሶች ያስነበቡን ሰነዶች “ሠላማዊ ወይስ ትጥቅ ትግል” በሚለው ትኩስ መነጋገሪያ ንጥብ ዙሪያ የሚያንዣብቡ ናቸው። እነዚህንና ሌሎችንም ጽሁፎች በ http://abugidainfo.com/ እና በሌሎች ድሕረገጾች ማንበብ ይቻላል።

ነገሬን አጭር እና ግልጽ-ያለ ለማድረግ እሞክራለሁ። “ከንግዲህ ሠላማዊ ትግል አያዋጣም” ብለው የተነሱትና ግንቦት 7 የሚባለውን ድርጅት የፈጠሩት ወገኖች እስከትናንት ድረስ በሠላማዊ ትግል ይምሉ እንደነበር አያከራክርም። ሞኝ፤ ወረቅት፤ ቴፕና ቪዲዮ ያስያዟቸውን አይለቁምና ማስረጃዎች ሞልተዋል። የሰሞኑ እንካ-ስላንቲያ የጫራቸው ርዕሶች የቱን ያህል ነርቭ-ነክ ቢሆኑም መንገዳችንን አጥርተን ለመጓዝ በምናደርገው ጥረት ውስጥ ከፍተኛ ዋጋ ስላላቸው እንዲድበሰበሱ መማጸን ትክክል አይመስለኝም።

የግንቦት 7 ንቅናቄ መቋቋም ለምን አወዛጋቢ ሆነ?
እራሴን ፕሮግሬሲቭ ከሚባለው አምባ ልደብልና “ማንም ሰው የፈለገውን የኑሮ ወይንም የትግል ጎዳና ለመምረጥ ያለውን መብት አከብራለሁ” ልበል። የናንተን አላውቅም እንጅ አንዳንዴ ይህ አባባል ስድ ፍካሬ ሆኖ አገኘዋለሁ። ግለሰቦች እራሳቸውን ብቻ የሚመለከት የሕይወት ምርጫ ቢያደርጉ የሚጠቅሙትም የሚጎዱትም ያው ራሳቸውን ብቻ ስለሆነ ለዚህ ዓይነቱ ምርጫ ቁብ ሊኖረን አይገባም። ከግለሰብ አልፎ ማሕበረሰብንና ሀገራዊ እንቅስቃሴን በሚነካ ጉዳይ ላይ የሚደረግ ውሳኔ ግን ጉዳያችን ይሆናል።

ከዚህ አንጻር የሕዝብን አመኔታና አደራ የተቀበሉ መሪዎች የሚያደርጉት ውሳኔ የተከታዮቻቸውን ፍላጎትና ይሁንታ ማግኘት እንዳለበት አያከራክረንም። ግልጽነትና ተጠያቂነት መመሪያዎቻችን ይሆናሉ ብለው ምህላ ፈጽመውልናልና። “ሠላማዊ ወይንም ትጥቅ” በሚል ዓቢይ ጥያቄ ላይ አንድ ወይንም ሁለት ሰዎች ሆነው ውሳኔ ካደረጉ በኋላ የይስሙላ ወረቀት በትነው “ኑ ተከተሉን!” ቢሉ ለሕብረተሰቡ ያላቸውን ንቀት ከማንጸባረቅ በስተቀር ሌላ የሚያመላክተው ነገር የለም። የሀይሉ ሻውል ችግር ይህ ነበር፤ ከልክ በላይ ወጠርከው አትበሉኝና መለስ ዜናዊና ሥዩም መሥፍን ከሱዳን ጋር ያደረጉት ስምምነትም ከዚህ አሠራር ብዙ የተለዬ አይደለም።

እንዲመራኝ የምመኘው ሰው፤ ይልቁንም ደግሞ ድጋፌን የሚሻ ፖለቲከኛ በራዕይ ጥራት፤ በሀቀኝነት፤ በመልካም ስነምግባርና በታማኝነት ባህርዮች የታነጸ እንዲሆን እፈልጋለሁ፡፡ ከዕብሪትና ከመሠሪ ጠባዮች የጸዳ እንዲሆን እፈልጋለሁ። ባስቀመጥሁት ቦታ እንዳገኘው እፈልጋለሁ። ዛሬ እዚህ ነገ እዚያ የሚሉ ሰዎች የምይዘውንና የምጨብጠውን ያሳጡኛልና ቀልቤ አይቀበላቸውም።

አንደኛው የግንቦት 7 መሪ “ሠላማዊ ትግል ከንቱ ነው” ከሚለው ድምዳሜ ላይ የደረሱት እስር ቤት እያሉ እንደነበር ሰምተናል። ይህ ከሆነ ደግሞ በሰላማዊ ትግል ከሚያምነው የቅንጅት አመራር ጋር በአሜሪካን አገር መድረክ መቋደስ አልነበረባቸውም። የጉዞ ፕሮግራሙ መገባደጃ ድረስ ይህን ያህል ግዙፍ ምስጢር ከትግል ጓዶች ደብቆ ማቆየት መልካም የማኔጅመንትና የወዳጅነት ባህርይ አይነበብበትም።

የመሪዎች ባሕርይ ሊቆረቁረን ይገባል ወይ?
ፈረንጆቹ በጣም ሊቆረቁረን ይገባል ይላሉ። መሪ ልሁን ብሎ የሚነሳን ሰው ከነአስተዳደጉ፤ ከነመሠረታዊ ዕምነቶቹ፤ ከነታሪከ ምግባሩ አበጥሮ ማወቅ ወደፊት ሊከሰት ከሚችል አደጋና ፀፀት ይሰውራል - ሙሉበሙሉ ባይሆንም በጅጉ ይሰውራል። ለነገሩ ይህ ብልህነት የፈረንጆች ብቻ አይደለም። ያገሬ ሰው በሲራራ ነጋዴነት አብሮት የሚዘምትን ሰው እንኳ በቅጡ ካላጠናው ከቤቱ አይወጣም። ይችን ያህል ብልህነት እንዴት አጣን?

ለመሪነት የምናጫቸውን ሰዎች በቅጡ መመርመር ነውር የለውምና ይህን ለማድረግ ወኔው ሊኖረን ይገባል። ይህን ሳናደርግ እየቀረን ስንት ጊዜ እንደተበለጥን የቅርብ ጊዜ ትዝታችን ነው። ሞኝን እባብ የነከሰው ሁለቴ ነው ይባላል። አንዴ እባብ ምን እንደሆነ ሳያውቅ አንዴ ደግሞ ከልምዱ ባለመማሩ።

ሁለቱ ተጻራሪ ሀሳቦች ጎን ለጎን የመሄድ ዕድላቸውስ?
ብዙ አይመስለኝም። ግንቦት 7 ንቅናቄውን ከማወጁ በፊትና በኋላ በአባልነት ለመመልመል ሲባጅ የከረመው በሰላማዊ ትግል ዙሪያ የተሰባሰቡትን የቀድሞውን ቅንጅት ያሁኑን የአንድነት ፓርቲ ደጋፊዎች ነው። እዚህም ላይ ትንሺ መሰሪነት ይታየኛል። ባንድ በኩል ለአንድነት መልካሙን ሁሉ እመኛለሁ እያለ የትብብር ዘንባባ ይዘረጋል። በሌላ በኩል ደግሞ “ሠላማዊ ትግል በተባለው ርዕዮት ቀመስ ትብትብ የታነቀ ትግል” (አንዳርጋቸው ጽጌ) ማካሄድ ፋይዳ ቢስ ነው እያለ የሚሊዮኖችን ዕምነት ያንኳስሳል።

