Thursday, November 05, 2009


ከሳጥን ውጭ ማሰብ አይከፋም!
(ስለ ሀይሉ፤ ኢህአዴግ፤ ፈረንጆቹና ብርቱካን)

ብርድ ልብስ ውስጥ እንደተጀበንኩ የኢትዮጵያን ፖለቲካ መፍታት ሲሳነኝ የቡና ተርቲበኛ ወዳጄን “ካሪቡ” እንደምቀጥረው አምና አካባቢ ያጫወትኳችሁ መሰለኝ። እጣኑ ይጐድል እንደሁ እንጅ የካሪቡ ቡናና የቤቱ ጌጥ (ፌንክ-ሹዌ ይሉታል ቻይናዎች) ከራማ ያስታርቃል። ታዲያ ይሄ ወዳጄ አንገቱን ከብርድ ልብስ ውስጥ ብቅ አርጎ መወያየትን አይፈራም። ጥልቅ አሳቢነቱን ብቻ ሳይሆን ወዛም ጨዋታውንም እናፍቀዋለሁ። እንዲህ ያለ ወዳጅ አያሳጣችሁ አቦ!

“እናም ሀይሉ ሻውል 2010 ምርጫ ውስጥ ለመግባት መወሰኑ ከምን መጣ? በእሥር የተንገላታበት የቅንጅት ባለ ስምንት ነጥብ ቅድመ ሁኔታስ ምን ጅብ በላው? ከትናንት በስቲያ የብርቱካን መፈታት ቅድመ ሁኔታ ነው አላለም ነበር ወይ? በርግጥ ሀብቱንና ንብረቱን ካደጋ ለመጠበቅ ሲል ያደረገው ሰጥቶ-መቀበል ነው? በ2005 ምርጫ ያሳዘናቸውን ደጋፊዎቹን እንደገና ማሰባሰብ እችላለሁ ቢል የለየለት እብደት አይደለም ወይ?” እነዚህንና ሌሎችንም ጥያቄዎች ወዳጄ ላይ ያራገፍሁት እንደመትረዬስ ነበር።

በንዲህ ያለ ስሜታዊነት ጨዋታ በጀመርኩ ቁጥር ምንጊዜም ዓይኑ ወደጣራው እጁ ወደ ቡናው ስኒ ነው የሚያመራው። በርጋታ ፉት ብሎ እስኪያጣጥም ድረስ የኔ ስሜት ሳይወድ-በግዱ እንደሚበርድ ያውቃል። ሰው የዚህን ያህል ውስጣችሁን ሲያነብ እህ! አትሉም? ቀጥልኩ ደግሞ ስለምርጫው - “የኢሕአዴግ ስሌት ምን ይመስልሀል? ምን ያህል ያገር ውስጥና የውጭ መንግሥታት ተጽዕኖ አለበት? ተጽዕኖዎችን ለመቋቋም ያለው አቅምስ? የኦባማስ አዲስ ፖሊሲ? ኢዩስ? የብርቱካንስ ጉዳይ? መድረክ ምርጫው ውስጥ የሚሳተፍ ይመስልሀል?....” ትንፋሼ መቆራረጥ ሲጀምር ራሴን ታዝብሁና እኔም እጄን ወደቡናው ስኒ ላክሁ።

ጥቂት ሴኮንዶች በፀጥታ ካለፉ በኋላ ጨዋታችን በተረጋጋ ሁኔታ መቀጣጠል ጀመረ። ሰው የሚያዘውትረውን ጎዳና ትተን በማይጓዝበት መስመር ማሰብና መመርመርን ቀጠልን። ጨዋታችንን ከነሙሉ ለዛው የማቅረብ ክህሎት ቢኖረኝ ምንኛ ደስ ባለኝ። ለዛሬው ግን ፈረንጆቹ እንደሚሉት ከሣጥኑ ወጣ ብለን (እኔ ከብርድ ልብሱ ያልኩት መሆኑ ነው) ለማሰብ ያደረግነውን ሙከራ አቃምሳችኋለሁ። “ይሄን መቼ አጣነው?” ለምትሉ አዋቂዎች ይቅርታ፤ የሚጥማችሁ ከተገኛችሁ ደግሞ መልካም።

የሀይሉ ሻውል ጉዳይ!
ሀይሉ ሻውል ሰንበት ያለ ፖለቲከኛ ብቻ ሳይሆን የተዋጣለት ነጋዴም ነውና ችሎታውን አኮስሶ ማየት የተዛባ ድምዳሜ ላይ ይጥላል ብለን እንሰጋን። በቃለ-ምልልስ ወቅት አንገት ከሚያስደፋው ሀይሉ ሻውል በስተጀርባ ሌላ ሀይሉ መኖሩን ታሳቢ ማድረግ በፖለቲካ ሳይንስ ሕግም የተደገፈ ነውና በዚህኛው ወገን መሳሳትን መረጥን። ይህን መነሻ አድርገን ነው የሀይሉን ድርጊት በለሆሳሱ የመረመርነው።

ሀይሉ እንደማንኛውም ፖለቲከኛ ለሥልጣን የተሰለፈ ሰው ነው። ችግሩ ግን ዕድሜው የገፋው ሀይሉና የዕድሜ ወስን የማታውቀዋ ሥልጣን በተለያየ ፍጥነት መሮጣቸው ላይ ሆነ። “ከህልፈቴ በፊት ታሪክ ገበታ ላይ ስሜን መቅረጽ አለብኝ” ብሎ ከተነሳ ማን ሊያቆመው ይችላል? ጥያቄው ታሪኩ የሚጻፍበት ርዕስና በየትኛው ገጽ ላይ ይሆናል የሚለው ብቻ ይሆናል። ሀይሉ የፖለቲካ ካርታዎች እንዳሉትም እንዘንጋ። የሀይሉ ስም ከመላ አማራ፤ መላ ኢትዮጵያና ከቅንጅት ጋር በተያያዥነት ሲነሳ ኖሯል። የስም ታዋቂነት ደግሞ በፖለቲካ ውስጥ ትልቅ ንብረት ነውና በተለይ በገጠሩ የአማራ ክልል ድጋፍ ሊያገኝ የሚችል ይመስለናል። አንዳንዶች እንደሚሉት ስሙ ጎድፎ ቢሆን እንኳ በባለሙያ የሕዝብ ግንኙነት ዘመቻና በገንዘብ ኃይል ሊታደስ የሚችል ነው። “የህዝብ ማስታወስ ችሎታ አፍታዊ ነው! ገንዘብ ካለ በሰማይ መንገድ አለ! ስለትናንቱ አትንገረኝ ዛሬ ምን አደርግክህልኝ!” የሚሏቸውን የፖለቲካ ብሂሎች ታውቁ የለም? ከዚህም ሌላ የሀይሉ ፓርቲ ባንዳንድ ክልሎች ውስጥ ማልዶ ሥራ መጀመሩ በሌሎች ተቃዋሚ ፓርቲዎች የወደፊት ይዞታ ላይ ተጽዕኖ አይኖረውም ማለትም አይቻልም።

ከሳጥን ውጭ ማሰባችን ካልቀረ ዘንድ በሀይሉ ጭንቅላት ውስጥ ሊመላለሱ የሚችሉ ሀሳቦችንም ቃኝተናል። “ኢሕአዴግ ለተወሰኑ ዓመታታ ሥልጣን ላይ መቆየቱ የማይቀር ከሆነ ሜዳውን ወለል አርገን መልቀቅ የበለጠ ጥፋት እንዲያደርስ የመፍቀድ ያህል ነው፤ ባለው የፖለቲካ ምሕዳር ውስጥም ኢሕአዴግን ማጋለጥ ምህዳሩንም እንዲሰፋ መግፋት ይቻላል፤ በፖለቲካ ጠርዝ ላይ ለረጅም ጊዜ መቆዬት መረሳትን ያመጣል ከበሬታንም እየቀነሰ ይሄዳል ወዘተ” ብሎ አስቦም ሊሆን እንደሚችል ገመትን። ከ 2005 ምርጫ ወዲህ ተቃዋሚው ወገን በፖለቲካ ጠርዝ ላይ አልሰፈረም ማለት ይቻላል?

ሌላም ከበድ ያለ ነገር አይጠፋ። ኢሕአዴግ፤ አሜሪካና የአውሮፓ ማሕበር “መኢአድ”ን እሹሩሩ ሲሉ ለመክረማቸው አያሌ ማስረጃዎች አሉ። ሀይሉ በድርድሩ ውስጥ መቆየቱ መድረክ አባላት ላይ ሥነ-ልቦናዊ ጫና ነበረው። መንግሥትና አምባሳደሮቹ ሀይሉን በኪሳቸው አርገው ነው መድረክን ሲጫኑ የከረሙት። በመጨረሻም ሀይሉ ፊርማውን በነጠብጣቡ መሥመር ላይ ባስቀመጠ ዕለት ተጨማሪ ተጽዕኖ ተፈጥሯል ባይ ነን። ያቶ መለስና የበረከት ስምኦን ደስታ ከዚያ የመነጨ ይመስለናል።

ታዲያ ሀይሉ ይህንን ሁሉ ውለታ የዋለው በነፃ ይመስላችኋል? ፈጽሞ! ከኢሕአዴግም ከፈረንጆቹም ተገቢውን ካሣ ለማግኘቱ አንጠራጠርም። አለያማ ርባና ያለው ፓለቲከኛም ጥሩ ነጋዴም አይደለም። ቢያንስ ቢያንስ ጥሩ የሚዲያ ጊዜ፤ የተመቻቼ የመንቀሳቀሻ ምህዳርና የገንዘብ ዳረጎት ያገኛል። የመልካም ተቃዋሚ ምሣሌ ለማድረግ ሲሉም በፓርላማና በያደባባዩ የክብር ቦታ ይሰጡታል። በውጭው ዓለም ደግሞ አሜሪካና አውሮፓ ለታላላቅ ተቃዋሚ ፓርቲዎች እንደሚያደርጉት ሁሉ ዲፕሎማቲክ ኢሚውኒቲና የክብር አቀባባል ቃል ገብተውለት ይሆናል። እነዚህ ነገሮች የትኛውንም ፖለቲከኛና የፖለቲካ ድርጅት ሲጎዱ አይተን አናውቅም። የዘረዘርናቸው ታሳቢዎች ዕውነት ከሆኑ ሀይሉ የፖለቲካ “ሃርድ-ቦል” ተጫውቷል ማለት እንችላለን።

ኢሕአዴግን በሚመለከት….
ከዕውነተኞቹ ተቃዋሚ ፓርቲዎች መሀከል ዳጎስ-ዳጎስ ያሉት በ2010 ምርጫ ካልተሳተፉ ለ ኢሕአዴግ ኪሣራ ነው። ባገር ውስጥም በውጭው ዓለምም መሳለቂያ እንደሚሆን ያውቀዋል። አዲሱ የኦባማ መንግሥት ደግሞ የዴሞክራሲ ምህዳሩን ለቀቅ እንዲያደርግ አምባሳደር ባለመሰየምና ከፍተኛ ባላሥልጣኖቹን በመላክ ጫና እያሳደረበት ነው። አውሮፓውያን ለኢሕአዴግ ጥፋቶች ይቅርታ ማፈላለግ ሰልችቷቸዋል። ዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብትና የዴሞክራሲ እምባ-ጠባቂ ድርጅቶች ይህን መንግሥት አሁን ከሚገኝበት ጭራ ደረጃ ወዴት ዝቅ እንደሚያደርጉት ግራ ሳይጋቡ አልቀሩም።

ከላይ የተዘረዘሩትና ሌሎችም ችግሮች ናቸው ኢሕአዴግን ወደ ድርድር ያመጡት። የሀይሉ ሻውል ፊርማ ምርጫው በጽኑ የሚፈልገውን “ሌጂቲመሲ” ባይሰጠውም ላፍሪካ ብዙ ትዕግሥት በሌላቸው ምዕራባውያን ዘንድ “የሚያበረታታ ጅምር” ተብሎ የሚታለፍ ዓይነት ሆኖ ይታየናል። ይሁን እንጅ ምርጫው እርባና ያለው ሌጅቲመሲ የሚያገኘው የቅንጅት ወራሺ የሆነው አንድነት ፓርቲ ወይንም በቅርቡ የተመሠረተው መድረክ ሲሳተፉ ብቻ እንደሆነ አይስቱትም። በዚህም የተነሳ ከአንድነትና ከመድረክ ጋር ውይይት አላቋረጡም የሚል ስሜት አድሮብናል።

በዚህ በ2010 ምርጫ ድርድርና ቻቻታ ውስጥ የተደበቀውንም የኢሕአዴግ ግኝት አንርሳ። “መኢአድ” በሙሉ ኃይል መንቀሳቀስ የሚጀምረው በ “ብአዴን” ኪሣራ ነው። ለዚህ ነው መለስ ሰፊ የሕዝብ መሠረት ያለውንና የሚፈራውን ያማራውን ክልል ለሁለት በመሰንጠቁ ደስተኛ ሊሆን የሚችለው። ምስኪን ብአዴን!