የ1997ቱ የዴሞክራሲ መስኮት ገርበብ ብሎ ከመከፈቱ በፊትም ሆነ ከዚያ በኋላ በነበረው የፖለቲካ መልክዓ ምድር ውስጥ ሕዝብን ማደራጀትና ለዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ማብቃት ይቻላል ብለው የታገሉ ሰዎች ዛሬ ምን ሀሳባቸውን ሊያስለውጣቸው እንደሚችል አይገባኝም። የኢሕአዴግ ባሕርይ ትናንትም ዛሬም አንድ ነው። በጎሳ ላይ የተመሠረተ ፖለቲካ የሚያራምድ፤ የአብዮታዊ ዴሞክራሲ በሽታ የተጠናወተው፤ ዴሞክራሲያዊና ሰብአዊ መብቶችን የሚረግጥ መንግሥት ነው።

ይህን ሁሉ እያወቅን ነው ሥርዓቱን በሠላማዊ ትግል መለወጥ እንችላለን ብለን የተነሳነው። የ97ቱ የዴሞክራሲ ቀዳዳ የተከፈተው ሕዝብ፤ ፓርቲዎች፤ ነጻው ፕሬስና ዓለም አቀፉ ሕብረተሰብ በኢሕአዴግ ላይ ባሳደሩት ተጽዕኖ ነበር። ኢሕአዴግ የተከፈተውን ቀዳዳ ዘግቶ ለማቆየት የሚያስችል አቅምና ምቹ የፖለቲካ ምልክአ ምድር እንደሌለው ማመን አለብን። ሕብረተሰቡ መሀል የሰፈነ የሚመስለው ዝምታ አንድ የፖለቲካ ወይንም የኤኮኖሚ ቀውስ ሲፈጠር የሚለወጥ ነው። እየተደራጀና እያደራጀ በሕዝብ መሀል የሚቆይ ፓርቲ መኖሩ ለቀውጢዋ ቀን ያስፈልጋል።

የትጥቅ ትግል ከማይመረጥበት ምክንያቶች
የትጥቅ ትግል ኮሎኒያሊስቶችንና አምባገነኖችን ለማስወገድ በአማራጭነት ያገለገለው ዓለም በሁለት የፖለቲካ ማዕዘኖች በተከፈልችበት ዘመን ነበር። ለዚያውም ቢሆን አንድን አምባገነን በሌላ አምባገነን ከመተካት ያለፈ ፋይዳ አልነበረውም። ፋይዳ አስገኝቶ ከሆነም ከስንት አንድ ነውና ጂኦ-ፖለቲካው በተለወጠበት ባሁኑ ዘመን እንዳማራጭ መታየቱ ብልህነት ይጎድለዋል።

ሌላም አለ። ጎረቤት አገሮች መጠለያ መስጠት በማይፈልጉበት ዘመን፤ ከራስ ፀጉር የበዛ ሰላይ በከተማና በገጠር ነዋሪው መሀል ተሰግስጎ ባለበት ጊዜ፤ እልቆ መሳፍርት ያለው፤ በዘመናዊ መሣሪያና በሳተላይት መገናኛ የታጠቀ ሠራዊት በሚርመሰበስበት ሁኔታ፤ ምዕራባውያንና የቻይና መንግሥት እሹሩሩ የሚሉት ታዛዥ መንግሥት በነገሠበት ሁኔታ ለትጥቅ ትግል ምቹ አየር ያለ አይመስለኝም። እነዚህ የማያመቹ ሁኔታዎች የሚለወጡት መንግሥትን መውጫ ቀዳዳ የሚያሳጡ ኤኮኖሚያዊ፤ ወታደራዊና ፖለቲካዊ ቀውሶች ሲገኑ ነው። ያኔ የፖለቲካው ሜዳ የለወጣል።

ሳላነሳ ማለፍ የማልፈልገው ሌላ ነገርም አለ። በትክክል ገብቶኝ ከሆነ ግንቦት 7 የትጥቅንም የሠላማዊ መንገድንም የሚከተሉ ፓርቲዎችን አስተባብሬ ኢሕአዴግን አስወግዳለሁ የሚል ዓላማ ያለው ይመስለኛል። የትጥቅ ትግል ያካሂዳሉ ከሚባሉት መሀል ደግሞ ኦነግና ኦብነግ ሳይኖሩበት አይቀርም። ታዲያ እነዚህ ሁለት ድርጅቶች በኢትዮጵያ አንድነት የማያምኑ መሆናቸው ሲታወቅ ከነርሱ ጋር ማሕበር መጠጣቱ ለምን ግብ ነው? ኤኤፍዲ በተመሳሳይ ዓላማ ሲቋቋም ሁለቱን ድርጅቶች ወደ መሃል ማምጣት ይቻላል በሚል ታሳቢ እንደነበር ትዝ ይለኛል። የሁለት ዓመት ዕድል ተሰጥቷቸው ካቋማቸው ትንሽ እንኳ ፍንክች የማለት አዝማሚያ አለማሳየታቸው እንድንጠረጥራቸው አያደርገንም?

ይህንኑ ክርክር ልቀጥልበትና፤ የኢሕአዴግ መንግሥት በግንቦት 7ም በኦነግም በኦብነግም የትጥቅ ትግል (በአመጽ) ይወገድ እንበል። አመጹ በሚያስከትለው ትርምስ ውስጥ ኦነግና ኦብነግ ለዓመታት ሲያልሙ የነበረውን የመገንጠል ሀሳብ ቢያውጁ ማን ያቆማቸዋል? ይህ ዓይነቱ ትግል በሚፈጥረው ቀውጢ ውስጥ የኢትዮጵያን አንድነት የሚያስከብር የተማከለ ሠራዊ እንደማይኖር ከወዲሁ መገመት አያዳግትም።

ከሁለት ገጽ በላይ ላለመጻፍ ለራሴ የገባሁትን ቃል ስላፈረስኩ ይቅርታ በመጠየቅ እዚሁ ላይ አቆማለሁ። አይደግመኝም።

Kuchiye@gmail.com

Thursday, June 26, 2008

"የቅራኔ መፍቻ ዘይቤያችን ችግር አለው ወዳጄ!"

ጥንታዊነት ህዝቦችን የሚያስተሳስር ድርና ማግ የመፍተል ችሎታ ያለውን ያህል በአንጻሩ ደግሞ በጎሪጥ የሚያስተያይና ውስብስብ ቁርሾ ጥሎ የማለፍ መዘዝም አለው።

ቅራኔዎቻችንን ፈትተን ወደተረጋጋ የልማት እንቅስቃሴ መጣደፍ አለብን የምንል ሁሉ በሚያስትሳስሩን ድሮች ላይ መደስኮሩን ቀነስ አድርገን ለስጋቶቻችንንና ለቁርሾዎቻችን መነሻ የሆኑትን የታሪክ ጭብጦች አፍጠርጥረን በማውጣት ለጠረጴዛ ዙሪያ ውይይት መዘጋጀት አለብን። እስካሁን እንዳየሁት የቅራኔ ፍች ጥረቶቻችን ወይንም ሃቀኝነት የጎደላቸው፤ ወይንም ብልሀቱ የጠፋቸው ነበሩ።

የጁዲዮ-ክርስቲያኑም የእስልምናውም የሀይማኖት መሠረታችን ነገርን ጠበቅ አርጎ የማየት በህርይ አለውና ብዙዎቻችን ዓለምን የምናያት በጽድቅና በኩነኔ፤ በብርሀንና በጨለማ፤ በበጎና በክፉ፤ በበዳይና በተበዳይ እየፈረጅን ነው። መሃል ላይ ሌላ ውብ ዓለም እንዳለ መቀበል ያዳግተናል። በማህበረሰብም በግለሰብም ደረጃ ይህ አመለካከት ከተንጸባረቀ የሚገልጸው ኋላቀርነታችንን ነው።

ስለ ዘመናዊ ቅራኔ መፍቻ (ኮንፍሊክት ሬዞሉሽን) ዘዴዎች አንዳንድ ነገር ከማለቴ በፊት ከወዲሁ ግልጽ የማደርገው ነገር የ “አንተም ተው አንተም ተው” ባህላዊ ሺምግልና ጊዜው ያለፈበትና ጊዜን አባካኝ መሆኑን ነው። ፕሮፌሰር ኤፍሬም ይስሀቅ የባህላዊው ሽምግልና ደቀ-መዝሙር መሆናቸውን ስለማውቅ ከኔ ጋር ባይስማሙ አልደነቅም። የሀያ አንደኛው ክፍለዘመን ችግር ሊፈታ የሚችለው በሃያ አንደኛው ክፍለዘመን ዘዴዎች መሆን አለበት ለማለት እንጅ ለባህላችንም ለፕሮፌሰር ኤፍሬምም ከበሬታ አለኝ።

የቅራኔ መነሻዎች
-ሳይፈቱ የቆዩ ቅራኔዎች ወይንም ቁርሾዎች
-ለክብር፤ ለሥልጣንና ለዕውቅና ያለ ፍላጎት ሳይሟላ ሲቀር። (እነዚህን ፍላጎቶች በሠላማዊና -ገንቢ በሆነ መንገድ ለማሟላት ሳይቻል ሲቀር)
-የህልውና፤ የሥልጣን፤ የንብረት፤ የግንኙነትና የመሳሰሉት ገደቦች በግልጽ ሳይቀረጹ ሲቀር ወይንም በቂ መስለው ሳይታዩ
የቅራኔ መፍቻ ዘዴዎች
-የግንኙነቶችን ዳር ድንበር በግልጽ መከለል ከሌሎች ጋር ያለን ግንኙነት ወግ እንዲኖረው ያደርጋል።
-የራስንም ሆነ የባላንጣን ፍላጎት በቅድሚያ አንጥሮ ማወቅ ወደድልና ወደስምምነት ያመራል። የራስን ጥቅምና ምኞት ሳይጎዱ የባላንጣን ፍላጎት ለማቻቻል በአርምሞ ማሰብ ተገቢ ነው።
-ግልጽ ጠቀሜታ ከማይታይበት የስምምነት ሀሳብ ውጤት መጠበቅ አይቻልም። ሌላውን ወገን ምን እንደሚያጓጓው ማወቅና ትብብሩን የሚመጥን ማካካሻ ማውጠንጠን ብልህነት ነው።
-የሌሎችን ስጋት ሲቻል የሚያጠፋ አለያ ደግሞ የሚቀንስ አስታራቂ መንገድ ማሰላሰል ትልቅነት ነው።
-በድርድር ጠረጴዛ ላይ የዕብሪት፤ የስጋት፤ የሺንፈትና የብልጣ-ብልጥነት መንፈስ ከተንጸባረቀ ጥረቱ ውጤት አልባ ይሆናል። የትብብርና የመከባበር ዓየር ሊፈጠር ይገባል።
-ሁሉም አሸናፊ የሚሆንበት የኃይል ሚዛን መቀየስ አስተውይነት ነው።
-አሉታዊና አወንታዊ ውጤቶችን ከበቀል ነፃ በሆነ መንገድ የሚቀበል ባህል መዘርጋት
አቋምን ለመቀየርም ሆነ ለማስተካከል የሚያበረታታ የ “ክፍት በር” ፖሊሲ ማዳበር

ስለ ዘመናዊ የቅራኔ አፈታት ዘዴዎች ለማወቅ በየቦታው የቃረምኩት እውቀት በርካታ ነው። ያነበብኳቸው ታሪኮችም ጉደኛ ናቸው። ታዲያ በሁለት ገጽ መጣጥፍ ማጠቃለል አይቻልምና እንዲች ብየ አልሞክረውም። ትንሽ ዕውቀት አደገኛ ናት እንዲሉ የለቃቀምኳትን ዕውቀት አንግቤ ነገር ማውጠንጠን ጀመርኩ። ከቶ የኢሕአዴግ ችግር ምንድነው አልሁ። ምን ቢሆን ነው እንዲህ በርጋጊ፤ እንዲህ ቁጡ፤ እንዲህ ተጠራጣሪ፤ እንዲህ እብሪተኛ የሆነው? የሚለውን። አቶ አዕምሮ እንዲህ ሲል መለሰልኝ ስለ ኢሕአዴግ ስጋቶችና ፍላጎቶች….

የኢሕአዴግና የመለስ ዜናዊ ስጋቶች
-የአነስተኛ ብሔረሰቦች መብትና ጥቅም በታላላቅ ብሔረሰቦች ይዋጣል
-ዴሞክራሲ የቁጥር ድምር ውጤት ስለሆነ አነስተኛ ብሔረሰቦች የስልጣን እርካብን መርገጥ ይሳናቸዋል
-የአነስተኛ ብሔረሰቦች ቋንቋና ባህል በታላላቅ ብሔረሰቦች ቋንቋና ባህል ይዋጣል
-የትግራይ ሕዝብ በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ የነበረው ቦታ ይኮስሳል
-የትግራይ ሕዝብ ባለፉት 40—50 ዓመታት የደረሰበት ጉስቁልና (ግስቁልናን ለትግራይ ብቻ ማን እንደሰጠው ባላውቅም) እንዳይደገም ማረጋገጫ ይፈልጋል
-በኤርትራ መገንጠል፤ አሁን ደግሞ ለሱዳን በተሰጠው መሬት ላይ ተጠያቂነትን ይፈራል
-በኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት በከንቱ ለጠፋው ሕይወት ተጠያቂነትን ይፈራል
-የትግራይ የልማት፤ የንግድና የኢንዱስትሪ ድርጅቶች በመንግሥት አድሎዋዊነት ያጋበሱት ሀብት ይወሰዳል ብሎ የሰጋል
-ለመንበሩ ቀረብ ያሉ የትግራይ ተወላጆችና ሌሎች ዳረጎተኝች በአጭር ጊዜ ውስጥ ያጋበሱት ሀብት አደጋ ላይ ይወድቃል ብሎ ይሰጋል
-ቅንጅት/አንድነት ፓርቲ በመላ አገሪቱ ውስጥ ተቀባይነት ማግኘቱ የኢሕአዴግን የፖለቲካ ጭብት ያመነምነዋል ብሎ ይፈራል
-ካላቸው የሕዝብ ብዛት አንጻር የአማራና የኦሮሞ ፓርቲዎች ትብብር ለሕውሀት/ኢሕአዴግ አስቸጋሪ የፖለቲካ ዘመን ያመጣል ብሎ ይሰጋል

የኢሕአዴግና የመለስ ዜናዊ ፍላጎቶች
-አነስተኛ ብሔረሰቦች (ስጋቶች እስኪጠፉ ድረስ) እኩል ሚና እንዲኖራቸው የሚያደርግ የፖለቲካ ድርድር
-ወያኔ አርነት ትግራይና የትግራይ ክልል በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ ዓቢይ ቦታ ይዘው እንዲቆዩ ማድረግ። የይገባኛል አበሳ
-በአንጻራዊ ደረጃ ያልዳበረ የልማት መሠረት ያላቸው አካባቢዎች ፕሪፈረንሻል ትሪትመንት እንዲኖራቸው ማድረግ
-በወያኔ አገዛዝ ዘመን ለተካበተ ድርጅታዊና ግለሰባዊ ሃብት ማረጋገጫ ማግኘት
-በወያኔ ዘመን ለተወሰዱ ውሳኔዎች ከተጠያቂነት የሚያድን ማረጋገጫ
-መለስ ዜናዊ የኢትዮጵያ የዴሞክራሲ ሥርዓት አባት የመባል ምኞት
-መለስ ዜናዊ የአዲሲቱ አፍሪካ ባለራዕይ ተብሎ የመሰየም ጉጉት
-መለስ ዜናዊ ከ 2005 ምርጫ በኋላ ያጣውን የታላላቅ መንግሥታት እቅፍ ማግኘት