በየትኛውም ወገን እያገላበጥን ብናዬው ከሰሞኑ ሆያሆዬ እንደ ኢሕአዴግ የተጠቀመ የለም። ስለሆነም በምርጫው ስሞን ሚዲያውን ከፈት፤ ወከባውን ቀነስ፤ እሥረኛውን ለቀቅ ... በማድረግ ጥሩ ልጅ መስሎ ቢታይ ልንገረም አይገባም። ያን ካደረገ የርዳታውም የምኑም ቧንቧ እንደማይዘጋበት ያውቃል።

አሜሪካንና አውሮፓ ሕብረትን ደግሞ እንዳስ?
የኦባማ መንግሥት የውጭ ፖሊሲ ያገሩን ብሔራዊ ጥቅም ተከትሎ እንደሚሄድና ከቀድሞው ብዙም ሊለይ እንደማይችል ባለፈው የተስማማን ይመስለኛል። ይህን በሚመለከት “በርግጥ ኢትዮጵያ ላይ ሴራ አለ?” በሚል አምና አካባቢ ያቀለምኳትን እንድታነቡ እጋብዛችኋለሁ። http://kuchiye.blogspot.com/2008_07_01_archive.ht

ዘመዶች! ፈረንጆቹ ያፍሪካ ቀንድ የውጭ ፖሊሲያቸውን የሚያጠነጥኑት ሁለት እንዝርቶች ላይ መሆኑን አትዘንጉ - እርግጥ ዘይት መሳይ ቢኖረን ሦስተኛ እንዝርታቸውን ከማውጣት ወደኋላ አይሉም። አንደኛው እንዝርት ባፍሪካ ቀንድ አገሮች ውስጥ እልቂት የሚያስከትል የፖለቲካ ቀውስ አለመኖሩን የሚያረጋገጥ ሲሆን ሁለተኛው እንዝርት ደግሞ ሺብርተኞች ባካባቢው አስቀያሚ ድራቸውን እንዳያደሩ የሚከላከል ነው። በኢትዮጵያ ውስጥ ሁነኛ አማራጭ ኃይል እስካላገኙ ድረስ መለስ ላይ የሚቻላቸውን ያህል ተጽዕኖ እያደረጉና የሚያገኙትን ያህል የፖለቲካ እንጎቻ እየተቀበሉ ከመኖር የተሻለ አማራጭ የላቸውም። መለስ በሁለት ያማራ ድርጅቶች ቅልልቦሺ ለመጫወት እንደታደለው ሁሉ እነርሱም በኢሕአዴግና በሌላ አማራጭ ፓርቲ ቅልልቦሺ መጫወትን ይፈልጋሉ። ይሄ ነዋ የፖለቲካ ሳይንሱ።

የብርቱካን ጉዳይ!
ከወዳጄ ጋር የምናደርገው ወግ ከሳጥን ውጭ በማሰብ ላይ የተመሰረተ መሆኑን እያወቅን እንኳ የብርቱካን ተራ ሲደርስ ስሜታችን እንደመጋል አለ። ብርቱካን የምን ተምሳሌት እንደሆነች እንኳንስ ያበሻ ሰው ተክሉና አራዊቱም ያውቃልና በዝርዝር ትችት አናሰለቻችሁም። መንግስታት ሳይቀሩ የዚችን ሠላማዊ ትግል አራማጅ መሀረብ ማውለብለብ ጀምረዋል።

ታዲያ የጥያቄዎችም ጥያቄ የሆነብን “ይሄ ኢሕአዴግ ብርቱካንን በማሠር ምን የፖለቲካ ትርፍ አገኘ?” የሚለው ሆነ። ብርቱካንን የዴሞክራሲ ትግሉ ሰንደቅና ማዕከል ነው ያደረጋት። ብርቱካንን ባልረባ ሰበብ ማሠሩ ኢሕአዴግን በቀለኛና እብሪተኛ መንግሥት የሚል ስም ነው ያከናነበው። መቀራረብ ተስኖት የነበረውን የተቃዋሚው ጎራ ነው እንዲሰባሰብ ምክንያት የሆነው። ባጭሩ ትልቅ የፖለቲካ ቡቡ ነው የሠራው!

ታዲያ 2010 ምርጫን አስመልክቶ የብርቱካን መፈታት ለሁሉም ነገር ቅድመ ሁኔታ ሆኖ መቅረቡ ማንንም ሊያስደንቅ አይገባ። ሕዝቡም፤ ፖለቲካ ፓርቲዎቹም፤ የውጭ መንግሥታትም ብርቱካን እንድትፈታ ይፈልጋሉ። ጥቂት የማይባል የኢሕአዴግ ደጋፊ እንኳ የብርቱካን መታሠር የፖለቲካ ፋይዳ እንደሌለው ከመነሻው ጀምሮ ይከራከር እንደነበር እናውቃለን። በዚህ ሁሉ የተነሳ ነው ዲፕሎማቲክ ሕብረተሰቡ የብርቱን ጉዳይ እኋለኛው ምድጃ ላይ ሊጥድ ያልቻለው። ለዚህም ነው መድረክ፤ ኢሕአዴግና የውጭ መንግሥታት ተወካዮች ባደረጓቸው ስብሰባዎች ላይ ሁሉ አቢይ መነጋገሪያ የሆነችው።

ኢሕአዴግ ብርቱካንን ይፈታል። ስንብቶም ቢሆን የተጫወተው ቁማር እርሱን እንዳልጠቀመው ገብቶታል። የምትፈታበትን አጋጣሚ ግን ቸርና ይቅርታ አድራጊ መስሎ የሚታይበት ያደርገዋል። ሀይሉ ሻውልና ዲፕሎማቶቹም የኛ ልፋት ፍሬ ሰጠ ለማለት ይሺቀዳደማሉ፤ አንዱ የሌላውን ጀርባ ቸብ-ቸብ የሚያደርግበት ዘመንም ይሆናል።

ከምርጫው በፊት ብርቱካንን ለመፍታት ኢሕአዴግ ወኔው ይኑረው አይኑረው የሚታይ ነገር ነው።

“Thinking out of the box”
The case of Hailu, EPRDF, the Ferenjies and Bertukan
kuchiye@gmail.com

ማሳሰቢያ
በዚህ ጽሁፍ ውስጥ “የተከበሩ፤ አቶ፤ ወይዘሮ፤ ኢንጅነር... ወዘተ” የሚሉትን ቅጽሎች ያልተጠቀምሁት ለሰዎቹ ከበሬታ ሳይኖረኝ ቀርቶ አይደለም። በፖለቲካ ሥነጽሁፍ የተለመደ አሠራር ስለሆነ ነው። “ኢንጅነር እከሌ” የሚሉት መጠሪያ ካለ “አካውንታንት እከሌ” “ኤኮኖሚስት እከሌ” ስንል ልንኖር ነውና እባካችሁ ይህን አጉል ባህል እንተው። ከየት እንደመጣ የሚያስረዳኝ አለ?”

Wednesday, October 28, 2009


የ2010 ምርጫና ቻቻታው!

ከ2010 ምርጫ ጋር በተያያዘ ፊት-ለፊትና በሠያፍ የሚወረወሩት ትችቶች ብዛታቸውም ግለታቸውም እየጨመረ መሄዱ በመሀላችን የሰፈነውን የመረበሺና የጥርጣሬ ስሜት ያመለክታል። ስጋቱ ማንንም ከማን የለየ አይደለምና ትንሺ ልተችበት ፈለግሁ።

በኢሕአዴግ ልጀምር...
“ነገሮች በቁጥጥሬ ሥር ናቸው!” የሚል ገጽታ ማስተጋባት የሚፈልገው ኢሕአዴግ ውስጣዊ ጭንቀት እንዳለበት የፖለቲካን አቡጊዳን ለዘለቀ ሁሉ ስውር አይደለም። በ2005 ምርጫ ያደረሰው ጥፋት፤ ተቃዋሚ ፓርቲዎችን ለማዳከም የሚያካሂደው ቅጥ ያጣ ዘመቻ፤ ሕዝብ የማስተባበር ችሎታ ያላቸውን መሪዎች ማሠሩና ማሳደዱ፤ ነጻውን ፕሬስ ማዳከሙ፤ ፍትሀዊ የምርጫ ሜዳ የለም ብለው ተቃዋሚዎች ባይካፈሉ የሚደርስበት ኪሣራ፤ ብቻውን ሮጦ አሸነፍኩ ቢል የውጭ መንግሥታት የገንዘብም የዲፕሎማሲም ድጋፍ ለመስጠት የመቆጠባቸው ጣጣ፤ የተዛባ ምርጫን ተከትሎ ሊመጣ የሚችል ቀውስ......እነዚህ ሁሉ ኢሕአዴግን ማስጨነቃቸው እርግጥ ነው።

የጠቀስኳቸው ዝርዝሮች በቂ አይደሉም የምትሉ ከሆነ ደግሞ ጥቂት ላክልበት እችላለሁ - በአሜሪካው ፀረ-ሺብር ዘመቻ ውስጥ ኢሕአዴግ የነበረው ተፈላጊነት መመንመኑ፤ ባፍሪካ ቀንድ የፖለቲካ “ንብረትና ዕዳ” ሚዛን መዝገብ ላይ ኢሕአዴግ በዕዳው ዘርፍ መፈረጁ፤ ሀገሪቱን እያጥለቀለቀ ያለው የኤኮኖሚና የረሀብ ግሽበት፤ ጠቅላይ ሚንስትሩ በዓለም መሪዎች መድረክ ላይ ቀዝቃዛ ትከሻ እያገኙ መሄዳቸው....እነዚህ ሁሉ ኢሕአዴግን እንቅልፍ መንሳታቸው ከቶውንም አያጠራጥር። ቁንጮ ላይ ያሉት ባለሥልጣኖች ደፍኖባቸው ቢሆን እንኳ አንዳንድ አስሊ ፖለቲከኞቻቸው ይህን አይስቱትም።

ወገኖቼ! ከላይ የተዘረዘሩት ጭንቀቶች ናቸው ኢሕአዴግን ከተቃዋሚዎች ጋር እንዲደራደር ያስገደዱት። ተቃዋሚዎችም ወደ ድርድሩ ያመሩት የመንግሥቱን አጣብቂኞች ከግምት አስገብተው፤ የፖለቲካ ኮንሴሺኖች እንደሚኖሩ አምነው፤ አጋጣሚው የነርሱን ራዕይ ልዑዋላዊነትና የኢሕአዴግን ፕሮግራም ክስረት ለማሳዬት ያመቻል ብለው ነው። በየትኛውም የፖለቲካና የዲፕሎማሲ ሚዛን ላይ ብናስቀምጠው ተቃዋሚዎቹ ማለፊያ ስሌት አድርገዋል።

ስለ ስሌት ካነሳን ዘንድ የኢሕአዴግ አመራር ፍጹም ወጥ የሆነ አመለካከት አለው ብሎ መደምደም ስህተት እንደሆነ ሳላመላክት አላፍም። መንግሥት ከህዝብ ጋር እየተራራቀ መሄዱና ባጠቃላይ አገሪቱ ያለችበት አሳዛኝ ሁኔታ የሚያሳስባቸውና ለውጥ ማየት የሚሹ ግለሰቦች/ቡድኖች መኖራቸው ሊያከራክር አይገባም። ጥያቄው ቁጥራቸውና የኃይል ሚዛናቸው ተፈላጊውን ለውጥ ማምጣት ከሚችልበት ደረጃ ላይ ደርሷል አልደረሰም ከሚለው ላይ ብቻ ነው። ኢሕአዴግ በጥቅል ሲታይ ጫካውን ከዛፉ ለይቶ ማየት የተሳነው፤ የፍልስፍና ችኮነትና የ “ስኬታማነት” እብሪት ጠላቶቹ የሆኑት መንግሥት ይመስለኛል። እነዚህ ሁለቱ ደግሞ የብዙ መንግሥታት መጥፊያ (ወተርሉ) ለመሆናቸው የኛም ያለም ታሪክም ይመሰክራሉና ኢሕአዴግን ከንቅልፉ የሚያነቃው “ደብል-ኤስፕሬሶ” ያስፈልገዋል እላለሁ።

ወደ ተቃዋሚው ልሸጋገር?
ተቃዋሚው ወገን በሁለት ጎራ ሊከፈል የሚችል ይመስለኛል። ጎራ-አንድ “ኢሕአዴግ ከመሣሪያ ትግል ውጭ አይሞከርም፤ የሠላማዊ ትግሉ ምዕራፍ አክትሟል፤ ገዥው መንግሥት ዴሞክራሲያዊ ምርጫ ያካሂዳል ማለት ዘበት ነው” የሚለው ነው። የሳይበር ደጋፊዎቹ ቻቻታ አስተማማኝ መለኪያ ይሆናል ብንል ይህ ጎራ “ሠላማዊ ትግል” ብሎ አገር ውስጥ ለሚንቀሳቀሰው ወገን ብዙም አድናቆት ያለው አይመስልም። በጎራ-አንድ ደግፊዎች እይታ ያገር ውስጦቹ ፓርቲዎች ወይ ባንዳዎች ናቸው ወይንም ደግሞ ባንዳ ለመሆን የተሰለፉ ናቸው። እንዴ! ይሄ ፍረጃ የሚባለው ነገር ጊዜው ያለፈበት ርካሺ የግራ ፖለቲካ ቅሪት መስሎኝ? ያሁኑን ዘመን ፖለቲካ እኮ በነጭና በጥቁር ብቻ ፈርጀው የሚያዩት አይደለም። “እኔ ልክ አንተ ስህተት” የሚባልበትም አይደለም። እመሀል ላይ ሁሉም አሸናፊ የሚሆንበት መስክ መፍጠር ነው አሸናፊ ፖለቲካ የሚባለው። ስለዚህ ተቃዋሚው ወገን ዓይን ላይን መተያየትን ሊለምድ ይገባል፤ ሊከባበር ያስፈልጋል፤ አንዱ የሌላውን ስብራት ለማገም በጎ ፍቃድ ማሳየት አለበት። እዚህ ላይ የመሪዎቹ ምሳሌ መሆን እስከታች የሚዘልቅ መልዕክት ያስተላልፋልና የመጀመሪያውን ርምጃ ሲወስዱ ማዬት እንፈልጋለን። “ሁሉም ዜሮ ዜሮ” ዓይነት ፖለቲካማ ይብቃን።

ጎራ-ሁለት ደግሞ “ሠላማዊ እንጅ ትጥቅ ትግል ለማካሄድ አመች አገራዊና ዓለም-አቀፋዊ ሁኔታ የለም” ባይ ነው። በተጨማሪም ኢሕአዴግን መግጠም በሠለጠነበትና በተካነበት የመሣሪያ ትግል ሳይሆን ፍጥጥ ብሎ የሚታየውን ደካማ ጎኑን ዕለት ተለት በማጋለጥ፤ ደንጊያ እንደምትሰብረዋ የዝናብ ጠብታ ያልታከተ የፖለቲካ ሥራ በመሥራት ነው ይላል። በሁለቱ ተቃራኒ አቋሞች ላይ ብዙ ስለተጻፈ በዝርዝር አላሰለቻችሁም። ስለ ግል አመለካከቴ “ሠላማዊ ወይስ ጥጥቅ - እንካስላንቲያዎቹ” በሚል ርዕስ የጻፍኩትን ማንበብ ትችላላችሁ።

የጎራ-ሁለት ደካማ ጎን አምስት ዓመት እንኳ ዕድሜ ያላስቆጠረ ብላቴና መሆኑ ነው። ስለሆነም የልምድ ማነስ ቢታይበት ልንበረግግ አይገባም። የዚህ ዓይነቱ ትግል አራማጆች ፈተና ብዙና ውስብስብ ነው። የሚመሩባቸውን ሰነዶች የማዘጋጀት ብቻ ሳይሆን ግልጽ የማድረግ ግዴታ አለባቸው። ደጋፊያቸው በሰቀቀን ኑሮ ውስጥ የሚገኝ ነውና ዛሬውኑ ውጤት ውለዱ ይላቸዋል። ሥራቸው ፊትለፊት ነውና ለነቀፋ፤ ለሴራና ለወከባ የተጋለጡ ናቸው። የሚጋፉት ካዝናውንም ወታደሩንም ሚዲያውንም ፍርድ ቤቱንም የግሉ ካደረገ መንግሥት ጋር ነው። በየድርጅቶቻቸው ውስጥ ሊመሠርቱ የሚሞክሩት የዴሞክራሲ ባሕል ለብዙዎች ባይተዋር ስለሆነ የግጭትና አንዳንዴም የመሰንጥቅ ጣጣ ያመጣባቸዋል። ከሥራው ጠባይ ጋር አብሮ የሚጓዝ መሰናክል ስለሆነ እንዴት እንደሚዘሉት ብቻ ነው ማሰብ የሚችሉት። ሊያስወግዱት ግን አይሆንላቸውም። እንዲህ ዓይነቱን የኃላፊነት ፈተና ለመቀበል የቆረጡ ወገኖቻችንን መደገፍ ባንችል እንዴት ልናከብራቸው እንቸገራለን?