ካለው መንግሥት ጋርም ሆነ በተቀናቃኝ ፓርቲዎች መሀከል ያሚታየውን አለመግባባት ለመፍታት የፖለቲካ ድርድር አያልፉት ዓይነት አባዜ ነው። ጽሁፌን ከሁለት ገጽ ላለማስበለጥ ለራሴ የገባሁትን ቃል ማክበር አለብኝና በዚህ ጎዳና እንጓዝ ካልን መጠየቅ ካለባቸው ጉዳይች አንዳንዶቹን በግርድፉም ቢሆን አቅርቤያለሁ። ውይይት ከፈለጋችሁ በሩ ክፍት ነው።

kuchiye@gmail.com

Thursday, June 19, 2008


"Yes, UDJ’s birth is significant!"


In a country where abuse of power and gross incompetence surpass hitherto unseen proportions, it is crucially important Ethiopians get leadership of a resident political party that they can trust. The June 17, 2008 General Assembly of Andnet (UDJ) gave them exactly that.

Technically speaking, June 17 did not herald the birth of a brand new party - the whole world including EPRDF knows that. What it did is proclaim the re-birth of Kinijit, the renaissance of a popular movement that was cut short by the unwise and still paranoid tendencies of a government that is at odds even with its own interests.

Popular movements have this thing that unsettle tyrants, even more so when they are organized under the banner of peaceful struggle. Look, for example, at EPRDF who used the silliest pretext to disrupt the UDJ GA meeting of June 14. If its leaders had a semblance of wisdom or a shred of commitment for the advancement of democracy in Ethiopia, they would have stepped in and let the GA proceed scoring some points for the benefit of their international backers who they care very much about. EPRDF’s silly action gave us a couple of clues on its fears . One, it is afraid UDJ will fall into the popular embrace of Ethiopians once again. Two, it is uncomfortable with a viable opposition from inside which could turn into a pain in the neck. Three, there will be a revival of pressure on EPRDF from international donors as UDJ escalates its peaceful ways. Four, with the worsening economic and political situation in Ethiopia, the opposition will have compelling reason to work under a minimum platform and increase the pressure on the government.

EPRDF’s attempt at disrupting the GA also ended up further energizing the spirit of the assembly participants, unsettling the diplomatic community, angering the general population and exposing the vulnerability of a government that tries so hard to portray images of a macho man.

There is a certain truth that any action by EPRDF or the dictates of the international community will never change. Ethiopians are determined to see their fight for democracy and good governance succeed no matter what the cost is and no matter how long the journey takes.


UDJ will stay the course of peaceful struggle and conduct its program in a much more organized manner. It will work for lasting victory guided by well-considered short and long term goals. It will leave no stone unturned to bring about national consensus and national reconciliation. It will stay vigilant and fight threats that work against the unity and territorial integrity of the country.


UDJ will be by the side of the drought victim, by the displaced citizen, by the side of the young and the old that suffer from a justice system that fails to serve the interest of all Ethiopians. It will be by the side of Ethiopians anywhere and everywhere. It will organize the people under the hallowed banner of democracy, justice and national unity confident that the general population, its members and leaders are behind it.

Yes, UDJ’s rebirth is significant!


kuchiye@gmail.com

Wednesday, June 11, 2008

"Salute to Kinijit, Andnet, Kinijit!"


Forward with Andnet!
As a party that sprung up at a momentous phase in Ethiopian history, there is no doubt in anybody’s mind that the Kinijit movement ushered an entirely new era in the way we look at politics and politicians. Reason rather than rhetoric, reconciliation rather than protracted conflict, unity rather than fragmentation became lingua franca of choice. Parties who found themselves trapped in the bygone days of sloganeering and empty rhetoric lost both respect and followers.

After decades of gridlock, the country and its people wanted to see fresh and forward looking direction. That was what Kinijit offered and that was why millions followed it. Kinjit elaborated on the political, economic and social realities of the country like no other party in the past. Its approach was as candid as it was constructive.

The party’s vision was, and still is, based on the ever so exact premise that what really matters in this day and age is today and the future rather than the past. No country that volunteered to be prisoner of its past was ever able to break the shackles of poverty or conflict and usher an era of stability and wealth. As they say, the past is only as good as we can derive lessons from.

Unjustified but understandable frustration
Given our long unfulfilled dream for an Ethiopia where human and democratic rights are respected and where the people are endowed with good governance, it is not difficult to comprehend why many grow impatient and take respite on the sideline following a political hiccup the like of which was experienced by Kinijit. However, we should not lose sight of the fact that winning democracy and building a stable society necessarily requires travel through arduous roads - with lots of bumps twists and turns on the way. Remembering this painful truth will guard us from undue frustration and from an ever looming withdrawal syndrome.

“Our greatest glory is not in never falling, but in rising every time we fall”. I will never get over this omnipresent Confucian proverb.


Continued involvement in Andnet
The greatest gift we can give to 80 million compatriot Ethiopians and the lasting memorial we can erect to those who paid in dear life during the 2005 atrocity, is by pledging to continue our involvement at levels of our individual choice. No amount of propaganda aimed at portraying Kinijit as a fractured organization should break our will. What Kinijit has to go through the last two years can only be considered a minor set back that will be rectified as soon as the party finalizes its regrouping effort and starts to operate through the length and breadth of the country. Despite the massive effort of the government aimed at infiltrating and dividing the party, despite the elaborate intimidation targeting Kinijit’s supporters and despite the relentless campaign to paint the party in all kinds of shades, Kinijit and its vision remain deeply engrained in the blood system of Ethiopians. You just can’t erase a popular spirit, can you?

Blessed are those..
Any nation will be considered blessed when it is bestowed with leaders who not only understand the arduous nature of democratic struggle, but are also willing to put their own lives and the lives of their loved ones in harms way in pursuit of the dreams of millions. That is exactly what most of Kinijit’s leaders chose to do; first by prevailing over a traumatic prison experience, then by deciding to regroup and continue with the peaceful but always dangerous struggle. In my book, this is “paying the ultimate sacrifice”. These, in my book, are the real heroes.

How about the name “Andnet”?
For me and for many others it is the story of the “Silicha” and the “Qelqelo”. I saw wisdom in the leader’s decision to change the party’s name so the struggle could forge ahead without further delay. By so doing, they foiled EPRDF’s trap which was aimed at bogging the party in a Kangaroo court battle where the winner will always be EPRDF. True to its principle, Andnet will demonstrate to our citizens and to the world at large that that the peaceful struggle will continue even as the repression tightens and the political environment gets more suffocating.

The re-inauguration of Kinijit as Andnet will create a vitally necessary impetus the democratic struggle so desperately yearns. Andnet will remain in the face of EPRDF, will expose the government’s excesses, will show the way, will serve as a shining star in a country where the large majority of the population lives under looming draught, war and unparalleled economic and political hardship.

We salute the General Assembly of “Andnet for Democracy and Justice Party”, its participants and the Ethiopian people at large on yet another milestone that will be spearheaded by a party that has grown wiser and stronger. June 14, 2008 will be yet another landmark in Ethiopian politics.

Kuchiye@gmail.com

Monday, May 05, 2008

"ችግሩ የማኔጅመንት ነው ወዳጄ! "

ኋላቀር አገር ብሎ የለም፤ በማኔጅመንት ያልታደለ እንጅ”
ይህ ጊዜ የማይሽረው አባባል ፒተር ድራከር የተባለ አሜሪካዊ የማኔጅመንት ጠቢብ
የተመራመረበት ነው። የፖለቲካም ሆነ የልማት ጥረታችን ክስረት ሰበቡ ምን ይሆን እያልኩ ሳሰላስል ነው ፒተር ድራከር ትዝ ያለኝ።

እስኪ ልብ እንበል። በተፈጥሮ ሀብት የተንበሸበሹ ሆነው ኋላቀርነት በሚያስከትለው መዘዝ
የጦርነት፤ የአፈና፤ የበሽታና የድንቁርና ሰለባ የሆኑ አገሮች ስንት ናቸው? በኛው ክፍለ ዓለም እንኳ ዛዬርን፤ አንጎላን፤ ናይጀሪያን፤ ሱዳንን መጥቀስ ይቻላል። ዘይት እንደጉድ
የሚገነፍልባቸውና አንዷን በርሜል በ$120 ዶላር የሚቸበችቡ እንደ ሳውዲ፤ ኩዌት፤ ኢራን፤ ኢራክና ቬነዙዌላ የመሳሰሉ አገሮች አሁንም የሚመደቡት እንደኋላ ቀር አገር ነው።

በሌላ በኩል ደግሞ የተፈጥሮ ሀብት ሳይኖራቸው ባዳበሩት የመኔጅመንት አቅምና በደረሱበት የልማት ደረጃ ብቻ ከበለጸጉ አገሮች የሚመደቡ እንደ ሆንግ-ኮንግ፤ ሲንጋፖር፤ ደቡብ-ኮርያና ታይዋን የመሳሰሉትን መጥቀስ ይቻላል። ቁምነገሩ ያለው እዚህ ላይ ነው። የኢንዱስትሪ፤ የአገልግሎትና የመልካም አስተዳደር መሠረቶች ያልዳበረበት አገር ቀጣይና የተረጋጋ ሕይወት ሊኖረው ስለማይችል እንደ በለጸገ አገር ሊቆጠር አይችልም። ስለሆነም የማኔጅመንት ባሕል ባልዳበረበት ሕብረተሰብ እድገትንም ሆነ አሸናፊነትን በርግጠኝነት መጠበቅ አይቻልም ማለት ነው። በፖለቲካው መስክም አሸናፊ ሆኖ ለመገኘት የዳበረ የማንኔጅመንት ሙያን ይጠይቃል።

ትምሕርት ያለ ሥራ ልምድ?
ይህን ካልን ደግሞ የኢንዱስትሪ፤ የአገልሎትና የመልካም አስተዳደር ዘርፎች መዳበር ከየት ይመነጫል የሚለውን መጠየቅ ተገቢ ይሆናል። ወዲያውኑ በአእምሮአችን የሚመጣው“ትምሕርት”ቢሆን አያስገርምም። እዚህ ላይ ታዲያ አንድ የግንዛቤ ችግር አይጠፋም። ትምህርት የጽንሰ ሀሳቦች መሠረትና የመተንተን ችሎታን የሚያላብስ ምትክ-የለሺ እሴት ቢሆንም በሥራው ዓለም ካልተለበለበና የመታረቅ እድል ካልገጠመው ብዙ ፋይዳ አያስገኝም። ይህ ብቻ አይደለም። የተማረ ሰው እውቀቱን በማያቋርጥ የሥልጠና ፕሮግራምና በንባብ ካላደሰ ዱልዱም ቢላዋ የመሆን አሳዛኝ እድልም ይገጥመዋል። ለዚህ ነው በሰለጠነው ዓለም ዩኒቨርሲቲዎች፤ ኮርፖሬሽኖችና የመንግሥት አስተዳደር ዘርፎች ባለሙያዎችን እንደተውሶ እቃ የሚለዋወጧቸው። አሜሪካ የዓለማችን የማኔጅመንት እውቀት መናገሻና ተወዳዳሪ ያልተገኘላት የኤኮኖሚ ኃይል የሆነችውም በዚህ ፈር-ቀደደ ባህሏ ነው ።

አነሳሴ ለተደጋጋሚ የፖለቲካ ክስረታችን ስበቡ የማኔጅመንት አቅም አለማዳበራችን እንጅ
የርእዮት ወይንም የራእይ ማነስ አይደለም የሚለውን ለማመላከት ነውና ወደዚያ ከመሸጋገሬ በፊት ማኔጅመንት ለመሆኑ ምንድነው የሚለውን ልዳስ።

ማኔጅመንት ባጭሩ።
የማኔጅመንት ችሎታ ከተፈጥሮ የሚታደል ፀጋ የሚመስላቸው ቢኖሩም ሀቁ ይህ አይደለም። ማኔጅመንት በትምህርትና በስልጠና የሚገኙ ቴክኒካዊ፤ ቴክኖሎጅያዊና ስነ-አእምሮዋዊ ብቃቶችን፤ እንዲሁም በተግባር የተፈተነ ልምድን ይጠይቃል። በማኔጅመንት ሙያ ውስጥ የሚጠቃለሉት ተግባሮች ፈታኝና ውስብስብ ናቸው። ከነዚህ መሀከል፤ ሊደረስበት የሚችል እቅድ መንደፍን፤ ወደ እቅዱ የሚያደርሱ ስትራቴጂዎች ማውጣትን፤ የሰውና የማቴሪያል አቅም አሰባስቦ በብልሀት መጠቀምን፤ ችግሮች ሲከሰቱ ከስሜታዊነት ነጻ በሆነ መንገድ ተንትኖ ሲሆን በአሸናፊነት ካልሆነ ደግሞ ጉዳትን ባላበዛ መልኩ ችግሮቹን ፈትቶ ወደፊት መቀጥልን፤ ከተወዳዳሪዎች ጋር በጥቅም የሚያጋጭ ሁኔታ ከተፈጠረ ሁሉንም አሸናፊ በሚያደርግ ቀመር መፍታትን፤ በእቅድ ዘመን አንጓዎች ላይ ያፈጻጸም ምዘና እያካሄዱ የርምት ርምጃ መውሰድንና ከዛሬው የጥድፊያ ሥራ
ባሻገር እያማተሩ ሊከሰቱ የሚችሉ ፈተናዎችንና እድሎችን በቅድሚያ ተንብዮ ከወዲሁ ዝግጅት ማድረግን ያጠቃልላል። ስለሆነም የኢንዱስትሪ፤ የአገልግሎትና የመልካም አስተዳደር መዳበር የማኔጅመንት ብቃት መዳበር ውጤት ነው ማለት ይቻላል። የፖለቲካ ውጤታማነትም እነደዚሁ። ከዚህ አንጻር በIትዮጵያ የፖለቲካ ታሪክ ውስጥ ፓርቲዎችንና አገርን የመምራት እድል የገጠማቸውን ልሂቃን ስንመረምር ሁለት ጉድለቶች እናይባቸዋለን። አንድም የቴክኒክና የታክኖሎጅ ክህነት ያላገኙ ነበሩ፤ አንድም ደግሞ ትምህርቱ (ቴክኒክና ቴክኖሎጅው) ኖሯቸው በውነተኛው የተግባር ዓለም ውስጥ ድርጅት መርተው፤ ተለብልበውና በልምድ ዳብረው የወጡ አልነበሩም። ከ60ዎቹ ወዲህ የመጡትን ነጥለን ብናይ ደግሞ ወይንም ተማሪዎች፤ ወይንም አስተማሪዎች፤ ወይንም ደግሞ ወታደሮች ነበሩ።