የ “አንድነት” እና የ “መድረክ” ጉዳይስ?
“ቻተር” ይሉታል ፈረንጆቹ። የተሻለ ትርጉም የሚነግረኝ እስኪመጣ ድረስ “ቻቻታ” ብየዋለሁ። የሳይበሩ ሕብረተሰብ በአንድ ጉዳይ ላይ የሚያደርገው ቻቻታ ከተጧጧፈ ያ ጉዳይ አሳስቦታል ማለት ነው። ያሳሳቢነቱ ደርጃ የሚለካው ደግሞ የተወሰኑ ቃላቶች ድግግሞሺ ሲበዛ ነው። የሀበሻውን ድረ-ገጽ ላንዳፍታ ብትቃኙት “አንድነት” “መድረክ” እና “ምርጫ” የሚሏቸው ቃላት ድግግሞሺ ጣራ ነክቷል። ለምን? ማለት ጥሩ ነው። እስቲ “ምርጫና አንድነትን” እንዲሁም “አንድነትና መድረክን” ላንዳፍታ እንመርምራቸው።

ምርጫና አንድነት። አንድነት ከመነሻው ሠላማዊ ትግል አካሂዳለሁ ብሎ ያወጀ ድርጅት ነውና ስለ2010 ምርጫ ቢያወራ፤ መግለጫ ቢሰጥ፤ ከመንግሥትና ከመንግሥታት ጋር ቢደራደር፤ ስትራቴጅያዊና ታክቲካዊ ጥቅም ባየበት ቦታ ከሌሎች ጋር ቢሻረክ ፍጹም መብቱ ነው። የሚጠበቅበትም ነው። ከነዚህ ተግባሮች ሊታቀብ የሚችለው ሥርዓትን በተከተለ መልክ በአባሎቹ በሚደረግ ውሳኔ ብቻ ነው። የሠለጠነው አገር አሠራርም የዴሞክራሲ ወግም ከዚህ የተለየ አይደለም። በሌሎች ፓርቲዎች ውስጥና ዙሪያ የተሰባሰቡ ግለሰቦች በአንድነት የፖለቲካ ምርጫዎችና ውሳኔዎች ላይ ተጽእኖ የማድረግ ሕጋዊም ሞራላዊም ሥልጣን እንደሌላቸው ቢረዱ ጥሩ ይመስለኛል። እነዚህ ፓርቲዎችና ደጋፊዎቻቸው የራሳቸውን ቤት የማጠናከርና የማሳመር ብርቱ ኃላፊነት እያለባቸው ስለሌላው ቤት ለምን እንደሚጨነቁ ግራ የምጋባበት ጉዳይ ነው።

አንድነትና መድረክ። ተሳስቼ ከሆነ እታረማለሁ እንጅ በመድረክ መቋቋም ፀጉራቸውን ሲነጩ የማየው በሰላማዊው ትግል ዙሪያ ያሉ ፖለቲከኞች አይደሉም። “አንድነት ፓርቲ የብሔር ቅኝት ካላቸው ድርጅቶች ጋር ትብብር መፍጠሩ የስህተትም ስህተት ነው” እያሉ የሚደሰኩሩትም ከጥቂቶቹ በስተቀር የፓርቲው አባል ያልሆኑ፤ በደጋፊነት ደረጃ ተመዝግበው እንኳ የገንዘብም የሀሳብም አስተዋጽኦ የማያደርጉ ናቸው። ራስህን ዋቢ አደረግህ አትበሉኝ እንጅ በዚህ ርዕስ ላይም የጻፍኩትን http://kuchiye.blogspot.com/2009_07_01_archive.html ማየት ትችላላችሁ። ዘርዘር አድርጌ እንዳልተች በራሴ ላይ የጣልኩት የገጽ ገደብ ይዞኛልና በቅርቡ እመለስበታልሁ።

አንድ ነገር አስተውላችኋል? ልብ ብሎ ለተመለከታቸው ጥያቄዎች ብዙውን ጊዜ መልሳቸውንም አዝለው ነው የሚጓዙት። እስኪ በተረፉኝ መስመሮቼ ጥቂት ጥያቄዎች አንስቼ ልሰናበታችሁ።

1. በቅርብ ዘመን ታሪካችን ድርጅቶችና ፓርቲዎች ሕብረት፤ ጥምረት፤ መድረክ መፍጠራቸው ትዝ ይለናል። የውጤታማነታቸውን ነገር ለጊዜው ወደጎን ብንተወው በመተባበራቸው ምክንያት ደም ፈሶ አይታችኋል?
2. መተባበር ቀርቶ መነጋገርን አሻፈረን ያሉ ድርጅቶች ጦር በመማዘዛቸው ትውልድ እንዳለቀ ረስተነው ይሆን?
3. የመድረክ መቋቋም የተራራቁ አቋሞችን ለማቀራረብ፤ የጥርጣሬ ቀዳዳዎችን ለመዝጋት፤ የርስበርስ መተማመንን ለማዳበር ከመርዳት ሌላ ምን የሚያስከትለው ጠንቅ አለ?

Kuchiye@gmail.com.

Thursday, October 22, 2009

የአውራዎች አንድነት!
“በዚያን ሰሞን የ “አውራን” አስፈላጊነት ላዋያችሁ ብዬ ብዙ ጥይት ነው ያባከንሁት። ዳግማዊ ዳዊት በተመጠኑ የሥነ-ግጥም ቃላት መልዕክቱን ደህና አድርጎ ስላቀረበው አንብባችሁ ትደሰቱበት ዘንድ ለጥፌዋለሁ።” ኩችዬ
-----------
ጃርት የሚባል አውሬ-ግፍ ቢያበዛበቸው
ንቦቹ ወጡና- ከየመኖሪያቸው
ጥያቄ አቀረቡ- ለየአውራዎቻቸው።
ስብሰባ - ቁጭ አሉ፣
በስፋት - መከሩ።
አውራዎቻቸውን- ፊት ለፊት ቁጭ አርገው
እንዲህ ነገሩዋቸው
እንዲተባበሩ
መሪወቹ ሁሉ
አውራወች በሙሉ - በአንድነት ከሰሩ
ክፉ ጃርት አይመጣም - በዚህ በሰፈሩ።
ቃልም ተገባቡ-ከዚህ ቃል ላይወጡ፣
ለአናቢው ገበሬ-ትዕዛዝንም ሰጡ
አንተ ንብ አናቢ-ከዛሬ ጀምረህ
አሳየን ብለናል- በአንድ ቀፎ አድርገህ።
አናቢው ገበሬ- ልቡ እያመነታ
ትናንት በሚያውቀው- በለመደው ፋንታ
አንድ ቀፎ መርጦ- በጭስ አጠነና
ንቦችን በመለ- ከአውራወቹ ጋራ
በአንድ አስቀመጣቸው
እንደጥያቄያቸው።

ያለ አፈጣጠሩ
ሆኖ ትብብሩ
እያንዳንዱ መሪ-ሰራዊቱን ይዞ
ቀፎው ባዶ ቀረ- ንብ ሁለ ተጉዞ።
ድሮም ሆኖ አያውቅም፣
ትናንት ሆነ ዛሬም
አንድ የንብ አውራ ነው- ከሺህ ሰራዊት ጋር
ውጤትን የሚያሳይ- የሚጋግረው ማር፡፡

ዳግማዊ ዳዊት
ጥቅምት 2002
Ethio_dagmawi@yahoo.com

Thursday, September 24, 2009

አውራ የሌለው ምንም የለው! (No Leader no Glory!)


ሶሻሊዝም ካወረሰን መዘዝ አንዱ በ “ጋራ አመራር” ላይ ያለን የተወላገደ አስተሳሰብ ይመስለኛል። እዚህ ድምዳሜ ላይ የደረስሁት ጥቂት የማይባሉ ማሕበራዊና ፖለቲካ-ቀመስ ድርጅቶችን አሠራር ካገናዘብሁ በኋላ ነው።

ተደጋግፎ መኖር የግድ ከሆነበት ዘመን ጀምሮ በ “አውራ” መመራት አማራጭ አልተገኘለትም። ይህ ታዲያ በሰው ልጅ ዘር ብቻ የተገደበ እንዳይመስላችሁ። እንደ ንብ በደመ-ነፍስ የሚንቀሳቀሱት ሳይቀሩ አውራ ከሌላቸው ጣፋጭ ማር ቀርቶ ደረቅ ቂጣ መጋገር ይሳናቸዋል። ልብ ብላችሁ ከሆነ “አውራዎች” አላልኩም - ባንድ ቤት ውስጥና ባንድ ወቅት አንድ አውራ ብቻ ነው ሊኖር የሚችለውና ነው።

ጥሩ አውራ የጠለቀ ትምህርት፤ የተመሰከረ ልምድ፤ በሀቅ ለማገልገልና በውጤቱም ለመኩራት የጋለ ፍላጎት ያለው ነው። የሰውና የማቴሪያል ኃይሎችን አነቃቅቶና አስተባብሮ መሥራት ይችላል። በቅጣት ፋንታ ሽልማትን ማነቃቂያ መሣሪያው ያደርጋል። የሰዎችን አመኔታና ድጋፍ የሚያገኘው በተግባሩ ምሳሌ ሲሆንና ለሚያገለግለው ሕዝብ ፍቅርና ከበሬታ ሲያሳይ እንደሆነ ያውቃል።

ታዲያ እንዲህ ያለ ችሎታና ሥነ-ምግባር ያለውን ሰው የሚፈልገው ብዙ ነውና የኛ እናደርገው ካልን ከመንገዳችን ወጥተን ልናግባባውና ምቹ የሥራ አካባቢ ልንፈጥርለት ግዴታ ነው። በራዕይና በአጠቃላይ መርሆች ላይ ስምምነት እስካለን ድረስ ስልት የመቅረጹንና ውሳኔ የመስጠቱን ሥልጣን ለመሪውና እርሱ ላዋቀረው ቡድን መተው አለብን።

እሱ ላዋቀረው ቡድን?
አዎ! አውራው ላዋቀረው ቡድን። አንድን ድርጅት ወይንም መሪ ለሥልጣን የምናበቃው ብዙ አማራጮችን አገናዝበንና የዚህኛው ድርጅት ራዕይ ይጥመናል፤ ለኛም ላገራችንም ይበጃል ብለን ነውና የኛ ሀላፊነት እዚያ ላይ ማቆም አለበት። የመረጥነው የተሻለውን ፕሮግራም ብቻ ሳይሆን ፕሮግራሙን ለማስፈጸም በቂ ዝግጅትና ዕውቀት እንዲሁም ተአማኒነት አለው የምንለውን አውራ ጭምር ነው።

ልብ ብላችሁ ከሆነ በኢትዮጵያ ፖለቲካዊና ማሕበራዊ ድርጅቶች ውስጥ እንዲሰፍን የፈቀድነው ያሠራር ባህል አውራን ሺባ ያደርጋል። ዕውቀቱም ልምዱም ታማኝነቱም አለህና ና ምራን ካልነው በኋላ ለመምራት የሚያስችለውን ሥልጣን እንነፍገዋለን። ከማያውቁትና ከማያውቃቸው ሰዎች ጋር ተጣመድና ውጤት አሳይ እንለዋለን። በዕውቀትም በባሕርይም በምንም እርሱን ከማይመስሉ ሰዎች ጋር አቆራኝተን “እየተግባባችሁ” ሥሩ እንለዋለን። የማኔጅመንትን ሳይንስ ያልተማረው ገበሬ እንኳ ትጉውን በሬ ከአባያ በሬ ጋር አያጣምድም። የተገራውን ካልተገራው ጋር አያሰማራም። አንዳንዴማ ደብዳቤ እንኳ ሳይቀር በጋራ እንዲረቀቅና በያንዳንዷ ቃል ላይ “የጋራ” ስምምነት እንዲኖር እንፈልጋለን። የጽሕፈት ቤት ሠራተኞች መቅጠር፤ መገምገምና አስፈላጊ መስሎ ሲታየውም ያስተዳደር ርምጃ መውሰድ የአውራው የማይገሰስ ሥልጣን መሆኑን እንኳ የማናውቅ አለን። በኔ ይሁንባችሁ ወገኖቼ! - ያወቀውና የተማረው በእንዲህ ዓይነቱ ኋላቀር ማሕበር ውስጥ ጥዋ አይጠጣም፤ አባልም መሪም ለመሆን አይጣደፍም። ለዚህ ሳይሆን ይቀራል በአብዛኞቹ የኢትዮጵያ ድርጅቶች ውስጥ በባለሙያ ፋንታ የተገኘው የተነሰነሰበት? - ባገር ቤትም በዳያስፖራውም ማለቴ ነው። ከለብ-ለብ አመራር ልንጠብቅ የምንችለው የኋልዮሺ ጉዞና እጅግ የቀናን እንደሁ ደግሞ ለብ-ለብ ውጤትን ነው።