ችግራችን ፈጽሞ የራዕይ እጥረት አይደለም!
ለሀገራችንና ለሕዝባችን ከምንመኘው Aንጻር ሲታይ ራእይ ገዶን አያውቅም። ከቅርብ ዘመን መሪዎቻችን ብንነሳ እንኳ ዮሐንስ፤ ቴዎድሮስ፤ ምኒልክ፤ ኃይለ ሥላሴና መግሥቱ ሀገራቸውን ከድህነት የማውጣትና ልUዋላዊነቷን የማስከበር ራእይ እንደነበራቸው አያከራክርም። የቱን ያህል አወዛጋቢ ቢሆንም መለስ ዜናዊም ባለ ራእይ ነኝ ባይ ነው። ታዲያ ራእይን በተግባር ለመተርጎም የሚያስችል የማኔጅመንትና የቴክኖሎጅ አቅም ስላልነበራቸው ነው ምኞታቸውም ልፋታቸውም ከመጨረሻው የድህነት እርከን ፈቀቅ እንኳ ያላደረገን። በኔ አመለካከት በዘመናችን የፖለቲካ ፓርቲዎች ውስጥ የሚታየው ችግርም ሆነ ለፍሬ አለመብቃታቸው ከማኔጅመንት ችሎታ ማነስ የመነጨ ነው። ለዚህ ይመስለኛል ለፍትህና ለዴሞክራሲ ስርጸት መስዋእትነት ለመክፈል ዝግጁ የሆኑ ወገኖቻችን የሚለካ መርሀ-ግብር አውጥተው ከመንቀሳቀስ ይልቅ ማንም አዋቂ መስሎ ሊታይ በሚችልበት ርእዮታዊ ክርክር ላይ እድሜያቸውን የሚፈጁት። የግሪክ ፈላስፋዎች“ፈረስ ስንት ጥርስ አለው?” በሚል ርእስ እስኪነጋ ይከራከሩ ነበር ይባላል። ወጣ ብለው የታሰሩ ፈረሶቻቸውን ጥርስ ቢቆጥሩ መልሱን በሁለት ደቂቃ ውስጥ ሊያገኙት ሲችሉ።

ዕቅድ! ዕቅድ! ዕሁንም ዕቅድ!
የፖለቲካ ፓርቲዎች የዛሬውን የፖለቲካ ሁኔታ በተጨባጭ ገምግመው፤ የወደፊቱን ተንብየው፤ ከዚህ ተነስተን እዚያ መድረስ እንፈልጋለን ብለው ያወጡት የአምስትና የአስር ዓመት ዕቅድ ስለመኖሩ እርግጠኛ አይደለሁም። የረጅም ጊዜ እቅድና የስትራቴጅ ትልም አላቸው ብንል እንኳ ዕቅዱን በስትራቴጅ ትልሙ መሠረት ለማስፈጸም የሚያስችል በቂ የባለሙያና የማቴሪያል ኃይል አሰባስበው ባንድ ልብና ባንድ መንፈስ ብቻ ሲተጉና ከዳር ሲያደርሱ አናይም። ፓርቲዎቹም ልሂቃኑም ከየሱባኤያቸው ብቅ የሚሉት ብሄራዊ ቀውስ ሲከሰት፤ ወይንም የሕዝብ ስሜት ተነክቶ ቁጣና ቁጭት ሲገኑ ብቻ ነው። ድፍረት አይሁንብኝና ይህ ባሕርይ የሚያስመድበው ከሠለጠነው ወገን ሳይሆን በደመ-ነፍስ ከሚመራው ከወደ አራዊቱ ነው። ለምሳሌ ያህል፤ የ1953 1966 እና የ1980 የፖለቲካ አጋጣሚዎች በተከሰቱ ጊዜ ፓርቲዎቻችን የተያዙት ሳይደራጁ፤ ወይንም
በረንጆቹ አባባል ቁምጣቸውን ዝቅ እንዳደረጉ ነው።

“የምትሄድበትን ካላወቅህ ሁሉም መንገድ እዚያ ያደርስሀል”ይላል ዮጊ ቤራ የተባለው አሜሪካዊ የቤዝቦል ባለታሪክ...ከማታውቀው መንደር ማለቱ ነው። ልንደርስ የምንፈልግበትን ግብ ወስነን፤ የመንፈስና የማቴሪያል አቅማችንን ለዚህና ለዚህ ብቻ ዳርገን መንቀሳቀስ ካልጀመርን አድሮ ጭቃ የመሆናችን እድል የጎላ ነው።

ከየት እንጀምር?
በኤኮኖሚና በማሕበራዊ ቀውስ፤ በወታደራዊ ጣልቃገብነት፤ በሙስና፤ በዘረኝነትና በመብት ረገጣ የድጋፍ መሠረት ያጣው የIሕአዴግ አገዛዝ ብዙ እድሜ ሊኖረው እንደማይችል እየታወቀ የሚከሰተውን ያመራር ኦና ለመሙላት ፓርቲዎች የቱን ያህል ቅድመ ዝግጅት አድርገዋል ብለን መጠየቁ ፍጹም አግባብነት አለው። ተዘጋጅተናል ወይንም እየተዘጋጀን ነው የሚሉን ቢሆን ጥንስሱን አሳዩን ብለን መሞገት መብታችን ይመስለኛል። ስንፍና በ “ምሥጢራዊነት”እያሳበበ እንዲሸነግለን መፍቀድ የለብንም።

የፓርቲዎቹ የአምስት እና የአስር ዓመት ዕቅድ ቢያንስ የሚከተሉትን አካቶ ማየት እንፈልጋለን። ዘመናዊ መዋቅር፤ ዕቅዱ ላይ የሚያዳርስ የስትራቴጅ መርሀ-ግብር፤ በተወሰኑ ኢላማዎች ላይ ያተኮረ የማስተማርና የመቀስቀስ ፕሮግራም፤ አሃዛዊ የአባላትና የደጋፊዎች ምልመላ፤ በተወሰኑ ግኝቶች ላይ ያነጣጠረ የሎቢ፤ የዲፕሎማሲና የትብብር ሥራ፤ በፕላን ዘመኑ አንጓዎች ላይ የሚደረግ ያፈጻጸም ግምገማ፤ በግምገማው ላይ የተመሠረተ የድክመቶች ማረሚያ ሥርዓትና የመሳሰሉት።

ከላይ የተዘረዘሩት ተግባሮች የማያከራክሩና “ደ!” የሚያሰኙ ይመስላሉ እንጅ ይህ ነው የማይባል ዕውቀትና ልምድ፤ የባላሙያዎች ተሳትፎ፤ የገንዘብና የማቴሪያል ኃይል፤ የማስተባበርና የስምምነት መፍጠር ችሎታን የሚጠይቁ ናቸው። በተሳካላቸውና ገና በሚንደፋደፉ፤ በጫጩና በሚመነደጉ ፓርቲዎች መሀከል ያለው ልዩነት ይህ የብቃት ደረጃ ብቻ ነው። ሌላ ምስጢር የለውም።