ለዚህ ነው ፕሬዚደንትም እንበለው ሊቀመንበር፤ ጠቅላይ ሚኒስትርም እንበለው የድር ዳኛ፤ አብሮት የሚሠራውን ካቢኔ ወይንም ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ የመምረጥ መብት ሊኖረው ይገባል ብዬ የተነሳሁት። ይህ ሀሳብ እንደ ኮሶ የሚመራቸው “የጋራ አመራር” ደቀመዛሙርት እንዳሉ አልጠራጠርም። የቱንም ያህል ይምረራቸው እንጅ ትምህርትንና ሙያን በስሜትና በወገናዊነት ልናካክሳቸው እንደማንችል መቀበል አለባቸው።

በፖለቲካም በሌላውም መስክ ችኮ አቋም መያዝ በጎ አይደለምና እመሀል ላይ አስታራቂ መፍትሔ አግኝቻለሁ። እንዲህ ይሁን - አሠራሩን እስክንለማመደው ድረስ አውራው 51% የሚሆነውን ካቢኔ ወይንም የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ የመምረጥ ሥልጣን ይኑረው። ሳንውልና ሳናድር በሁሉም ዓይነት ድርጅቶች ውስጥ የአውራውን ሥልጣን (executive power) ብናጠናከር በሁሉም ድርጅቶች ውስጥ ውጤታማነት ጣራ በጥሶ ይወጣል። ባለሙያውም ከየከተመበት ብቅ እያለ “እሺ ላገልግል” ይላል። የመጨረሻ ቤሳየን ሳልቆጥብ የምወራረድበት ጉዳይ ነው።

ታዲያ ይሄ አምባገነንነትን አይጋብዝም ወይ?
ፈጽሞ! አምባገነንነት በላያችን ላይ ይነግሥ ዘንድ የኛንም የማንንም ፈቃድ ጠይቆ አያውቅም። ለዚህ ከኢትዮጵያ የበለጠ ምስክር የለም። የምንመርጠው መሪ በኛና በርሱ መሀከል የተፈረመውን የራዕይና የፕሮግራም ሰነድ ተከትሎ ነው የሚሠራው። ይህን ለመከተሉ ማረጋገጫችን ደግሞ የተዘረጋው የቁጥጥርና የሪፖርት አቀራረብ ሥርዓት ነው። ለርሱ፤ ለሥራ አስፈጻሚውና ለጠቅላላ ጉባዔው አከፋፍለን የሰጠነው የሥራና የሥልጣን ድርሻ ነው። “አራተኛው መንግሥት” የሚባለው ነጻ ፕሬስም ፍቱን የማረጋገጫ መድሀኒታችን ነው።

የጋራ አመራር ጉዳይስ? የሰፊው ህዝብ ጉዳይስ?
ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ባለበት አገር ሕዝብ ያገሩ ባለቤትም ነው የሥልጣን ቁንጮም ነው። መሪዎቹን የመምረጥና የመሻር ዕድል ባላገኘበት ሁኔታ ግን ሰፊው ሕዝብ የማንም ባለቤት የምንም ቁንጮ አይደለም። ሀቁን እንነጋገር ካልን ሰፊው ሕዝብ ከሚገለጽባቸው መለያዎች መሀከል መሀይምነት፤ ድህነት፤ ረሀብተኝነትና ኋላቀርነት ጥቂቶቹ ናቸው። ለተፈጥሮና ለመንግሥት አደጋ መጋለጥም የዋዛ አበሳዎቹ አይደሉም። ይህ ዕውነታ ዝንተ-ዓለም አብሮን መኖሩን እያወቅን ነው ሌኒናውያን “ታሪክ ሠሪው ሰፊው ሕዝብ ነው!” እና “የጋራ አመራር!” የሚሏቸውን ሴሰኛ መፈክሮች ኳኩለው ብቅ ያሉት። ታዲያ ይኼ በሕዝብ ጀርባ ላይ ፊጥ ለማለት እንዲጠቅማቸው ያመጡት እንጅ ሰፊው ሕዝብ አንዲት ሀባ ስልጣን ያየበት ጉዳይ አይደለም። ለነገሩ ሕዝብ ያልተማረ ከሆነ እንዴት ነው በጋራ መርቶ ውጤት የሚያስገኘው? እንዴትስ ነው ታሪክ ሊሠራ የሚቻለው? እስቲ እነዚህን መፈክሮች የሙጥኝ ብለው የነበሩ ሶሻሊስት አገሮችን ጤንነት አጠያይቁ። ሁሉም እንደከሰሩና አንዳዶቹም ብትንትናቸው እንደወጣ ትሰማላችሁ።

ትዝ ይላችሁ እንደሁ በ“ሰፊው ሕዝብ” እና በ“ጋራ አመራር” ዘፈን መደንቆር የጀመርነው ከ 1966 በኋላ ነበር። ጥቂት የማይባለው የሕብረተሰብ ክፍል በይሉኝታም ባድርባይነትም ባለማወቅም ተገፋፍቶ “አዎን ሰፊው ሕዝብ!” “አዎን የጋራ አመራር!” አለ። በግለሰብ የመፍጠርና የተነሳሽነት ኃይል ላይ ቀዝቃዛ ውኃ ቸለስንበት። ግላዊነት “እርኩስ-ወአርዮስ” ተብሎ እንዲያቀረቅርና እንዲሰደድ ተገፋ። ከግለሰብ ጋር ተፈጥሮዋዊ ቁርኝት ያለቸው ፋይዳዎች - ዕውቀት፤ ምጥቀት፤ ተነሳሺነት፤ ፈጣሪነትና ምሁራዊነት የንኡስ ከበርቴው ፀያፍ ባህርዮች ተብለው ተኮነኑ። በጥራት ፋንታ ብዛት፤ በዕውቀት ፋንታ ታማኝነትና ጎጥ፤ በሙግት ፋንታ የጅምላ ስምምነት ባህላችን ሆኑ። ከዚያን ዘመን ጀምሮ ነው መቅኖ ያጣ ሕዝብ የሆንነው ወገኖቼ።

የግለስቡ ጉዳይስ?
ባንጻሩ ደግሞ “ግለሰብ የችሎታም የፈጠራም የታሪክም ብቸኛ መንስኤ ነው” የሚሉ አገሮች አድገውና ተመንድገው እናያለን። የግለሰብ መብት መከበር የቡድንና ያገር ነፃነት መከበርን ያረጋግጣል ብለው ስለተማማሉ ዘንድሮም የብልጽግናና የመረጋጋት ባለቤት ናቸው። የግል
ንብረትንና የግለሰብ የፈጠራ ሥራ መከበርን የሕገ-መንግሥታቸው አውታር በማድረግ የተፈጥሮ ሃብታቸውን ባግባቡ እየፈለፈሉ ላገርና ለወገን ጥቅም አውለዋል። የጫካ መጨፍጨፍና በሣት የመጋየት አሳዛኝ ዕጣ አልደረሰባቸውም። አፈራቸው ተሟጦና ለዛውን አጥቶ ሕዝባቸው ለስደትና ለምጽዋት አልተዳረገም። እነዚህ አገሮች የሁሉንም ግለሰብ እድገትና የዕውቀት አድማስ በመገንባት ላይ ብቻ የተወሰኑ ሳይሆኑ ከዜጎች ውስጥ ልዩ ችሎታና ተሰጥኦ ያላቸውን ወጣቶች (ያገር ንብረቶች) እየመረጡ ተሰጥኦዋቸውን በሚመጥን ልዩ የ “ኤሊት” ትምህርት ቤት አስገብተው ይንከባከቧቸዋል - የነገው መሪዎችና የፈጠራ ሰዎች ከነርሱ መሀል ነው የሚገኙትና!

ማርክሲስቶች “ኤሊትዝም”ን ላፋቸው እንደማይወዷት ሁላችንም እናውቃለን። ይሁንና ልጆቻቸው ኤሊትና ያገር መሪ ይሆኑ ዘንድ በልዩ ትምህርት ቤት ለማስተማር የሚሽቀዳደሙት እነርሱው ናቸው። ሀርቫርድን፤ ስታንፈርድንና ፕሪንስተንን ለልጆቻቸው ሲቃዡ ነው የሚያድሩት። ልጆቻቸው የነዚህ ኤሊት ዩኒቨርሲቲዎች ምሩቅ እንዲሆኑ የማይፈነቅሉት ድንጋይ የሚሳሱለት ገንዘብ የለም። ከዚህ የበለጠ ሂፖፕክራሲ አለ?።

የኛውን አገር ታሪክ መለስ ብለን ብናይ ግለሰቡን የመኮትኮትና የማነጽ አስፈላጊነት ግንዛቤ ያገኘው ገና ትናንት በ1896 ዓ/ም ነው። ዳግማዊ አፄ ምኒልክ የመጀመሪያውን የፈረንጅ ትምህርት ቤት ከግብጽ በመጡ ሁለት አስተማሪዎች ጀመሩና ይህን ጅምር በእጥፍ ድርብ ያፋጥኑት ገቡ (እኒህ መሪ 61 የዘመናዊነት መነሾ ፕሮጀክቶች እንደጀመሩ በብላቴን ጌታ መርስዔ ሀዘን መጽሐፍ ላይ አንብቤ ተደንቄአለሁ)። አፄ ኃይለሥላሴም በምኒልክ ጅምር ላይ ብዙ ገነቡ። ከመደበኛ ትምህርት ቤቶች በተጨማሪ እንደ ጀኔራል ዊንጌት፤ ቅዱስ ዮሴፍና ሳንፎርድን የመሳሰሉ የኤሊት ትምህርት ቤቶች ተቋቋሙ። ከነዚህ ትምህርት ቤቶች ነው ብዙዎቹ መሪዎቻችን የወጡት - ቢያጠፉም ቢያለሙም።

ቀጥሎ የመጡት መንግሥታት ግን ጀኔቲክ መሠረታቸው ማርክሲስት ስለሆነ የግለሰቡ ተነሳሽነትና የልማት ሞተርነት ሊዋጥላቸው አልቻለም። መሬት የግል መሆኑ፤ ፍትሀዊ የንግድና የኢንዱትሪ መስክ መፈጠሩ ገበሬውንና ነጋዴውን ከጭብጣችን እንዲያፈተልክ ያደርጋል ብለው ስልሚሰጉ ፖሊሲዎቻቸው ፀረ-ግለሰብና ፀረ ውድድር ናቸው።

እነዚህ መንግሥታት በምሁሩ ላይ ያደረሱት በደልና አገር ጥሎላቸው እንዲወጣ ያካሄዱት ሴራ አንደኛው አንጀት-አቁሳይ ታሪካችን ነው። ምሁሩ ለማይፈልገኝና ለሚያንጓጥጠኝ ሕብረተሰብ ምንተዳዬ አለና መድረኩን ላላዋቂዎች አስረክቦ ኑሮውን ማሳመር ተያያዘ - ተሰደደም። የሚወደስበትና የሚከበርበት ዓለም ሲያገኝ ያን አዲስ ዓለም ዓለሜ ብሎ ተቀበለ። ባሁኑ ጊዜ የሀበሻ ባለሙያ ከሁዋይት ሀውስ እስከ ኮንግሬስ፤ ከወል-ስትሪት እስከ ሜይን-ስትሪት ከአካዴሚያ እስከ አምራችነት ተነስንሶበታል። ለተማረው ሕዝብ ፍልሰት (brain drain) ጥሩ ተምሳሌት ከፈለጋችሁ ሩቅ መሄድ አያስፈልጋችሁም ለማለት ነው።

ታዲያ ከየት እንጀምር?
የምንጀምረውማ የተሳሳቱ አመለካከቶችን ከመቀየር ሊሆን ይገባል። ዴሞክራሲያዊ አሠራር ማለት “የጋራ አመራር” ማለት እንዳልሆነ እንቀበል። ሕብረተሰቡን ሳይሆን ግለሰቡን የመብትና የደሞክራሲ ሥርዓት መነሻም መድረሻም እናድርግ። ከስኬታማ ድርጅቶችና ሀገሮች በስተጀርባ ምንጊዜም አንፀባራቂ አውራዎች እንዳሉ አንዘንጋ። ባንድ ቤትና ባንድ ወቅት ሊኖር የሚችለው አንድ አውራ ብቻ ነውና ለመረጥነው አውራ በቂ ሥልጣን እንስጠው። እንንከባከበው። እንደንቦቹ ዙሪያውን ከበን ከሀሳየ-መሲሆች እንጠብቀው። እንዲፈታልን የምንጠይቀው ችግር ባንድ ጀንበር የሚሞከር አይደለምና ዋና መሥመሩን እስካልሳተ ድረስ ቢያዳልጠውም “አይዞህ አለንልህ!” እንበለው። አውራ የሌለው ምንም እንደማይኖረው እንወቅ!

ከሁለት ገጽ በላይ መጻፍ መንዛዛት ነው የሚለውን የራሴን ህግ ሰበርኩ ልበል?

kuchiye@gmail.com

Friday, July 31, 2009

"መድረክ እንዲህ ሊያናቁር ይገባል?"
በአንድነት ፓርቲ ዙሪያ የሚናፈሰው ውዝግብ ወርደ-ሰፊ ትምህርት ያዘለ ነው።

ትምህርቱ ለፓርቲው ሀላፊዎችና ደጋፊዎች ብቻ ባድራሻ የተላከ ሳይሆን ባገራቸው ፖለቲካ ሕይወት ውስጥ ሁነኛ ለውጥ እናመጣለን ብለው ለሚባዝኑ ሌሎች ፓርቲዎች ጭምር የሚተርፍ ይመስለኛል። ከዲስኩር ላድናችሁ ብዬ ነው እንጅ በዚህ ዙሪያ ብዙ የምለው ነበረኝ።

አንድነት ውስጥ አሁን ለተፈጠረው ውዝግብ መነሻ የሆነው “መድረክ ውስጥ እንግባ አንግባ? የምንገባስ ቢሆን ምን ዳር-ድንበር አስቀምጠን ቢሆን ይሻላል?” የሚለው ነው። ሌሎች በበራሪ ወረቀት የሚበተኑ ክሶችና ሀሜቶች በተረፈ-ፖለቲካና በማድቤት ወሬነት የሚመደቡ ናቸው።

መድረክ በመሠረቱ፤
ማንም ይጀምረው ማን መድረክ ያለፈው 18 ዓመት የተዛባ የፖለቲካ ጉዞ የፈጠረው ህዋስ ነው። ዘረ-መል (ጄኔቲክ) ምንጩ የተለዬ ነውና ቀደም ባለው ዘመን ከተፈጠሩ ስብስቦች ጋር በመሳ ሊታይ የሚገባው አይደለም።

መድረክ ከሚነቀፍባቸው ምክንያቶች፤
መድረክ ላይ ከሚሰነዘሩት ነቀፋዎች መሀከል ሁለቱንና ዋናዎቹን ላንሳ። (ሀ) መድረክን የመሠረቱት የብሔር ድርጅቶች ናቸው፤ (ለ) መድረክ ውስጥ ሕዝባዊና ድርጅታዊ መሠረት የሌላቸው ግለሰቦች ተሰንገዋልና እነሱን ከድርጅት ጋር መሳ ማዬትና መወጣጫ እርካብ ማቀበል ጅልነት ነው የሚሉት ናቸው።

የብሔር ድርጅቶች የሆኑ እንደሆንስ?
ኢትዮጵያ ውስጥ የብሔር ድርጅቶችና የብሔር ስሜት የለም ብሎ ራሱን የሚያታልል ካለ በዚህኛው ክፍለዘመን የሚኖር አይደለም። የቱን ያህል ዘግናኝ ቢሆንም ያገራችን የፖለቲካ እውነታ የብሔር ቅኝት አለው። የቅኝቱ ቁስል መንግሥት ባለፉት አሥራ ስምንት ዓመታት ባካሄደው የተሳሳተ ዘመቻ ይበልጥ እንደሰፋ መዘንጋትም ስህተት ላይ ይጥላል። አንድ የዩኒቨርሲቲ መምህር በቅርቡ የገጠመውን ግራ መጋባት ላጫውታችሁ። መምህሩ በንግሊዝኛ አነበነበና ተማሪዎቹ ገብቷቸውና አልገባቸው እንደሆነ ጠየቀ። ጭንቅላቶች ግራና ቀኝ ተወዛወዙ። ችግሩ የንግሊዘኛ ቋንቋ ችሎታ መሆን አለበት አለና ትምሕርቱን በብሔራዊ ቋንቋው ባማርኛ ደገመውና ተከትለውት እንደሁ ጠየቀ። ጥቂት የማይባለው ክፍል አሁንም እንዳልተከተለው ተረዳ።

የመምህሩን ልምድ ከብዙ አኳያ ልንተነትነው የምንችል ቢሆንም ከጽሁፌ ዓላማ አንፃር ዓይኑን ያፈጠጠብኝ ነገር አለ። የብሄርን ጉዳይ የምንፈታው አግልለነው ሳይሆን ወደጉያችን ጠጋ አድርገን መሆኑን ነው። ባዲስ አመለካከትና በብልህ ስሌት መልክ ካልያሳዝነው አገራችን የምታመራበት አቅጣጫ እጅጉን አያምረም። ለዚህ ነው መድረክ ውስጥ ገብቶ መሥራትም ሆነ በተወሰነ ደርጃ ተሻርኮ መንቀሳቀስ ትክክለኛ የፖለቲካ አማራጭ መስሎ የሚታዬኝ።

ሌላም ልንስተው የማይገባን የፖለቲካ ቁምነገር አለ። መድረክ ውስጥ ያሉት ድርጅቶችም ሆኑ ግለሰቦች ይህን ያህል በብሔርተኝነት ልክፍት የተጠመዱ አይመስሉኝም - ያለፈው አሥራ ስምንት ዓመት የፖለቲካ ተመክሯቸው ብሔርተኝነት ለነርሱም ለክልሎቻቸውም ለኢትዮጵያም ጠቀሜታ እንደሌለው አስገንዝቧቸዋል የሚል ታሳቢ ማድረግ ይቻላልና። ከዚህም በተጨማሪ የምንኖርበት ዓለም ወደ ግሎባላይዜሺን መጣደፉ ትምህርት ሳይሰጣቸው ያልፋል ማለት ብልህነታቸው ላይ መሳለቅ ይሆናል አልሞክረውም።

“ታዲያ ይህ ከሆነ ድርጅቶቻቸውን ለምን ሕብረብሔራዊ አያደርጉም?” የሚል ጥያቄ ቢነሳ አግባብነት አለው። ወገኖቼ! ሁሉም ፖለቲካ መንደራዊ ነው የሚለውን ብሂል መዘንጋት የለብንም። ፌደራላዊው የፖለቲካ አወቃቀርና የባጀቱ አፈሳስስ አጉራ-ተኮር እንደመሆኑ መጠን እነዚህ ፓርቲዎች ደጋፊዎቻቸውን የሚደርሱት በዚሁ መሥመር በመጓዝ ይመስለኛል። በፈረንጁ አገር እንደምናየው “ፌደራል መንግሥቱ ጋር ተሟግቼ መንገድ አሠራሁልህ...ወዘተ” ማለት የማይችል ፓርቲና ፖለቲከኛ ዳግም ላይመረጥ ነውና አንዳንድ ፖለቲከኞች ይህን መንገድ ቢከተሉና መራጮቸውን ለመቅረብ መንገዳችን ይህ ነው ቢሉ ልንደነቅም ልንነቅፋቸውም አይገባም። ለነገሩ ብንደነቅና ብንነቅፍ ምን ለውጥ እናመጣለን?

ትንሺ ላክልበት። ፓርቲዎች የብሔር ቅኝት ስላላቸው ብቻ ሁሉም የአንቅጽ 39 አሺቃባጭ ናቸው ማለት አይደለም። ሁሉም ክልላዊ አወቃቀርን ይደግፋሉ ማለት አይደለም። እንዲህ ዓይነት ፓርቲዎች ጋር ተቀራርቦ መሥራት ብሔራዊ አንድነትን ሊያስገኝ የሚችል አጀንዳ በመቅረጽ ረገድ በር ይከፍታል። ካልተነጋገሩና አልፎ አልፎም “የቢራ ዲፕሎማሲ” ካላካሄዱ መተማመን አይገኝም፤ ስውር ጥላቻንና ጥርጣሬን ማስወገድ አይቻልም። ዴሞክራሲያዊ ባህልን ለማዳበርም ሆነ ከውዝግብ ነፃ የሆነች ኢትዮጵያን ለመፍጠር አይቻልም። ያችን የምታውቋትን ጥቅስ አሁንም ልድገማትና “የፖለቲካ መነሻውም መድረሻውም ንግግር ነው” ።

የታዋቂ ግለሰቦች ጉዳይ!
በመድረኩ ውስጥ በግለሰብ ደረጃ ከተሰባሰቡት መሀከል የስዬ አብርሃና የነጋሶ ጊዳዳ ስም ጎልቶ ይነሳል። ገብሩ አሥራት በአረና ትግራይ ጃንጥላ ሥር ይሁን እንጅ ስሙ በጅጉ ሲነሳ እሰማለሁ። ቀልዱን እናቁምና ሁሉም ሰው እኩል አቅም፤ እኩል ተደማጭነት፤ እኩል ዕውቅት፤ እኩል ልምድ እኩል ዝናና ግርማ-ሞገሥ የለውም። ባንድ በኩል “ሴሌብሪቲ” የምንላቸው አሉ በሌላ በኩል ደግሞ “እኛ” አለን። ምን ማድረግ ይቻላል? ጨካኝ ዓለም ናት!

ሁሉም እኩል ቢሆንማ ኖሮ እኔና ኃይሌ ገብረሥላሴ እኩል ልንደመጥ ነው፤ አንኳኩተን እኩል በር ሊከፈትልን ነው፤ በምርጫ ተወዳድረን ኃይሌን የማሸንፍ ዕድል አለህ ልትሉኝ ነው። ህልም!

እነስዬ መድረክ ውስጥም ሆኑ ከመድረክ ውጭም ሆኑ የሴሌብሪቲ ደረጃቸው የሚያስገኝላቸው የፖለቲካ እሴት አለ። የሚያመጡት ዕውቀት ልምድና ተከታይ አለ። ያሳለፉት ሕይወትም ሆነ በቅርቡ ዘመን የደረሰባቸው ጉስቁልና ስለራሳቸውም ስላገራቸውም ብዙ ያስተማራቸው አለ። ስለሌሎቹ አላውቅም እንጅ ስዬ አብርሃ በቪ.ኦ.ኤ ደህና ነገር ሲናገር ትዝ ይለኛል። ሙሉ በሙሉ አንጀቴን ባያርሰውም ገብሩ አሥራት ዋሺንግተን መጥቶ በተናገረው ላይ ማለፊያ ጅምር አይቸበት ነበር። ሰዎችን የምናቀርበውና የምናርቀው ብትናንት ተግባራቸው ብቻ እየመዝንን ከሆነ በማናውቀው ንግድ ውስጥ ተሰማርተናል ማለት ነው። በጨዋ ቤት ፖለቲካ የወደፊት ጥቅም ማስከበሪያና የወዳጅ ክበብ ማስፊያ መሣሪያ ነው። ባለጌ ቤት ደግሞ የቂም በቀል መወጫና የዜሮ ድምር ሙግት መንኮራኩር ይሆናል። ምድባችን ከባለጌዎቹ ጎራ እንዳይሆን አምላክን መማለድ ተገቢ ነው።

ከመዝጋቴ በፊት የምመኛቸውን ጥቂት ነገሮች ላካፍላችሁ። በትናንቱ ላይ የማላዘንና የቁርሾ አባዜያችን እንዲለቀን እመኛለሁ። ከዴሞክራሲያዊ ውይይት በኋላ በተደረጉ ውሳኔዎች ተገዥ መሆንን እንድንማር ልቦናችንን ይከፍትልን ዘንድ እመኛለሁ። ግለሰቦችም፤ ድርጅቶችም፤ መንግሥታትም የሚያመሩት ወደ ዝቅተኛው የውጤታማነት ዕድሜያቸው መሆኑን ይቀበሉ ዘንድ እመኛለሁ።
kuchiye@gmail.com
ማሳሰቢያ። አስፈላጊ ባይሆንም ከመድረክም ከተጠቀሱት ግለሰቦችም ጋር እውቅና እንደሌለኝ እገልጻለሁ

Saturday, June 13, 2009


"የግልገል ግቤ-3 እና የላሟ ታሪክ!"

“ላም እሳት ወለደችና እንዳትልሰው እሳት እንዳትተው ልጇ ሆነ!”
ይህ አባባል ግለሰቦችም ማሕበረሰቦችም በኑሮ ሂደት ውስጥ አስጨናቂ ምርጫ እንዲያደርጉ የሚገደዱባቸው ሁኔታዎች መኖራቸውን የሚያመለክት ነው። እነዚህ ሁኔታዎች ብንዘጋቸው የማይዘጉ፤ መልስ እስካላገኙ ድረስ ከፊታችን ዞር የማይሉ ችኰ ነገሮች ናቸው። 3ኛው የግልገል ግቤ ፕሮጀክት እንዲህ ሆኖብን ስለከረመ እንደልማዴ የማውቀውንና የሚሰማኝን ላካፍላችሁ መረጥሁ፡
ስለ ግቤ
ግቤ የተንጣለለውን የኢትዮጵያ ደቡብ ምዕራብ ክፍል እያካለለ መልኩን አሳምሮ ወደ ኬንያ ዳርቻ የሚነጉድ ወንዝ ነው። ታዲያ እርባና ያለው ሕይዎት ሳይኖር ቆይቶ በደርጉ ዘመን ሠርተህ ብላ ተባለ። ከዚያ በኋላ ግቤ-1 እና ግቤ-2 የሚባሉ ፕሮጀችቶች ተከናውነው 400 ሜጋዋት ኤለክትሪክ ኃይል የማመንጨት አቅም ተገንብቷል። ግቤ-2 ፍጻሜ ያገኘው በኢሕአዴግ ዘመነ መንግሥት መሆኑን መግለጽ ተገቢ ይመስለኛል።
ግልገል ግቤ-3
የግልገል ግቤ-3 ፕሮጀክት ፅንሰ-ሀሳብ በአፍሪካ ውስጥ ተወዳዳሪ የሌለው የኤሌክትሪካ ኃይል ማመንጫ ጣቢያ በመገንባት ላይ የተመሠረተ ነው። እንደ ግብጹ “አስዋን” ዳም ለኢትዮጵያ የልማት ሞተር ሊሆን የሚችል ሃይል ለመፍጠር ማለት ነው። የፕሮጀክቱ ሥራ ሦስት ቢሊዮን ዶላር አካባቢ እንደሚፈጅ ሲገመት በሚጠናቀቅበት ጊዜ 1870 ሜጋዋት እሌክትሪሲቲ ያመነጫል። ለንጽጽር እንዲረዳችሁ ያሁኑ የኢትዮጵያ አቅም የሚያሳዝን 600 ሜጋዋት ብቻ ነው። ለዚህ ነው አገራችን በኩራዝ የምትኖረው። ለዚህም ነው ዋና ከተማዋ አዲስ አበባ ሳትቀር በሳምንት ለሦስት ቀን የኮረንቲ ራሽን የተዳረገችው። ግልገል ግቤ-3 ካገሪችን ተርፎ ለጎረቤት አገሮችም የመሸጥ አቅም እንደሚያስገኝ ይነገራል።