በፕላን ያልተመራ የደመነፍስ እንቅስቃሴ ባስቸኳይ ሊቆምና ወደተረጋጋና በመልካም
የማኔጅመንት ሥርዓት ወደሚመራ ዘመን መሸጋገራችን ወሳኝነት አለው። በኢትዮጵያ ውስጥ ዲሞክራሲ፤ ፍትሕና መልካም አስተዳደር የማምጣትን ክቡር ሥራ የ “ፖለቲከኞች” ድርሻ
አድርገን መቁጠር ትልቅ ስህተት ነው። ትግሉ ይበልጥ የሚጠይቀው የፖለቲካ ከያኒዎችን
መደራረብ ሳይሆን በማኔጅመንት ሙያ፤ በቴክኒክና በቴክኖሎጂ መስክ የተካኑና የተፈተኑ
ዜጎችን ጭምር ስለሆነ ለነዚህ የሙያ ዘርፎች የላቀ ክብርና ቦታ ልንሰጥ ይገባል። ባለሙያዎችም ለፖለቲካ ሰዎች ያላቸውን ምጸትና ጥርጣሬ አስወግደው ወገናችን የዴሞክራሲ፤ የፍትህና የመልካም አስተዳደር ባለቤት እንዲሆን በሚደረግ ክቡር እንቅስቃሴ ውስጥ አስተዋጽኦ ለማድረግ ሸሚዛቸውን መጠቅለል አለባቸው።
kuchiye@gmail.com

Wednesday, March 26, 2008

"Kinijit Continues"


On the way to earning respectable existence, every organism faces growing pain. It will stumble and rise and it will wilt and regenerate. Probably not a surprise considering that fact that we live on a planet which sometimes is harsh and unfair. In the total scheme of things, Kinijit is an organism that necessarily has to go through life’s cycle. There is no way around it.

Along with Kinijit’s meteoric rise came organizational, financial and political challenges that no young party could possibly have been prepared for. You can compare it to a Katrina type crisis which even mighty America failed to handle skillfully. Along with that meteoric rise also came a great deal of expectation from millions and millions of us. That we were inspired by the party and bestowed it with massive trust was all good; but I am not entirely certain if it was fair to the budding organization.

No doubt Kinijit had faced set backs - it has stumbled, it has disappointed, it has disgruntled its supporters, albeit temporarily, and it even has been a subject of some ridicule. All these come with the territory and they are things the leadership, members and supporters can and must be able to handle. “The greatest glory” Confucius said, “is not in never falling, but in rising after every fall”. Indeed, Kinijit is rising after some very trying political times much to the delight of lovers of democracy and to the chagrin of others who craved its untimely death. With valued experience in its inside pocket, the party will continue with its journey much wiser, stronger and with even greater magnanimity.

The teams of Kinijit parliamentarians and party officials who are about to be dispatched through the length and breadth of the country to collect supporting signatures are harbingers of renewed hope, peace democracy, unity and reconciliation.

No matter which way we look at it, this is a moment to celebrate, to renew vows, to regroup and to look forward to a promising future for Ethiopia. We just cannot afford to let the ugly cloud of gloom and doom prevails over us. When the brave sons and daughters of Kinijit and of Ethiopia volunteer their services and their lives in a most unpredictable environment, the least the rest of us can do is give them the moral and financial support that will help them in getting the job done. We will follow their every step and echo their call for “Andinet”, for “Democracy” and for “Fithe”.

May the team’s presence amidst our people bring good omen as they go through what could be termed as the severest economic hardship and a drought that threatens over nine million lives.

Thursday, March 13, 2008

"Why I continue to be an ardent fan of peaceful struggle."

I want to get some facts straight. The EPRDF of today is the EPRDF of yesteryear - repressive, divisive and corrupt. The entire Kinijit leadership including Hailu, Bertukan, Mesfin, Berhanu, Berhane, Andargachew championed peaceful democratic struggle as the most appropriate for Ethiopian conditions. They earned the support of millions only because the party’s vision and the chosen mode of struggle stroke a chord across the length and breadth of the Ethiopian public.

Strip peaceful struggle off Kinijit and you will end up with an entirely different animal with awfully different set of values and strategies. If the leadership decides to revisit the party’s ways, as it should from time to time, then the place to do it is its own board room and, I might add, in Ethiopia. When individuals who are in the top echelon of the party trigger public discourse over some core values without first having discussed them internally, it becomes a case of recklessness. When it is done from the safety of thousands of miles it even becomes a case of outrage.

Whilst ordinary citizens and the general public have every right to start discourse on any particular topic, the standard, unfortunately, is quite different for party and government officials. With the acceptance of public office, one actually surrenders a little bit of that “personal right” to brag and say what ever one wants. No matter how well crafted a statement an official makes claiming it is a personal view, it will always be construed as the position of the organization. That is why we see responsible politicians walk unenviable fine lines in the public arena. That is also why we should demand people we put in leadership position conform to generally accepted standards of leadership behavior and organizational codes of conduct. It matters very little whether the organization is a blue chip corporation, a democratic party or a communist party of bye gone years; ethical, moral and operational standards are what differentiate our way of life from that of animal kingdoms.

Personally, I am not in a position to declare that peaceful struggle is a failure since we have not even tried a quarter of its potent tools. On the other hand, our entire history, more so the recent one, is replete with examples of armed struggle that resulted in hundreds of thousands of lives being lost with nothing to show at the end. EPRP, OLF, TPLF, EPLF, ELF, ONLF and several others can be cited as examples. When armed struggle reached the finishing line, like it did in Eritrea and Ethiopia, the population ended up with the short end of the stick and worse of from where it started. I hate to speculate there are people among us who are still enamored by the guerilla fighting years of Mao Tse-tung and Che Guevara. Pardon me, but we live in the era of helicopter-gun-ships and satellite communication that could make the life of a guerilla force down right miserable if not devastating. Besides, how does a society that is war-weary factor into the call for armed struggle? Judging from the obscenely unpopular nature of EPRDF, couldn’t one make the case that the inherently subtle, colorless and silent ways of peaceful struggle are working?

As much as I resent armed struggle, I also resent the continued loitering in the arena of individuals who lack the patience and the skill to see a strategy succeed. It is disheartening that the very same people who advocated peaceful struggle and pleaded with millions to follow them are now hoodwinking the party and the movement at their leisure. The fabric that holds Ethiopian society is much weaker today than it was yesterday, all the more reason to exercise caution when we make choices. Choices shall never be made from the dictates of frustration and despair. Let’s be firm, let’s be resolute.

'……but screw your courage to the sticking-place, and we'll not fail.' Shakespeare in Macbeth

Saturday, March 01, 2008

ይድረስ ለአቶ ኃይሉ ሻውል
አሜሪካ
March 1 2008


ቃሊቲ በእስር ሆነህ ለጻፍኩልህ ደብዳቤ እስካሁን መልስ ባላገኝም አንዳችም ቅሬታ አላደረብኝ። አንድም የጤንነትህን ጉዳይ ስለማውቅ ሌላው ደግሞ ከምርጫው ወዲህ የተመሳቀለውን ፖለቲካ ግራ-ከቀኝ አገናዝበህ ያላፊነት ግዴታህን ለመወጣት ፋታ እንደሚያስፈልግህ ስለማምን ነበር።

ይኸው ከተፈታችሁ ስድስት ወር ያህል ሆነ። ታዲያ የኢትዮጵያ ሕዝብ ችገር እጅጉን እየባሰ፤ የመንግሥት አምባገነንነት ቅጥ እያጣ፤ የተቃዋሚ ፓርቲዎች ሮሮ እየጠና፤ የጦርነት ዳመና በሰሜንና በምሥራቅ እያንዣበበና ሕዝባችን ታይቶ በማይታወቅ የኑሮ ውድነት አለንጋ እየተገረፈ ነው። በዚሁ ላቁም ብየ ነው እንጅ ዝርዝሩ እንኳ እርቆ መሳፍርት የለውም።


ከላይ የዘረዘርኩዋቸው ፈተናዎች ከህመምህ የበለጠ እንቅልፍ እንደሚነሱህ ላንዳፍታም አልጠራጠር። ሕዝብ ለነዚህ ሁሉ ችግሮቸ መታደጊያ ይሆነኛል ብሎ ተስፋ የጣለበትን የቅንጅትን ቤት መልሶ ለማቋቋም በሚደረግ ወሳኝ ጥረት ውስጥ ማንንም ምንንም ሳታስቀድም ትሳተፋለህ ብየ ብጠብቅም የምሳሳት አይመስለኝም። ታዲያ በአንድ ቤተሰብ ውስጥ የተፈጠረን ችግር ለመፍታት ይህን ያህል ጊዜ መፍጀቱ ምን ይባላል? ኬንያ ውስጥ በሁለት ተጻራሪ ፓርቲዎች መሀከል የተከሰተው በደም የተበከለ ቅራኔ እንኳ ይኸው በስድስት ሳምንት ውስጥ ተፈቶ የለምን?