ታዲያ ከባድ ችግር ተፈጥሮላችኋል! የግቤ ወንዝ ውልደቱም ጉልምስናውም እርጅናውም ኢትዮጵያ ውስጥ ሆኖ እያለ ኢትዮጵያ በዚህ ወንዝ እንዳሻት ልትጠቀም አትችልም የሚሉ ጉዶች ፈልተዋል። “በገዛ ዳቦዬ ልብ-ልቡን አጣሁት” ዓይነት ነገር መሆኑ ነው። እንዳሸን መፍላት ብቻ ሳይሆን ለዚህ ፕሮጀክት የሚያስፈልገውን ገንዘብ ኢትዮጵያ እናዳትበደር እያከላከሉም ነው። ግብጽና ሱዳን በግልገል ግቤ-3 ታላቅነት ተደናግጠዋል (ኬንያም እንዲሁ)። ኤንቫይሮንሜንታሊስቶች የሚያናፍሱት አጀንዳና የሚያፍሱት ዶላር በማግኘታቸው ፈንድቀዋል፤ እኛ ደግሞ በነገሩ ግራ ተጋብተን የላሟን ዓይነት ሆነናል። ሦስቱንም በየተራ ላስረዳ።
ግብጽና ሱዳን
በምናውቀው ምክንያት ግብጽና ሱዳን የኢትዮጵያን መጎልበት አይፈልጉም። ጠንካራ ኢትዮጵያ ማለት ካባይ ወንዝ ላይ ድርሻዋን የምትጠይቅ ኢትዮጵያ ትሆንባቸዋለችና ወደሠላምና ወደብልጽግና የሚወስዳትን ጎዳናዎች ሁሉ በፈንጅ ከማጠር አይቦዝኑም። ያባይ ወንዝ መነሻውን እስካልለወጠ ድረስ ከነዚህ አገሮች ጋር ያለን ባላንጣነት ይቀጥላል። ይህ ያጉል ተጠራጣሪ አመለካከት ሳይሆን (ኮንስፒረሲ ቲዎሪስት አለመሆኔን ታውቃላችሁና) ግብጦችም ደርቡሾችም በሰነዘሩብን ተደጋጋሚ ጦርነትና ባሴሩብን ሴራ መጎዳታችን በታሪክ የተመሰከረ ነው።

ግብጾች የግቤ-3ን ፕሮጀክት ለማሰናከል ጥድፊያ ላይ ናቸው ይባላል። በውሀ አጠቃቀም ሕግ የተራቀቁ ናቸው የሚባልልላቸው ድርጅቶቻቸው፤ ምሁራኖቻቸውና የዲፕሎማቲክ ጡንቻቸው የግቤ-3 ፕሮጀክትን “ጐጅነት” በማስተጋባት ላይ ይገኛሉ። የውሮፓ ኢንቬትመንት ባንክ፤ ዓለም ባንክና አሁን ደግሞ ያፍሪካ ልማት ባንክ ለግቤ-3 ገንዘብ እንዳያበድሩ ከኤንቫይሮንሜንታሊስቶች ጀርባ ሆነው ዘመቻ እያካሄዱ ነው። ዘመዶቼ! ግብጽ በዓለም አቀፍ መድረኮች ያላት ተደማጭነት ቀላል እንዳልሆነ ምንጊዜም መዘንጋት የለብንም ።
የኤንቫይሮሜንታሊስቶች ጫጫታ!
ኤንቫይሮንሜንታሊስቶች ጥሩ ጎን ያላቸውን ያህል አንዳንዱ ባሕርያቸው አስቂኝ ነው። ግቤ-3ን በሚመለከት ግድቡ ከተሠራ ያካባቢው ነዋሪ ሕዝብ ኑሮ ይበላሻል ይላሉ። ኤኮሎጅ ይናጋል ይላሉ። እስኪ በፈጠራችሁ የትኛው የኑሮ ዓይነት ነው የሚበላሸው? መለ-መላ የሚኬድበት? ከንፈር የሚተለተልበት? ረሀብ፤ ድንቁርና፤ መሀይምነትና በሽታ የነገሱበት? ወይንስ ደግሞ ጥቂት ቱሪስቶች የፎቶ አጋጣሚ አግኝተው የበላይነት ስሜት የሚገዙበት?

ቢማሮ አምደልካር የተባለው ከጋንዲ የሚተካከል የህንድ አባት “ምሁሩ በገጠሩ ላይ ያለው ፍቅር ማለቂያ የሌለው ብቻ ሳይሆን አሳፋሪም ነው” ይልና “በሀቅ ከተመለከትነው ገጠሩ የድንቁርናና የበሽታ ጉሮኖ፤ የጎሰኝነት ኩሬ፤ የጠባብ አመለካከት ጎተራ ነው” ብሎ ይደመድማል። እኔ ደግሞ “ኋላቀር የኑሮ ዘይቤዎችን አላግባብ የሚያወድሱና ከዘመናችን የኑሮ ዘይቤ ጋር መሳ-ለመሳ ለማስቀመጥ የሚሞክሩ እነርሱ ጤነኞች አይደሉም ደህና ሀኪም ያስፈልጋቸዋል።” እላለሁ

ስለ ኤንቫይሮንሜንት ካነሳን ዘንድ የዓለም ሥልጣኔ አስቸጋሪና አስቸጋሪ ያልሆኑ ምርጫዎችን እያደረገ ነው እዚህ የደረሰው። አሜሪካ፤ አውሮፓና እስያ የተገነቡት ኤንቫይሮንሜንት ሳይቀየር አይደለም። ሁቨር፤ አስዋን፤ ሜርዌ፤ ያንግቴዝና ሌሎችም እርቆ መሳፍርት የሌላቸው ግድቦችና ልማቶች ሲከናወኑ ሰፋፊ መሬቶች በውሀ መጥለቅልቅ ነበረባቸው። የታሪክ ቅርሶችና ማዕድኖች ሳይቀሩ በሐይቆቹ ሥር ማቅረታቸው አማራጭ አልነበረውም። እነዚህ ታላላቅ ፕሮጀክቶች የዜጎችን የኑሮ ደረጃ በመለወጥ በኩል ያደረጉት አስተዋጽኦ ግዙፍ ነውና ክርክር እንኳ አይጠይቅም።

ልብ በሉ። የመኖርና ያለመኖር ጥያቄ በተነሳ ቁጥር ኤንቫይሮንሜንት ሁለተኛ ደረጃ ትኩረት ነው የሚያገኘው። በኔ ግምት ግቤ-3 ለኢትዮጵያ የመኖርና ያለመኖር ጥያቄ ነው። የሚያወላዳ ሀብት ለሌላትና በመጨረሻው የድህነት እርከን ላይ ለምትገኝ ኢትዮጵያ “ኤሌክትሪፊኬሽን” አማራጭ የሌለው የልማት ርምጃ ስለሆነ የትኛውም መንግሥት ሥልጣን ላይ ቢሆን ወደኋላ የሚባልበት ጉዳይ አይሆንም። የምናዘገዬው ጉዳይም አይደለም።
ታዲያ ምኑ ነው እኛን ግራ ያጋባን?
እኛን ግራ ያጋባን የኢሕአዴግ ጉዳይ ነው። ኢሕአዴግ በላሟ ልጅ ይመሰላል። ከጎኑ እንዳንቆምና ያለም ባንኮችን ሎቢ እንዳናደርግ የኢሕአዴግ ደጋፊ ልንመስል ነው። አይተን እንዳላየን እንዳንሆን ደግሞ ያገር ህልውና ጥያቄ አለበት። የቅርብ ዘመን ታሪካችንን እንኳን መለስ ብለን ብናይ ይህ ትውልድ ሁለት ተመሳሳይ ፈተናዎች ገጥመውት እንደነበር ማስታወስ እንችላለን። አንደኛው በ1969ኙ የሶማሌ ጦርነት ጊዜ ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ በኤርትራው ጦርነት ጊዜ ነበር። ሕዝባችን ያደረገው ምርጫ ከመንግሥቶቹ ጋር የነበረውን ቅራኔ ለጊዜውውም ቢሆን ወደጎን አርጎ ባገር ጉዳይ ላይ ተረባረበ። የግቤን ጉዳይ በዚያ ትይዩ የማስቀምጥበት ምክንያት አለኝ። ይኸውም የታሪክ ጠባሳና መጥፎ “ፕሬሲደንስ” ፈጥረን እንዳናልፍ ከመስጋት ነው።
የምን ፕሪሲደንስ ነው ደሞ?
ኢትዮጵያ በአባይ ውሀ ሳትጠቀም ለዘመናት ኖራለች። በአንፃሩ ደግሞ የሱዳንና የግብጽ ሕልውና የተመሠረተው በዚህ ወንዝ ላይ ነው። ኢትዮጵያ በአባይ ወንዝ ላይ የረባ የባለቤትነት መብትና ያጠቃቀም ፕረሲደንስ አልመሠረተችምና በወንዙ ላይ ሁነኛ ፕሮጀክት እጀምራለሁ ብትል የሱዳንንና የግብጽን ስምምነት ማግኘት ያስፈልጋታል። ያለም ሕግ እነሱን ይደግፋልና። ህልውናቸውን ለማስጠበቅ በኢትዮጵያ ላይ ጦርነት እስከማወጅ የሚያደርስ መብት ይኖራቸዋል። ሰዶ ማሳደድ ይሏችኋል ይሄ ነው።

አባይ ጥሩ አስተምሮናልና ግቤ ወንዝን ሰደን ማሳደድ አንችልም። ስለሆነም ያለንን የባለቤትነትና የመብት ጥያቄ በማያወላዳ ሁኔታ የማረጋገጡ ጉዳይ ወሳኝ ነው። ለኤንቫይሮንሜንታሊስቶችና ለአሳዳሪዎቻቸው ግፊት ከተፈታንና መብታችንን አሳልፈን ከሰጠን ሀገራችን ሁነኛ ልማት ማካሄድ የምትችልበትን የመጨረሻ ዕድል አባከነች ማለት ይሆናል። ከመጨረሻው የድህነት እርከን ፈቅ ለማለት እንኳ ላንችል ነው ማለት ነው። ዛሬም ጎጅ ፕረሲደንስ ላለመክፈት እንጠንቀቅ። የውጭ ባላንጣዎቻችን ማለፍ የማይችሉትን መሥመር ዛሬውኑ እናስምር።

ይህን ስናደርግ ዴሞክራሲንና የሕግ የበላይነትን በሀገራችን ለማስፈን ከኢሕአዴግ ጋር የምናደርገውን ትግል እየቀጠልን መሆኑ አነጋጋሪ እንኳ አይደለም። በኔ ግምት ሁለቱ እንቅስቃሴዎች አይጻረሩም። እንዴትና በምን መልኩ የሚለውን ልንወያይበት እንችላለን። የቱን ያህል አስጨናቂ ቢመስልም በጉዳዩ ላይ ጨዋ ውይይት ማድረግን ልንሸሸው አንችልም።
ፀጋዬ ሙሉሸዋ በዚህ ጉዳይ ላይ ጥሩ ጽፏልና አንብቡለት። http://www.ethiomedia.com/adroit/2431.html

kuchiye@gmail.com

Friday, June 05, 2009


"ይድረስ ለውድ ብርቱካን!"
ቃሊቲ እስር ቤት - አዲስ አበባ


“ታውቅ ይሆን?” እያልኩ አወጣና አወርዳለሁ። “የስንቱን ህሊና እንደነካች ታውቀው ይሆን?” እላለሁ።

የሰሞኗ ጀንበር የምትጠልቀው የሁለተኛ ልጄን መወለድ ሳሰላስል ነው። ታዲያ ከየት መጣ የማልለው ጭንቀት በድንገት ይወረኛል። ጭንቀቱ ስለልጆቼ እንጅ ስለኔ እንዳይመስልሺ። “እኔ የማውቃትንና ያደግኩባትን ኢትዮጵያ፤ በማይነጥፍ የፍቅር እስተንፋስ ኮትኩቶ ያሳደገኝን ቀዬ፤ ይሰማኝ የነበረውን ልበ-ሙሉነትና ብሩህ ተስፋ፤ በበቂ የማይወሳለትን የወገኔን ጨዋነትና የመቻቻል ባህል.....ልጆቼ የነዚህ ቅርሶች ባለቤት የመሆን ዕድል ይገጥማቸው ይሆን?” እያልኩ ነው የምጨነቀው።

ከአጉል ውዳሴ አይቆጠርብኝ እንጅ ምንኛ ስሜቴን እንደነካሺው ላሳውቅሺ እፈልጋለሁ። ከቃሊቲ እሥር ቤት በጥር ወር 2006 ገደማ የፃፍሺውን ደብዳቤና አሁን በታህሳስ 2008 እንደገና ወደ እስር ሊወረውሩሺ ሲዘጋጁ “ቃሌ!” በሚል ርዕስ ለሕዝብሺ የሰጠሺውን ምስክርነት ደጋግሜ አነባቸውና ስሜቴ ሲታደስ አየዋለሁ። አልፎ አልፎም ይሁን እንጂ ዓለማችን ጠንካራ መንፈስ ኖሯቸው የተስፋ ራዕይ በሚናኙ ሰዎች መታደሏን አስታውሼ እጽናናለሁ። ስለጠንካራ መንፈስሺና ስለ ተስፋ ሰጭነትሺ ከልብ አመሰግንሻለሁ።

ውድ ብርቱካን!
ቀይ ሺብርና ነጭ ሺብር የወላጆቻችንን ቅስም ሰብረው ለስደት ኑሮ ዳረጓቸው። አሁን ደግሞ ሕዝባችንን በጎሳና በሀይማኖት ለመከፋፈል የሚረጨው መርዝ የምንተነፍሰውን አየር እየበከለው ይገኛል። ለዚህ ነው ያሁኑም ትውልድ ስደተኛ እየሆነ የመጣው። አየሺ! ያምባገነኖች ተግባር ርኩስ ነው የሚባለው ተቀናቃኞቻቸውን በመፍጀታቸውና በማፈናቸው ብቻ አይደለም። ከዚያ ባላነሰ የሚጎዱን መጭው ትውልድ የተስፋ ባለቤት እንዳይሆን በሚያካሂዱት የሥነ-ልቦና ጦርነት ነው።

“ዴሞክራሲንና በሥነ-ምግባር የታነጹ መሪዎችን መሻት መብታችን ነው!” ማለትን ካቆምን፤ ተፈጥሯዊና ሕገመንግሥታዊ መብታችንን ከጃችን ሊመነጭቁ ሲመጡ “ወግዱ አናስነካም!” ማለትን ካልለመድን ያኔ ነው የሺንፈትም ሺንፈት የሚሆንብን። ለዚህም ነው ያንች “ወግዱ!” እና “መብቴን አላስነካም!” ለሁላችን ምሣሌ የሆነው።

ኢሕአዴግ ሊያሳምነን የሚጥረው ኢትዮጵያ ከዚህ የተሻለች መሆን እንደማትችል ነው። የተሻለ ዴሞክራሲ፤ የተሻለ ፍትህ፤ የተሻለ አስተዳደር ሊኖር እንደማይችል። የሚመራንን ፓርቲ ስንመርጥና ለዴሞክራሲ ዝግጁ መሆናችንን ስናስመሰክር የዴሞክራሲን ጎዳና ፈጽሞ ይዘጋዋል። የጎሣ ፖለቲካ እንዳላመቸው ሲረዳ የሀይማኖትና ሌሎች ልዩነቶችን ያሰፋፋል። ይሁን እንጅ ኢሕአዴግ ራሱ የማይስተው አንድ ዕውነታ አለ። የሚቆጣጠራቸውን የእርሻ መሬቶች፤ የፋይናስና የንግድ ድርጅቶች፤ ትልቅ ደመወዝ ከፋይነቱንና ወታደራዊ ኃይሉን የጭቆናና የማባበያ መሣሪያ ባያደርግ ኖሮ ላንድ ጀንበር ሥልጣን ላይ እንደማይቆይ ያውቃል። በሕዝባዊ ፍቅር ተከልሎ በሁለት እግሩ የቆመ መንግሥት እንዳልሆነ ያውቀዋል። ባለሥልጣኑም ካድሬውም ሠራዊቱም በውስጣቸው ይህን ያውቃሉ።

ውድ ብርቱካን!
ኢሕአዴግ በጥፋት ጎዳና መጓዙን አቁሞ የሕዝብና ለሕዝብ የሚያደርገውን ጎዳና ቢመርጥ የሁላችንም ምኞት ነው። የኛው መንገድ የአንድነት የዴሞክራሲ የመብት የዕኩልነትና የዕርቅ ስለሆነ በፍቅርና በተስፋ ተሞልቷል። ለሰው ልጅ ከተስፋ የሚበልጥ ቁምነገር የለምና ተስፋን ምርኩዛችን እስካደረግን የነገው ሕይወታችን ከዛሬውው የተሻለ እንደሚሆን አንጠራጠርም።

የተስፋን የአንድነትንና የጥንካሬን ካባ ስላላብሺን ለውለታሺ መጠን የለውም። በቅርቡ ከእስር ወጥተሺ የጀመርሺውን ያዲስ ትውልድ አደራ እንድትወጭ፤ ያዲሲቷን ኢትዮጵያ ጉዞ አብረሺን እንድትጓዥ እንጸልያለን። የኔዎቹ ሁለቱ እንዲሁም ያንችዋ “ሄሌ” እጅግ መልካም የሆነች ኢትዮጵያ ትኖራቸዋለች።
kuchiye@gmail.com

Friday, May 29, 2009

"መሬት የመቸብቸቡ ጉዳይ! "

ችስታ የመታቸው አገሮች ሰፋፊ መሬታቸውን ለውጭ መንግሥታት በገፍ የመቸብቸባቸው ፈሊጥ በዓለም መድረኮች አነጋጋሪ ሆኗል። በኛው አካባቢም ብዙ ንትርክና ቁጣ እንደጫረ ተረዳሁና ጉዳዩን መመርመር ጀመርኩ። ሳያጣሩ ወሬ ሳያነቡ መምሬ መሆን አጉል ነውና በመጠኑም ቢሆን አንብቤ ያገኘሁትን ላካፍላችሁ።

ሳኡዲ፤ ኤሚሬት፤ ኳታር፤ ኩዌት፤ ግብጽ፤ ሊቢያ፤ ቻይና፤ ደቡብ ኰርያና የመሳሰሉትን አገሮች የእህል ዋጋ ሰማይ እየነካ መሄዱ የምግብ ሴኪውሪቲ እያሳጣቸው ነው። ባዮ-ፊውል ለማውጣት ሲሉ ፈረንጆቹ ለዓለም ገበያ የሚቀርበውን እህል መቀነሳቸውም ሼኮቹን ያስደነቀ አይመሰለኝም።

ይሁን እንጅ እንደ ሳኡዲ ያሉትን የናጠጡ ሀብታሞች ያሳሰባቸው ከላይ የተጠቀሰው ብቻ አይደለም። ሳውዲዎች በማይታመን ዋጋም ቢሆን እህል በበረሀ ውስጥ ያመርታሉ። የሳውዲ እርሻዎች ለብሔራዊ ኩራት ምንጭ ሆነው ይቆዩ እንጅ በከርሰ-ምድር ያለውን የውሀ ክምችት ክፉኛ በሟሟጠጥና አካባቢን በመበከል ረገድ ጋውፋህ (የተሲያት እንቅልፍ) የሚነሱ ዓይነት ሆነውባቸዋል። በኢትዮጵያው ኮንትራት የተመረተው ሩዝ በታላቅ ሥነ-ሥርዓት ታጅቦ ለሳኡዲው ንጉሥ ሲቀርብላቸው በፈገግታ የተሞሉት ያለምክንያት አልነበረም። ለምን አይሞሉ? ርስቱ ከወንዝ ባሻገር፤ የተገኘው በነፃ፤ የኤክስፖርት ታክስ አይከፈልበት፤ የሚሟጠጠው የሌላ አገር ውሀ፤ የሚመረዘው የሌላ አገር መሬት።

ከወዲሁ ላስጠንቅቃችሁና የውጭ ኢንቬስትመንት ለዕድገት እጅግ አስፈላጊ ግብአት ነው ከሚሉት ወገን ነኝ። ስለሆነም የመሬቱን ኮንትራት የማየው በ “ጠርጥር” መነጽር ተጋርጄ አይደለም። ለዚህም ነው አዲስ ዓይነት “የጅ-አዙር ቅኝ አገዛዝ” ወዘተ የሚለውን ዝባዝንኬ ክርክር የማልስማማበት። አገርም ግለሰብም የሚፈርሙትን ውል በቅጡ ካሰቡበትና ጥቅማቸውን ለማስከበር በቂ ጥንቃቄ ካደረጉ የጅ-አዙርም የሌላም ዓይነት ቅኝ አገዛዝ ሰለባ አይሆኑም። ደ!

በነገራችን ላይ በመሬት ችብቸባው ንግድ የተሰማራችው ኢትዮጵያ ብቻ ሳትሆን ሱዳን፤ ዛምቢያ፤ ታንዛኒያ፤ ኮንጐ፤ ሞዛምቢክ፤ ካምቦዲያ፤ ዩክሬን፤ ሰርቢያና የመሳሰሉት ጭምር ናቸው። ሩስያ አውስትራሊያና ብራዚልን የምያካክሉ የዳጎሰ ኤኮኖሚ ያላቸው ሳይቀሩ ከነሳኡዲ ጋር ሽር ጉድ እያሉ ነውና ያዲሱ ዓለም የኢንቬስትመንት ቄንጥ ይህ እንደሆነ እንወቅ። በዚህ ረገድ ኢትዮጵያም ድርሻዋን ለማግኘት ብትሯሯጥ ልንገረም አይገባም - ኢንቬስትመንት ካፒታል እንደሷ የሚያስፈልገው አገር የለምና።

ታዲያ ችግሩ የት ላይ ነው? በጣም ጥሩ ጥያቄ። ችግሩ ያለው መሬት የሚቸበችቡት አገሮች ግልጽነትንና ተጠያቂነትን በማያውቁ መንግሥታት ሥር የሚተዳደሩ መሆናቸው፤ አኮናታሪዎቹም ተኮናታሪዎቹም ሙስናን ባህል ያደረጉ መሆናቸው፤ የውል ዝርዝሩ ድብቅ መሆኑ፤ ኢንቬስተሩ ያመረተውን እህል ሙልጭ አድርጎ ወዳገሩ ወይንም ወደ ዓለም ገበያ የመውሰድ መብት እንዲኖረው መደረጉ ይገኙበታል። ይህ ብቻ አይደለም! ውሉ ስለከባቢ ዓየር መበከል፤ ስለብሔራዊ የውሀ ቋት መሟጠጥ፤ ስለነዋሪው ሕዝብ መፈናቀል ከመጨነቅ ይልቅ የኢንቬስተሩንና የውል ሰጨዎችን ኪስ በማሟሸት ላይ የተጣደፈ ነው የሚሉም ይበዛሉ። እኔ ማነኝና ነው አዋቂዎች የሚሉትን ላስተባብል የምሞክረው? እንቀጥል…

ከኢንቬስተሮቹስ ምን ይጠበቃል? ይህም ሌላ ጥሩ ጥያቄ ነው። ኢትዮጵያን በሚመለከት ከሳውዲ ኢንቬተሮች ጋር የተፈረመው ውል በምስጢር ስለተያዘ ምን ዝርዝር እንዳለው አይታወቅም። ይህ ነው እንግዲህ ግልጽ ያለመሆን ጣጣ። ኢንቬስተሮቹ የሚሉት የሥራ ዕድል፤ ምርጥ ዘር፤ አዲስ ቴክኖሎጅ፤ ዘመናዊ ማኔጅመንት፤ ትምህርት ቤቶች፤ ክሊኒኮች፤ ይዘን እንመጣለን ነው። ከተጠቀሱት ጥቅሞች ኢትዮጵያ ምን ያህሉን እንዳገኘች የሚያውቅ ሰው ካለ ይንገረንና የትኞቹ ዕውንት የትኞቹ ደግሞ ባዶ ተስፋ እንደሆኑ መለየት እንችላለን።

እስከዚያው ድረስ ግን ከሌሎች አገሮች ያገኘነውን ተመክሮ መሠረት አድርገን መወያየቱ ክፋት የለውም። ሌሎች አገሮች ውስጥ የተቋቋሙ የ “መንግሥት-ለመንግሥት” ወይንም የ “መንግሥት-ግል” የርሻ ኮንትራቶች ብዙ ፋይዳ አሳይተው እንደማያውቁ ያለም ታሪክ ይመሰክራል። ለነገሩ መንግሥት የሚይዘው ነገር የት ቦታ ነው ፈይዶ የሚያውቀው? ባንጻሩ ደግሞ የውጭ የግል ኢንቬስተሮች ካገሬው የግል ኢንቬስተሮች ጋር የሚጀምሯቸው ፕሮጀክቶች ብዙ ውጤት ታይቶባቸዋል። የኢትዮጵያ መንግሥት ሁሉን በጄ ከሚለው አባዜ እስካልተላቀቀ ድረስ የሳውዲውም ሌሎችም ፕሮጀችቶች ብዙ ዕድሜ እንደማይኖራቸው ከወዲሁ መመስከር ይቻላል።

ወደማጠቃለሉ ላምራ። ከላይ እንደጠቀስኩት የውጭ ባለካፒታሎች በደሀ አገሮች ውስጥ የእርሻ ሥራ ለማስፋፋት መሺቀዳደማቸው የዘመናችን ክስተት ነውና ልናቆመውም ልንሸሸውም አይገባም። ጥያቄው ኢንቬስተሮች ይግቡና አይግቡ ከሚለው ላይ አይደለም - ይህ ብዙ አያከራክርምና። ፍሬ ነገሩ ያለው እንዲህ ያለው ውል ሁለቱንም ወገን ሚዛናዊ በሆነ መንገድ የሚጠቅም ነው አይደለም ከሚለው ላይ ነው። ለዚህ ደግሞ የግልጽነት ጥያቄ ወሳኝ ይሆናል። ያገሬው ኢንቬስተር ተሳታፊነት ወሳኝ ይሆናል። ብሔራዊ ጥቅም የማስከበሩ ጉዳይ ወሳኝ ይሆናል። ተገቢው የኤንቫይሮንሜንት ሕግ መውጣቱና ማስከበሪያ መሣሪያዎቹም መደራጀታቸው ወሳኝ ይሆናል። የውጭው ካፒታል የሚንቀሳቀስበት የሕግ ዳር-ድንበር መከለሉ ወሳኝ ይሆናል። ስለሚፈናቀለው ገበሬና በከብት-ርቢ ስለሚተዳደረው ሕዝባችን እጣ-ፈንታ በቅጡ ማሰብ ወሳኝ ይሆናል።

ከሁሉም በላይ ደግሞ የዴሞክራሲ የመልካም አስተዳደርና የሕግ የበላይነት መስፈንን የግድ ይላል።

እነዚህ ሳይሆኑ ቀርተው የመንግሥት ቢሮክራቶች በግብታዊነትም በሌላ ተነሳሺነትም የሚያደርጉት ውሳኔና የሚፈራረሙት ውል የሚያስገኘው ጥፋትና ኪሣራ ነው። በቆቃ ሀይቅና በወንዞቻችን ላይ እየደረሰ ያለው ሁኔታ አሳዝኖን ከሆነ ይኸኛው ደግሞ ከትውልድ ወደትውልድ የሚተላልፍ የሀዘንም ሀዘን ይሆናል። የኢትዮጵያ ሕዝብ የውሎቹን ዝርዝር የማወቅ መብት አለው።

Kuchiye@gmail.com

----------
(እንግሊዝ ለሚቀናችሁ፡ “The Economist” May 23, 2009 አንብቡ። ብዙውን ያገኘሁት ከዚያ ነው)

Tuesday, May 05, 2009

"ኤይድስ በዳያስፖራው ኢትዮጵያዊ መንደር! "

ከዲሲ ሕዝብ 3% ያህሉ በኤይድስ በሽታ የተበከለ ነው። አንዳንዶች ማዕከላዊ ቁጥሩ ከዚህም እጥፍ ይሆናል ይላሉ። የጥቁሩን ሕብረተሰብ ብቻ ነጥለን ብንወሰድ 7% የሚሆነው የበሽታው ሰለባ ሆኗል።

ዛሬ የኤይድስ አክቲቢስት መስየ የቀረብሁት በበቂ ምክንያት ነው። በውጭ ከሰፈረው ኢትዮጵያዊ ወገናችን አብዛኛው መቶኛ ዋሽንግተን ዲሲ አካባቢ የሚኖር ስለሆነ ሁኔታው በግለሰብም፤ በማህበረሰብም ደረጃ ሊያሳስበን ይገባል። ከዚያም አልፎ ሊያስደነግጠን ይገባል። በጤናው መስክ የተሰማራ ወዳጄ በኢትዮጵያዊው ህብረተሰብ ውስጥ የኤይድስ ቁጥር በከፍተኛ ደረጃ እየጨመረ መምጣቱን ያጫወተኝ አይቼበት ከማላውቀው ትከዜ ጋር ነበር። በሱ ግምት የሀበሻው ሕብረተሰብ ተነጥሎ ቢጠና የተለከፈው ወገን ከ 10% እንደማያንስ አልተጠራጠረም። በተለይ ወጣቱ አካባቢ።

የዋሺንግተን ዲሲው ኤች አይቪ ኤይድስ ሁኔታ የወረርሽኝ ያህል አስደንጋጭ ደረጃ ላይ ስለደረሰ የመንግሥትንና የሕብረተሰቡን ትኩረት እያገኘ ነው። በሀበሻው መንደር ግን ግንዛቤውም ድንጋጤውም ጎልቶ አለመታየቱ እጅግ ያሳስባል!