ልናገረው ይቀፈኛል እንጅ ስለቅንጅት የቤት ውስጥ ችግር ሰው የሚያትተው ብዙ ነው። በኃሀይሉና በብርሀኑ መሀከል ያለ አለመጣጣም ነው፤ የብርሃኑም የኃይሉም የሥልጣን ጉጉት አለበት፤ የኃይሉ ግትርነት ነው፤ የብርሀኑ አለመጨበጥ ነው፤ የመኢአድና የቀስተ ደመና ተቀናቃኝነት ነው፤ የገንዘብ ንኪኪ ነው፤ የለም የኢሕአዴግ እጅ አለበትና የመሳሰሉት ይገኙበታል።

ከመጨረሻው ልጀምርና ያንዱ ወገን በሌላው ላይ ጥላሸት ለመቀባት ከሚያደርገው የፕሮፓጋንዳ ዘመቻ ባሻገር አንተም ሆንክ ብርሃኑ በኢሕአዴግ የሚሸነገል ዓይነት ርካሺ ህሊና እንደሌላችሁ እውቅ ነው። ሁለታችሁም ከዚያ የርካሽነት ደረጃ ያለፋችሁ ናችሁና። የገንዘብ ንክኪ የሚባለውም አልባሌ ወሬ ለመሆኑ እኔ ራሴ ማረጋገጫ አለኝ። እነዚህን ሁለቱን አሉባልታዎች ካወጣን ግን ችግሩ በሁለት ግለሰቦች መሀከል የተፈጠረ አለመጣጣም እንጅ ከ80 ሚሊዮን ሕዝብ ጉዳይ ጋር የማይገናኝ ሆኖ እናገኘዋለን። በሌላ አነጋገር ቅንጅትና ደጋፊዎቹ ፈረንጆቹ እንደሚሉት የኢጎ አለያም ደግሞ የኋላቀርነት መገለጫ የሆነው የግትርነት ሰለባ ሆነናል ማለት ነው። ታዲያ ይህ አንጀትን ካላቆሰለ ምን ሊያቆስል ይችላል? ታዲያ ይህ መሳቂያና መሳለቂያ ካላስደረገን ምን ሊያስደርገን ይችላል?

ውድ ወንድሜ!

ፖለቲካ ሁሉም በኪሣራ የሚለያዩበት የዳተኞች ጨዋታ አይደለም። አንዱ አሸናፊ ሌላው ተሸናፊ የሚሆንበት የፖለቲካ ቀመርም አይደለም። “እኔ ቅዱስ እሱ እርኩስ” ከሚል እይታ የሚጠነጠን የፖለቲካ ስትራቴጅ ደግሞ የኋላ ቀርም ኋላቀር ነው። ልብ ብለን ካየነው ለሦስተኛው ዓለም ኋላቀርነትና ሥልጣንን በደም የማሸጋገር አስከፊ ባህል መነሻዎቹ እነዚህ አመለካከቶች ናቸው። ቀሪዎቹ ችግሮቻችን የነዚህ ምንዛሪዎች እንጅ ሌላ አይደሉም።

“እሱ እንዲህ ብሎ! እሷ እንዲያ ብላ” እየተባባላችሁ ከፈጠራችሁት በቀላሉ ከሚነሳ የፖለቲካ አቧራ ባሻገር ሁለታችሁም ወገኖች ለኢትዮጵያ ሕዝብ ያላችሁ የጋለ ስሜትና በቅንጅት ራዕይ ላይ ያላችሁ አቋም ቅንጣት እንኳ እንደማይለያይና እንዳልተቀየረም እናውቃለን። ታዲያ ይህ ሁሉ ጭቅጭቅና ውዝግብ፤ ይህ ሁሉ የኢትዮጵያን ሕዝብ ሰቆቃ ማራዘም፤ ይህ ሁሉ ወገንን ማሳዘን በታሪክ ውስጥ ክቡር ቦታን ያስገኛል? ታሪኩም ይቅርና ከህሊናስ ፀፀት ያድናል?

ለሀኪሞች ብቻ ማን እነደሰጣቸው አላውቅም እንጅ “የበሽታውን መንስዔ ለይቶ ማወቅ የመፍትሔውን አጋማሺ ማግኘት ነው” የሚል ብሂል አላቸው። እኔ ግን በፖለቲካና በዕለት-ተለት ኑሮም እንዲሁ ይመስለኛል።

ለቅንጅት፤ ለመሪዎቹና በሚሊዮን ለመቆጠሩ ደጋፊዎቹ የወቅቱ አጣዳፊ ተግባር የፓርቲውን የውስጥ ችግር መፍታት ብቻ ነው እላልሁ። ሰፊውና ውስብስቡ የኢትዮጵያ ጉዳይ አይደለም፤ የዴሞክራሲና የሰብዓዊ መብት ጉዳይ እንኳ አይደለም። እነዚህ ክቡር እሴቶች እውን የሚሆኑት መሪ፤ ተቆርቋሪና አራማጅ ፓርቲ ሲያገኙ ብቻ ነውና።

የቅንጅት አመራር በመሀከሉ ያለውን መለስተኛ ቅራኔ በውይይት ለመፍታት አለመቻሉ ለሕዝቡ የሀዘን ምንጭ መሆኑንና በርካታ ንቁ ደጋፊዎች ወደ ገለልተኝነት እንዲሸጋገሩ ምክንያት መሆኑን አለመገንዘብ ስህተት ይመስለኛል። ለኢሕአዴግና በቅንጅት ለሚቀኑ ለሌሎች ፓርቲዎች ደግሞ የመዘባበቻ መሣሪያ እንደሆነላቸው እውቃለሁ። ስለዚህ ነው ለቅንጅት ይህን አንገት የሚያስደፋ ሁኔታ ከመቀየርና ደጋፊዎቹን እንደገና በትግሉ መስክ ከማሰባሰብ የበለጠ አጣዳፊ ተግባር ሊኖር አይችለም ያልኩት።

ፖለቲካ የድርድርና የሰጥቶ መቀበል ልጅ ናትና ያለፈውን ወደኋላ ትታችሁ ሁሉንም አሸናፊ በሚያደርግ ቀመር ውስጥ ችግሮቻችሁን እንድትፈቱ አይምሮአችሁም ልባችሁም ይከፈት ዘንድ እጸልያለሁ። በፖለቲካው ዓለም ወቅታዊነት ወሳኝ ነውና የሚጠፋ ደቂቃ እንኳ ሊኖር እንደማይገባ አስገንዝቤ እሰናበትሀለሁ።

ከማክበር ሠላምታ ጋር
ኩችዬ
ማርች 1 ቀን 2008 ዓ/ም

ማስታወሻ፡
ቃሊቲ በእስር እያለህ የጻፍኩልህን ደብዳቤ ቅጅ አያይዠዋልሁ