ከወዳጄ ጋር ጭንቅላቶቻችንን ለጥቂት ጊዜ አጋጨንና የሚከተሉትን ቁምነገሮች ልናካፍላችሁ ተስማማን። በዚህ ዓለም ላይ ባለማወቅ ከምናደርጋቸው ስህተቶች እያወቅን የምንፈጽማቸው በጅጉ እንደሚበዙ የሰው ልጅ ታሪክ የመሰከረው ነውና የምናውቀውንም እንደገና መማማራችን አስፈላጊ ነው። ከተወሰነ ፍጥነት በላይ መንዳት ቅጣት እንደሚያስከትል እያወቅን ቲኬት የተከናነብን ስንቶች ነን? በኤይድስ ላይ የሚደረግ ውይይትንም በዚሁ መልኩ እንየው።

ኤይድስ መሠሪና ፈሪ ጠላት ነው። አዕምሮአችን በመጠጥ ወይንም በፍትዎት የተዘናጋበትን ሰዓትና አሳቻ ቦታ መርጦ ያጠቃል። ስለሆነም መጠጥ መጠጣት ካለብን ልካችንን እንወቅ።
ፍትዎት እንደታንጎ ሁለት ደናሺ ይጠይቃል። እኔ ጥንቁቅ ነኝና ጓደኛየም ትንቁቅ ትሆናለች ማለት አይቻልም። ያልተጋቡ ጓደኞች ኮንዶም መጠቀምን ከጀግንነትና ከስልጡንነት ሊቆጥሩት ይገባል። የኮንዶም ፍትዎት ያለኮንዶም ከሚደረግ ፍትዎት እኩል እንደሚጥም አዕምሮአችን ይቀበለው። ባለትዳሮችም ቢሆኑ አንደኛው ወገን በምንም መነሻ ይሁን ስጋት አደረብኝ ካለ “እንመርመር ቀፈፈኝ” ማለትን መፍራት የለበትም። ሌላው ወገንም እንዴት ተደፈርኩ! ብሎ አካኪ ዘራፍ አይበል። ምርመራው ለሁለቱም ይበጃል፤ መተማመንና ፍቅርን ያጠናክራል።
ሀገር ቤትን እንፍራ። አዎን ያገር ቤት ጉብኝትን መፍራት ነው። ያገራችን ሴቶች ቀድሞውንም ቆንጆ መሆናቸው አንሶ አሁን ደግሞ ይበልጡን እያማሩና እያማለሉ ሄደዋል። ኢትዮጵያ በዓለም ከፍተኛ የኤይድስ ተሸካሚ ከሚባሉት አገሮች አንዷ መሆኗን ስንገነዘብ፤ ሥራ አጥነት ወጣቱን በፍትዎት ንግድ ውስጥ እንዲሰማራና የቤተሰብ ሀላፊነትን እንዲሸከም ያስገደደበት አገር መሆኑን ስናይ፤ “ረሀብ ባንድ ቀን ይገድላል ኤይድስ ፋታ ይሰጣል” የሚሉት አሰቃቂ ቀልድ የነገሰባት አገር ሞሆኗን ስንረዳ፤ ከልማት ይልቅ የቡና ቤቶች የክለቦችና የማሳጅ ፓርለሮች ኢንዱስትሪ እንደ እንጉዳይ የፈሉባት አገር መህኗን ስናስታውስ፤ ሙያ ይመስል አዲሳባ ባንኮክን ሆናለች እያለ የፍትዎት ቱሪዝምን የሚያሞግስ ትውልድ የበረከተበት አገር መሆኗን ስንረዳ ዳያስፖራውያን ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግ እንዳለብን እንረዳለን። ዶላርንና የውሸት ትዳርን አሰፍስፈው የሚጠብቁ እነርሱ አደገኞች ናቸውና እንቆጠብ።

በዋሽንግተን ዲሲ አካባቢ የሚኖረው ኢትዮጵያዊ በኤይድስ ወረርሽኝ በከፍተኛ መቶኛ የተመታው አገር ቤት ጋር ባለው ንኪኪ እንደሆነ በድፍረት መናገር ይቻላል። በሌላው ያሜሪካ ክፍልና በሌላው ክፍለ ዓለም ያሚኖረውም ኢትዮጵያዊም ከዚህ መቅሰፍት የተከለለ አለመሆኑን መዘንጋት የለበትም።

ገለልተኛነታችን ሊጎዳን መሰለኝ። ሀበሾች ስንባል ከሌላው ስደተኛ ህብረተሰብ በበለጠ በራሳችን ማህበረሰብ ውስጥ ተከልለን መኖርን እንመርጣለን። ይህ ተፈጥሯዊ መነሻ ቢኖረውም ተቋሞቻችን የሚገባንን እንክብካቤና ትመህርት ከሚሰጡበት የዕእድገት ደረጃ ላይ ካልደረሱ ተጎጅዎች እንሆናለን። አሜሪካኖቹ ኤይድስን በሚያክል አደገኛ ጠላት ላይ በሚያካሂዱት ዘመቻ ላንሳተፍ ነው። በዚህ በሽታ የተጠመዱ ወገኖቻችን ተደብቀው እንዲኖሩና ራሳቸውንም ሌሎችንም እንዲጎዱ ሰበብ እየሆንን ነው። ሀበሻው ጋር አድረን ሀበሻው ጋር ውለን ሀበሻው ጋር እስካመሸን ድረስ እንዲህ ያለ አደጋ ይመጣል፡፤

እናስ ታዲያ ምን ይሁን? እናማስ ሀላፊነት እንውሰድ። በየግላችን መውሰድ የሚገባንን ርምጃ በሃላፊነት ስሜት እንወጣ። ልጆቻችንንም ሰብሰብ አድርገን ያለ መሽኮርመም በዚህ ጉዳይ ላይ መወያየት ነው። በሞት ፊት መሽኮርመምን ምን አመጣው?

የሀይማኖት የፖለቲካና የማህበራዊ ተቋሞችም ችግሩን እያዩ እንዳላዩ አይሁኑና ይህን መሠሪ ጠላት በመዋጋት ረገድ አመራር ያሳዩን። ሦስቱም ቢሆኑ ጤነኛ ሕብረተሰብ በሌለበት ሊጠነክሩና ሊከበሩ አይቻላቸውም። በንዲህ አይነት ቅዱስ ዘመቻ ውስጥ የነቃ ተሳትፎ ያሚያደርግ ተቋም ከበሬታም ያገኛል የአባላትና የደጋፊ መሠረቱንም ያሰፋል። ኤይድስ በርዕዮተ ዓለምና በሀይማኖት ቀኖና ላይ የሚያሾፍና የሚረታ ሴሰኛ ባላንጣ ነው።


ቁጥር ቀልባችሁን ያስገኝልን እንደሁ ትንሺ በቁጥር እናስደንግጣችሁ። ዊኪፒዲያ የተባለው ድርጅት ለአቅመ አዳም የደረስውን በኤይድስ የተለከፈ ሕዝብ እንዲህ ያስቀምጠዋል። ታንዛኒያ 8.8% ኬንያ 6.7% ኮንጎ 4.9% ኢትዮጵያ 4.4% ። የሲ.አይ.ኤው ርፖርት ደግሞ የኢትዮጵያውን ወደ 10-18% ይተምንና በ 2010ዓ/ም ደግሞ ከ19-27% እንደሚደርስ ያሳስባል።

እንግዲህ የዲሲው ኤይድስ መቶኛ ከሦስተኛው ዓለም መቶኛ መብለጡ ካላስደነገጠን ምን ሊያስደነግጠን እንደሚችል አናውቅም። ዲሲን ከሦስተኛው ዓለም ጋር እንመድበው ይሆን?

Kuchiye@gmail.com

Monday, April 20, 2009

"ከተለየኸን ደህና ሁን!"
ለጥላሁን ገሠሠ ሙዚቃ ሙት መሆኔን አገር ያውቃል። የርሱ ሙዚቃ ዳግም ላይሰማ ይታገዳል ያሉኝ ይመስል ከሰሞኑ መልሼ መልሼ የማዳምጠው ጥሌን ብቻ ነበር።

እንደኔ ሙዚቃን የሚያሻምድ ሰው ጥላሁን ለትውልዳችን የተሰጠ ልዩ በረከት፤ የዕምነታችንና የሁሉም ዓይነት ምኞታችን መገለጫ ነው ብሎ ከደመደመ ቆይቷል። አጋነንክ የሚል ከመጣም እስከመጨረሻው እሞግተዋለሁ እንጅ እንደ ሉሲና እንደ አክሱም ሀውልት ብሔራዊ ቅርሳችን ነው ባይ ነኝ። ለዚህ ይመስለኛል የጥላሁን ዜና-ዕረፍት እንደተሰማ ሚሊዮኖች በመብረቅ የተመታ ያህል ባሉበት የደረቁት፤ ያነቡትና የተከዙት።

የኔው ድንጋጤና ሀዘን ግን ወደ ፍስሐና ወደ መስጋና ሲለወጥ ፋታ አልፈጀበትም። ልማድ ሆኖብኝ ሲከፋኝና ፍቅር-ፍቅር ሲለኝ ኮምፒውተሬ ላይ ዘወትር በተጠንቀቅ የሚጠብቀውን የጥሌን ሙዚቃ ነው ጠቅ የማደርገው። ዛሬም ያንኑ አደረግሁና ወደ ትራክ ስድስት መራሁት። የሙዚቃው አጀማመር ገና ከመነሻው ምድርን ቃጤ የሚያደርግ ዓይነት ነው፤ በጣም የተሟሟቀ፤ የጥድፊያ ጥሪ ያለበትም የሚመስል…...ጥሌን የሚጣራ የሚመስል። ወዲያው ተቀላቀሉ ጥሌና ሙዚቃ…..ይለቀው ጀመራ በዚያ መረዋ ድምጹ!

“ያሳለፍነው ዘምን ደስታን ያየንበት…….ተመልሶ ቢገኝ አሁን ምን አለበት”
እ….ህህ! እህ..እህህ! አይይይይ!

ይሄን ሙዚቃ ስንቴ እንደሰማሁት የሚያውቀው ፈጣሪ ብቻ ነው። ጥላሁን እጅግ አስቸጋሪ የሆኑ ኖታዎችን አዋህዶ የዘፈነበትና የድምጹ ቅላፄ ጐልቶ የወጣበት በዚህ ዘፈን ይመስለኛል። ቢሮዬ ወዲያው ተሟሟቀ። ለቀቅሁት እኔም እንዳቅሜ… አጀብኩት ጥሌን። ቢሮዬ ውስጥ ማን ለሲማኝ? ምድረ ፈረንጅ “ምን ተፈጠረ?” ብሎ ቢመጣም በቂ ምክንያት አለኝ አልኩ። የከበረና የተባረከ ህይወትን እየተሰናበትሁ ነው ካልኳችው እንደሚገባቸው አልተጠራጠርኩም። መቼም ፈረንጆች አይደሉም? ቀጠልን እኔና ጥሌ!.. “እ….ህህ! እህ..እህህ! አይይይይ!” አልን። ስንቱን ባነሆለለ ፈገግታው አየት ያደረገኝና “ቀጥል! ጥሩ ይዘሀል!” ያለኝ መሰለኝ ምን ገዶኝና ማንን ፈርቼ? ቀጠልኩ የጥሌን ትዝታና ውለታውን በልቤ እየመዘገብሁ።

ይሄ ነው እንጅ አልኩ! እንዲህ ነው እንጅ ጥሌን ማስታወስ። 55 ዓመት ሙሉ የምድረ ሀበሻን ቤት በደስታና በፈንጠዝያ የመላ፤ ያሳቀ፤ ያስደለቀ፤ መድረኮችን ያስጨነቀ፤ የወደደና ያዋደደ። ሺኝቱ በተለየ መሆን አለበት አልኩ። ልንሸነው የሚገባው በትዝታ ቅኝት፤ በባቲ ለዛ፤ ባንች-ሆየ ቃና፤ በ “ሠላመካ” ዝማሬ መሆን አለበት ብዬ ወሰንኩ። የ “አልቻልኩም”ን ጀግና፤ የ “ይህ ነው ፍላጎቴን” መሪ-ጌታ የምንሸኘው ከበሮው እየተደለቀ፤ ሳክሱ እየሳቀ፤ ትራንፔቱ እያማለለ ሊሆን ይገባል አልኩ።

ጥላሁን ዝንተ ዓለም አይረሳም። መሰል-የለሺ እንጉርጉሮዎቹን፤ ግርማ ሞገሱንና የርሱ ብቻ የሆነ ለዛውን በውስጠኛው የምናባችን ክፍል አትሞብናልና። የዘመናችንን የኪነት የበህር ልጅ እንዴትስ ልንረሳው ይቻለናል?

በል ደህና ሁን ጥሌ! ከተለየኸን… ደህና ሁን!
Kuchiye@gmail.com

http://www.voanews.com/horn/amharic_audio.cfm